

የኤሌክትሪክ መኪና ቻርጀር ማድረጊያ ቦታ
ማኅበራዊ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ቻርጅ ማድረጊያ በሁሉም ነዳጅ ማደያዎች ሊተከል መሆኑ ተነገረ
ቀን: January 5, 2025
በሁሉም የነዳጅ ማደያዎች ሁለት፣ ሁለት የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎችን ቻርጅ ማድረጊያ እንዲተክሉ ሊደረግ መሆኑን፣ የነዳጅና ኢነርጂ ባለሥልጣን አስታወቀ፡፡
በአገር አቀፍ ደረጃ በሚገኙ በእያንዳንዳቸው ማደያዎች ሁለት ሁለት የኤሌክትሪክ ቻርጅ ማድረጊያ ለመትከል ከኩባንያዎች ጋር መግባባት ላይ መደረሱን የባለሥልጣኑ ዋና ዳይሬክተር ወ/ሮ ሰሃረላ አብዱላሂ ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡
በአገር አቀፍ ደረጃ 2,100 የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ ማድረጊያ ጣቢያዎች ለመትከል መታቀዱን የገለጹት ወ/ሮ ሰሃረላ፣ በእያንዳነዱ የነዳጅ ማደያዎች ቢያንስ ሁለት ሁለት ቻርጅ ማድረጊያ ለመትከል ከነዳጅ ማደያ ኩባንያዎች ጋር መወያየታቸውን አስረድተዋል፡፡
የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ መመርያ ሲዘጋጅ ጎን ለጎን በነዳጅ ማደያዎች ውስጥ ለኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ቻርጅ ማድረጊያ ጣቢያ መሠረተ ልማት ከመገንባት ይልቅ፣ ያለውን ለመጠቀም እንዲያስችል የነዳጅ አከፋፋይ ኩባንያዎችን ማወያየታቸውን ተናግረዋል፡፡
በውይይቱ ከተሳተፉ ማደያዎች መካከል ቶታል፣ ኦይል ሊቪያና ታፍ ኢነርጂ የኤሌክትሪክ ቻርጅ ጣቢያ ለመትከል ስማቸውን ጭምር እንደ አዲስ እየቀየሩ (ሪብራንድ) እንደሚገኙ ገልጸዋል፡፡
እነዚህ ማደያዎች ባላቸው ቦታ ከነዳጅ መቅዳት በተጨማሪ ኤሌክትሪክ ቻርጅ ማድረጊያ እንዲተክሉ መስማማታቸውን፣ በአገሪቱ በተመረጡ ማደያዎቹ በተሠራው መሠረተ ልማት ለመጠቀም የሚያስችሉና በቀላሉ የመንግሥት ፖሊሲን ተፈጻሚ ለማድረግ የሚያመቹ መሆናቸውን ገልጸዋል፡፡
በኢትዮጵያ በአጠቃላይ 1,800 የነዳጅ ማደያዎች እንዳሉ የገለጹት ዋና ዳይሬክተሯ፣ በዋና ዋና ከተሞች በሚገኙ 1,000 ማደያዎች የኤሌክትሪክ ቻርጅ ማድረጊያ ቢተክሉ በአጭር ጊዜ ተደራሽ ማድረግ እንደሚቻል ተናግረዋል፡፡
በዚህ ረገድ የግል ተቋማት ተነሳሽነት እንዳለቸው፣ ነገር ግን ውስንነቶች ስላሉ በሙሉ አቅም ወደ ሥርዓቱ ለመግባት አንዳንድ ሁኔታዎች ምቹ እንዳልሆኑ ገልጸዋል፡፡
የኤሌክትሪክ ቻርጅ ማድረጊያ የነዳጅ ማደያዎች እንዲሠሩ ከባለሥልጣኑ የብቃት ሰርተፊኬት እንዲያገኙ ማድረጉን፣ በሐሳብ ደረጃ አንድ ማደያ ስምንት ቻርጅ ጣቢያ ማድረጊያ እንዲኖው ተብሎ እንደነበር፣ ነገር ግን ወደ ሥርዓት ለማስገባት ሁለት ተሽከርካሪዎች ማድረጊያ ቢኖረው በሚል መነሳታቸውን ተናግረዋል፡፡
አጠቃላይ የኤሌክትሪክ ተሽከርካሪ ማድረጊያ ጣቢያዎች በቅርቡ መገንባት እንደሚጀምሩ፣ ‹‹የነዳጅ አቅራቢ ድርጅት ለአዲስ የነዳጅ ማደያዎች ነዳጅ አላቀርብም›› ያለበት አንዱ ምክንያት የመንግሥትን ፖሊሲ ተፈጻሚ ለማድረግ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
2,100 የኤሌክትሪክ የቻርጅ ማድረጊያ ጣቢያዎች እንደሚያስፈልጉ፣ ለዚህም የራሱን ቦታ ከመስጠት በተጨማሪ ባሉት የነዳጅ ማደያዎች (መሠረተ ልማት) ከሥርዓቱ ጋር እንዲጣጣሙ እየተደረገ ይገኛል ብለዋል፡፡
የመንግሥት የፖሊሲ አቅጣጫ ወደ ኤሌክትሪክ ተሽከርካሪዎች የሚያዘነብል በመሆኑ፣ አዲስ የነዳጅ ማደያ ፈቃድ መስጠት ለጊዜው መቆሙ መገለጹ ይታወሳል፡፡
መንግሥት ካለፈው ዓመት ጀምሮ ‹‹በነዳጅ የሚሠሩ ተሽከርካሪዎችን ወደ አገር ውስጥ እንዳይገቡ›› የሚል ፖሊሲ አቅጣጫ አስቀምጦ የነበረው በቀጣይ ነዳጅን እየቀነሱ መሄድ በሚል መሆኑን ተናግረዋል፡፡
ባለፈው ሳምንት በዓድዋ ሙዚየም ‹የአምስት ዓመት የትራፊክ ደኅንነት ስትራቴጂ ዕቅድ›› በሚል በተዘጋጀው መድረክ፣ የኤሌክትሪክ መኪና ቻርጅ ስቴሽን ጉዳይ ሐሳብ ያነሱት፣ የአዲስ አበባ ከተማ ትራንስፖርት ቢሮ ኃላፊ አቶ ያብባል አዲስ፣ መንግሥት የኤሌክትሪክ ቻርጅ ጣቢያ ሙሉ በሙሉ እንደማያሟላ፣ ይህ ሥራ በይበልጥ ለግል ባለሀብቱ የተተወ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
የግል ባለሀብቶች የቻርጅ ጣቢያ ለመትከል ቦታ ስለሚፈልጉ በመንግሥት በኩል ቦታዎችን እንዲያመቻቹና ለጊዜው ግን በከተማ አስተዳደሩ የቻርጅ ጣቢያ እንዲሆኑ የተመቻቹት በኮሪደር ልማት የተዘጋጁ የመኪና ማቆሚያዎች ላይ መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በእነዚህ ቦታዎች ግለሰቦች ወይም ባለሀብቶች የቻርጅ ጣቢያዎች እንዲሠሩ መፈቀዱን ገልጸው፣ የኤሌክትሪክ መኪና የገዙ የመንግሥት ድርጅቶች ደግሞ በተቋማቸው በኩል ማድረጊያ ጣቢያ›› እያዘጋጁ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡
ግለሰቦች ለሚገዟቸው ተሽከርካሪዎች ደግሞ በራሳቸው (በቤታቸው) ማዘጋጀት አለባቸው ያሉት አቶ ያብባል፣ ቢሮው አተኩሮ የሚሠራው የብዙኃኑን ትራንስፖርት ስለሆነ 100 የኤሌክትሪክ አውቶቡሶች መገዛታቸውን ተናግረዋል፡፡
ለሕዝብ ትራንስፖርት ተብለው የተገዙት አውቶቡሶች ምን ያህል ወጪ ተደረገባቸው ተብለው ለተጠየቁት ጥያቄ ሲመልሱ፣ በጉዳዩ ላይ በዚህ ወቅት መግለጽ እንደማይፈልጉና በጥር ወር የተሽከርካሪዎቹን ጉዳይ ሙሉ መረጃ ለሕዝብ ይፋ እንደሚደረጉ ተናግረዋል፡፡