የመከላከያ አዛዥ የሆኑት ጄነራል ክርስቶፈር ሙሳ በካናዳ መንግሥት ቪዛ ከተከለከሉ ከፍተኛ ወታደራዊ መኮንኖች መካከል አንዱ ናቸው
የምስሉ መግለጫ,የናይጄርያ መከላከያ አዛዥ የሆኑት ጄነራል ክርስቶፈር ሙሳ በካናዳ መንግሥት ቪዛ ከተከለከሉ ከፍተኛ ወታደራዊ መኮንኖች መካከል አንዱ ናቸው

ከ 5 ሰአት በፊት

የናይጄሪያ መንግሥት ካናዳ ለአገሪቱ ጦር አዛዥ እና ለከፍተኛ ወታደራዊ መኮንኖች ቪዛ መከልከሏን አወገዘ።

የመከላከያ ኤታማዦር ሹም ጄኔራል ክሪስቶፈር ሙሳ እንደተናገሩት ረቡዕ ዕለት ለይፋዊ የስራ ጉብኝት በካናዳ መገኘት የነበረባቸው የልኡካን ቡድኑ ግማሾቹ ቪዛ ባለማግኘታቸው መቅረታቸውን ተናግረዋል።

የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትር ኦሉቡንሚ ቱንጂ-ኦጆ የካናዳ ባለስልጣናት የወሰዱትን እርምጃ አውግዘው፣ ለምዕራብ አፍሪካዊቷ አገር “አክብሮት የጎደለው” ሲሉ ጠርተውታል።

በናይጄሪያ የሚገኘው የካናዳ ከፍተኛ ኮሚሽን ጉዳዩን እንደሚያውቅ ገልጾ ነገር ግን በተካተቱት የተወሰኑ ግለሰቦች ዙርያ በ”ግላዊነት ምክንያቶች” ተጨማሪ ዝርዝሮችን ከመስጠት ተቆጥቧል።

ይህ ውሳኔ የተሰማው ካናዳ ለኢሚግሬሽን ሠራተኞች በተወሰኑ ሁኔታዎች ጊዜያዊ የመኖሪያ ሰነዶችን እንዲሰርዙ ግልጽ ስልጣን የሚሰጥ አዲስ ደንቦችን ካወጣች ከሁለት ሳምንታት በኋላ ነው።

ለውጡ የተደረገው የድንበር ደህንነትን ለማጠናከር፣ የቪዛ ፕሮግራሞችን ታማኝነት እና የሕዝብን ደህንነት ለመጠበቅ ያለመ በሚል መሆኑን የካናዳ ባለስልጣናት ገልፀዋል።

ጄኔራል ሙሳ ሐሙስ ዕለት እርሳቸው እና ባልደረቦቻቸው በካናዳ የቀድሞ ወታደሮችን ለማክበር በተዘጋጀ ዝግጅት ላይ እንዲገኙ ቢጋበዙም ቪዛ በመከልከላቸው ምክንያት መቅረታቸውን ተናግረዋል ።

“ከቡድናችን ጋር ተጋብዘን ነበር፤ ነገር ግን ግማሾቻችን ቪዛ ስናገኝ፣ ግማሾቻችን ተከልክለናል፤ በጣም ተስፋ አስቆራጭ ነው” ብለዋል።

ክስተቱን ናይጄሪያ ሉዓላዊነቷን እንድታጠናክር እና “እንደ ቀላል ነገር እንዳትቆጥረው” የሚል “የጥሪ ደወል” መሆኑን ገልጸዋል።

ሐሙስ እለት በዚሁ ዝግጅት ላይ ንግግር ያደረጉት የብሄራዊ ደህንነት አማካሪ ኑሁ ሪባዱ እርምጃው እንዳሳዘናቸው ገልጸው “አክብሮት የጎደለው” ሲሉ ገልጸውታል።

ሪባዱ አክለውም “ናይጄሪያ እንድትሰራ ጠንክረን የምንሰራበት ሌላ ምክንያት ይህ ነው ብለዋል።

አርብ ዕለት በናይጄሪያ ቲቪ ላይ በተደረገ ቃለ ምልልስ ቱንጂ-ኦጆ የካናዳ እርምጃ ፍትሃዊ እንዳልሆነ በመግለጽ የዲፕሎማቲክ ቻናሎችን ማንኛውንም ስጋቶች ለመፍታት ጥቅም ላይ ሊውሉ አለመቻላቸውን ጠቁመዋል።

የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚኒስትሩ “ጦር ኃይል አዛዡ ላይ ይህ ሁኔታ ሊከሰት የሚችል ከሆነ ለአንድ መደበኛ ናይጄሪያ ስጋት ይገባኛል” ብለዋል።

ይኹን እንጂ ጉዳዩ በሁለቱ አገራት መካከል መከባበርን መሰረት ባደረገ ዲፕሎማሲያዊ መንገድ ይፈታል የሚል ተስፋ እንዳላቸው ገልጸዋል።