
ከ 35 ደቂቃዎች በፊት
በካምብሪጅ ዩኒቨርስቲ መጋዘን ውስጥ 350,000 መሆናቸው የተገመተ የአፍሪካ ቅርሶች፣ የእጅ ጽሑፎች፣ የሰው ቅሪተ አካሎች፣ ፎቶግራፎች እና የተፈጥሮ ታሪክ ናሙናዎች ተገኙ።
ዩኒቨርሲቲው ካከማቻቸው ስብስቦች ውስጥ ግብፅ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ አርኪዎሎጂያዊ ቅርሶች እና የእጅ ጽሑፎች ያላት አፍሪካዊ አገር ነች ተብሏል።
ዶ/ር ኢቫ ናሙሶኬ ከካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ ቅርሳ ቅርሶቹን ለመለየት ከዩኒቨርስቲው የቤተ-መጻሕፍት ሠራተኞች፣ አስተዳዳሪዎች፣ ቤተ-መዛግብት አስተዳዳሪዎች እና ሰናጆች ጋር በመሆን በመጋዘናቸው ውስጥ ለ15 ወራት ማሳለፋቸው ተገልጿል።
ትላልቅ ሙዚየሞች ያላቸውን ስብስቦች በሙሉ አለማሳየታቸው “በጣም የተለመደ ነው”፤ ነገር ግን “በዚህ መጠን እና ዓይነት ከመላው አፍሪካ አህጉር እንዲሁም አንዳንዶቹ ቅርሶች ለበርካታ አስርታት ዓመታት ተቀምጠው መገኘታቸው አሁንም የሚያስገርም ነው” ሲሉ ተናግረዋል።
ፕሮጀክቱ ዩኒቨርሲቲው በቅርብ ጊዜ ሙዚየሙ ከቅኝ ግዛት እና ከባርነት ጋር ተያይዞ የሚነሱበትን ጥያቄዎች ለመቅረፍ የተጀመረ ሲሆን፣ እግረ መንገዱንም አብዛኞቹ ቅርሶች በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ወቅት የተገኙ መሆናቸውን አሳይቷል።
የፊትዝዊሊያም ሙዚየም ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑት ዶ/ር ናሙሶኬ ከአፍሪካ ጋር የተያያዙ አብዛኞቹ ቅርሶች አሁንም ለሕዝብ ዕይታ አይቀርቡም።
አሁን ግን በስፋት ለዕይታ እንደሚቀርቡ እና ጥናት እና ምርመር እንደሚሠራባቸው ባለሙያዋ ተስፋ አድርገዋል።
እነዚህ ቅርሳ ቅርሶች በካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ ውስጥ በሚገኙት ስምንት ሙዚየሞች፣ በዕፅዋት ሙዚየም እንዲሁም በዩኒቨርሲቲው ቤተመጻሕፍት እና ስብስቦች እንዳሏቸው እምብዛም በማይታወቁ የዩኒቨርሲቲው ትምህርት ክፍሎች እና ተቋማት ውስጥ ነው የተገኙት።
በቅኝ ግዛት አስተዳዳሪ ከተበረከቱት የማሳይ ጎሳ አባላት የክንድ አንባሮች ጀምሮ፣ በቦር ጦርነት (1899-1902) በማጎሪያ ካምፕ ከተሰበሰቡ ትንንሽ አጥቢ እንስሳት፣ የመካከለኛው ዘመን የአይሁድ የእጅ ጽሑፎች ስብስብ እና የአፍሪካ ሕዝቦችን የሚያሳዩ የመጀመሪያ ፎቶግራፎች ከተገኙት መካከል መሆናቸው ተጠቅሷል።
- በአዲስ አበባ ከታህሳስ ጀምሮ የባንክ አካውንት ለመክፈት የ’ፋይዳ’ መታወቂያ ማቅረብ ግዴታ ሊሆን ነው2 ታህሳስ 2024
- በትግራይ ማኅሌት ተኽላይን አግቶ በመግደል ከተከሰሱት አንደኛው ሞት ተፈረደበትከ 3 ሰአት በፊት
- አርሰናል ከማንቸስተር ዩናይትድ – ማን ያሸንፋል? የእንግሊዝ ፕሪሚየር ሊግ ጨዋታዎች ግምትከ 3 ሰአት በፊት

ከእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ጋር ያለው ግንኙነት
አብዛኞቹ ቅርሶች የተወሰዱት በእንግሊዝ ቅኝ ግዛት ወቅት ነው፤ አንዳንዶቹ በስጦታ የተበረከቱ፣ የተገዙ፣ በቁፋሮ የተገኙ ሲሆኑ፣ ሌሎቹ ደግሞ የተዘረፉ፣ የተወረሱ እና የተመዘበሩ ናቸው።
በዩኒቨርስቲው አርኪዮሎጂ እና አንትሮፖሎጂ ሙዚየም ከጋና የመጣ የወርቅ ሀብል ያለ ሲሆን፣ በሦስተኛው የአንግሎ-አሳንቴ ጦርነት ወቅት፣ በአሳንቴሄኔ ኮፊ ካሪካሪ ቤተ መንግሥት በ1873-4 እንደተዘረፈ ይገመታል።
በተጨማሪም እንግሊዝ በ1897 በአሁኑ ደቡብ ናይጄሪያ በዚያን ጊዜው ቤኒን ሥርወ መንግሥት ለቅጣት በሚል በወሰደችው እርምጃ የተዘረፉ 116 እቃዎች ተገኝተዋል።
ዶ/ር ናሙሶኬ እንዳሉት “በዓለም ዙሪያ ባሉ ብዙ ሙዚየሞች ውስጥ እንደሚታየው ሁሉ በዚህም እንደዚህ ዓይነት ቅርሶችን እንደማገኝ ጠብቄ ነበር” ብለዋል።
“ዩኒቨርሲቲው የዶዶ (እንስሳ) ቅሪተ አካልን ያገኘው በካምብሪጅ ውስጥ በሚገኝ አንድ ሰው እና በሞሪሺየስ ውስጥ ባለው የቅኝ ገዢ አስተዳዳሪ መካከል ባለው ግለሰባዊ ግንኙነት አማካኝነት ነው” ትላለች።
“ከአንትሮፖሎጂ እና የቅኝ ግዛቶች አስተዳደር ጋር ጥምረት አለ፤ ማለትም ተመራማሪዎች ሕዝቡን እና ባህሉን ለማጥናት እና ለመመርመር መግባባት አላቸው።”
ይህንንም በመጥቀስ በ19ኛው ክፍለ ዘመን ይደረጉ የነበሩ ሳይንሳዊ ምርምሮችን ማድረግ እና መረጃ መሰብሰብ ከቅኝ ግዛት ጋር “እጅ ለእጅ ተያይዘው ይሄዱ ነበር” ትላለች።

የአፍሪካውያንን ጉልበት እና ዕውቀትን መግለጥ
የዶ/ር ናሙሶኬ መረጃ እንደሚያሳየው አፍሪካውያን ናሙናዎችን ወይም ቅርሶችን ለመሰብሰብ ስላደረጉት አበርክቶ፣ ስላካፈሉት ክህሎት፣ ዕውቀት በጣም በሚያስቆጭ መልኩ “ጥቂት” ብቻ ተሰንዷል።
“ከ1930ዎቹ ጀምሮ በካሜሩን ስለሆነው የምናገረው አንድ ምሳሌ አለ፤ ይህም ከፍተኛ መጠን ያለው የአፍሪካውያን አቅም የጉልበት ሥራ ላይ መዋሉ ግልጽ ነው” ስትል ተናግራለች።
“ካሜሩናውያን ወንዶች እንስሳትን ተከታትለው በማደን፣ ሸረሪቶችን እና ቀንድ አውጣዎችን ለመሰብሰብ የሙከራ ቱቦዎች ይዘው፣ ለሰዓታት በሆዳቸው ተኝተው አሳልፈዋል።”
“ይህ ሙሉ በሙሉ የአካባቢ ጉልበት እና ዕውቀትን፣ ምሁራዊ፣ አካላዊ እና የፈጠራ ሥራን መጠቀም ነበር። ትኩረት የተደረገው ግን የመሰብሰቡን አድካሚ የጉልበት ሥራ የተወጡት ላይ ሳይሆን በአውሮፓውያን ሳይንቲስቶች ላይ ነው።”

የተገኙትን ቅርሶች በጨረፍታ
- በዩኒቨርሲቲው ስብስቦች ውስጥ ግብፅ በአስር ሺዎች የሚቆጠሩ አርኪዮሎጂያዊ እቃዎች እና የእጅ ጽሑፎች ያላት አፍሪካዊ አገር ነች።
- የአርኪዮሎጂ እና አንትሮፖሎጂ ሙዚየሙ በግምት 137,000 እቃዎች ያሉት ቢሆንም ለዕይታ የቀረቡት ግን ከ 1 በመቶ በታች ናቸው።
- እንዲሁም በ1860ዎቹ የአፍሪካ ሰዎች ቀደምት ምሥሎችን የሚያሳዩትን ጨምሮ ከ29 ሺህ በላይ ፎቶግራፎች ይገኛሉ።
- ወደ 100 ሺህ የሚጠጉ ከአፍሪካ የተወሰዱ ናሙናዎች በሥነ እንስሳት ሙዚየም ውስጥ የተቀመጡ ሲሆን፣ በዚህ ክፍል በጣም በጥቂቱ ጥናት የተደረገባቸው ስብስቦችም ይገኛሉ።
- የዳክዎርዝ ላብራቶሪ ከግብፅ የተወሰዱ 4,800 እና ከሱዳን የተገኙ ደግሞ 1,200 ቅሪተ አካሎች በስሩ ያሉ ቢሆንም 750 ከአፍሪካ የተወሰዱ ቅሪተ አካሎች እንዴት ሊሰበሰቡ እንደቻሉ የሚያሳየው መረጃ በበቂ አልተሰነደም።
ፕሮጀክቱ በካምብሪጅ ዩኒቨርሲቲ የምርምር ተነሳሽነት የሚሠራ ሲሆን፣ ያሉትን ቅርሳ ቅርሶች ከማኅበረሰቦች ጋር ለማስተሳሰር ያለመ ነው።
ከዚህም በተጨማሪ በተለይም ከአፍሪካ ምሁራን እና ማኅበረሰቦች ጋር ተጨማሪ ምርምርን፣ ትብብርን እና ተሳትፎን ለማስተዋወቅ አቅዷል።
“የሚቀጥለው ትልቅ እርምጃ ግን ዕይታን መጨመር እና ስብስቦቹን ራሳቸው አፍሪካውያኑ እንዲመራመሩ መፍቀድ ነው” ብለዋል ዶክተር ናሙሶኬ።