

ማኅበራዊ የተጋነኑ ማስታወቂያዎች በጤናው ዘርፍ ላይ አደጋ መደቀናቸው ተነገረ
ቀን: February 23, 2025
በተለያዩ ሚዲያዎች የሚሠራጩ የተጋነኑና ነፍስ እናመጣለን ማለት የቀራቸው ማስታወቂያዎች፣ በጤናው ዘርፍ ላይ ከፍተኛ አደጋ መደቀናቸውን የጤና ሚኒስቴር አስታወቀ፡፡
አሳሳቢነታቸው እየጨመረ ያለውና ሕዝቡን የሚያደናግሩ የተጋነኑና እውነት ያልሆኑ ማስታወቂያዎች መንግሥት ባለበት አገር መቆጣጠር ካልተቻለ፣ በማኅበረሰቡ ላይ ከዚህ የባሰ ችግር መፍጠራቸው የማይቀር መሆኑን፣ በጤና ሚኒስቴር የጤናና ጤና ነክ ተቋማትና ባለሙያዎች ቁጥጥር መሪ ሥራ አስፈጻሚ አቶ እንዳልካቸው ፀዳል ተናገሩ፡፡
አቶ እንዳልካቸው ይህንን የተናገሩት የካቲት 13 ቀን 2017 ዓ.ም. የጤና ሚኒስቴር በጤና ነክ ተቋማትና በባለሙያዎች ላይ የሚደረጉ ቁጥጥሮችን፣ ለባለድርሻ አካላት በቢሾፍቱ ከተማ በተዘጋጀ የግንዛቤ ማስጨበጫ መድረክ ነው፡፡
በውይይት መድረኩ የኢትዮጵያ መገናኛ ብዙኃን ባለሥልጣን የፍትሕ ሚኒስቴርና ሌሎች ባለድርሻ አካላት የተገኙ ሲሆን፣ በሐሰተኛ ማስታወቂያዎች ነፍስ እናመጣለን በቀረው ልፈፋ፣ ኅብረተሰቡ እየተጭበረበረና ገንዘቡን ጭምር እየተዘረፈ መሆኑ ተጠቅሷል፡፡
በጤና ግብዓትም ሆነ አገልግሎት ላይ በአገር ደረጃ የሕግ ክፍተት አለመኖሩን የተናገሩት አቶ እንዳልካቸው፣ ነገር ግን በተለይ ወደ ታችኛው ማኅበረሰብ ሲኬድ የአፈጻጸም ችግሮች ጎልተው እንደሚታዩ ገልጸዋል፡፡
ተቋማት በተሰጣቸው የሥልጣን ዕርከን ተገዥ ሆነው አለመሥራት አንዱ የቁጥጥር ክፍተት ነው ያሉት አቶ እንዳልካቸው፣ የተጋነኑና ከእውነት የራቁ ማስታወቂያዎች ከፍተኛ ችግር እየፈጠሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
አንዳንድ ባለሙያዎች በማኅበራዊ ሚዲያ ‹‹እኔ ነኝ የተሻልኩ›› ብለው የሚያቀርቡት መረጃ በጤናው ዘርፍ ላይ ትልቅ ሥጋት ፈጥሯል ያሉት መሪ ሥራ አስፈጻሚው፣ ያለ ምንም ተጨባጭ ማስረጃ ሌሎች ባለሙያዎችን ማጥላላትና መሰል ችግሮች ማኅበረሰቡን መጉዳታቸው አይቀርም ሲሉ ተደምጠዋል፡፡
‹‹ሚዲያው በእኛ ሥር ስላልሆነ ለቁጥጥርና ለክትልል አስቸግሮናል፤›› ያሉት አቶ እንዳልካቸው፣ ሚዲያውን የሚቆጣጠሩ አካላት የሚያሠራጯቸውን ማስታወቂያዎች በአግባቡ ሊከታተሉና ሊቆጣጠሩ እንደሚገባ አሳስበዋል፡፡
የመረጃ አቅርቦት አማራጮች በመበራከታቸው ምክንያት በግለሰቦችም ሆነ በተቋም ደረጃ የሚደርሱ መረጃዎች ለማኅበረሰቡ መልካም ሆነው ሳለ፣ ነገር ግን የመረጃ ፍሰቱ የተለያዩ ተግዳሮቶችን ይዞ መምጣቱን የተናገሩት ደግሞ የጤና ሚኒስትር ደኤታ አየለ ተሾመ (ዶ/ር) ናቸው፡፡
በጤና ዘርፍ የሚቀርቡ መረጃዎች ብዙ ማስረጃዎችና የማጣሪያ ደረጃዎችን አልፈው መቅረብ ሲገባቸው ለማኅበረሰቡ ትክክል ያልሆኑ፣ ግራ የሚያጋቡና እርስ በርሳቸው የሚጋጩ መረጃዎችን እያደረሱ መሆኑን አየለ (ዶ/ር) አክለዋል፡፡
የጤና መረጃ እንደ ሌላው የንግድ ሥርዓት ከቁጥጥር ውጪ ሆኖ ሊሄድ አይችልም ያሉት ሚኒስትር ደኤታው፣ የሚሰጡት መረጃዎች አጠራጣሪ ከሆኑ ስህተት ስለሚፈጥሩ ከወዲሁ ሊታረሙ እንደሚገባ ጠቁመዋል፡፡
የሚዲያ ባለሙያዎችም የጤና መረጃዎችን ለማኅበረሰቡ ሲያቀርቡ የሚቀርበውንና የማይቀርበውን ከመለየት ባሻገር፣ ስለሚቀርበው መረጃ ከሚመለከተው አካላት ጋር በመሆን ተዓማኒነቱንና ትክክለኛነቱን ማረጋገጥ እንዳለባቸውና ሁሉም ባለድርሻ አካላት ኃላፊነታቸውን እንዲወጡ ጥሪ አቅርበዋል፡፡
‹‹መረጃዎችን ለማድረስ ባለሙያ መሆን ብቻ በቂ አይደለም፤›› ያሉት አየለ (ዶ/ር)፣ መረጃ ሰጪው ለሚፈጠረው ችግርም ኃላፊነትን መውሰድ የሚችል መሆን አለበት ብለዋል፡፡
የማይድኑ በሽታዎችን ‹‹እናድናለን፣ እንፈውሳለን›› የሚሉ ራሳቸውን ከሌሎች የተለየ ብቃትና ክህሎት እንዳላቸው በማስመሰል በማኅበረሰቡ ውስጥ ውዥንብር የሚፈጥሩ አካላት ተበራክተዋል ያሉት ሚኒስትር ደኤታው፣ ተገልጋዮችን ለአላስፈላጊ ወጪና ጉዳት የሚዳርጉ በመሆናቸው በሕግና በማዕቀፍ ሊመሩ እንደሚገባ አብራርተዋል፡፡
በተለይ ካለፉት ጥቂት ወራት ወዲህ ብዙ አዳዲስ ልምዶች መስተዋላቸውን የተናገሩት አየለ (ዶ/ር)፣ ቲክቶክ በተባለው ማኅበራዊ የሚዲያ አውታር በርካታ ባለሙያዎች የተለያዩ መረጃዎችን ለማኅበረሰቡ እያደረሱ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
የሚሰጡት መረጃ የተገልጋይን መብትና ግዴታ ያላከበረና ተገልጋዩን ለገበያ የሚያውሉ ሕገወጥ ተግባራትን የሚያባብሱ ልምዶች መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡ በዘርፉ የሚታዩ ችግሮችን በአንድ ጊዜ ለመቆጣጠር መሞከር ለጤናው ዘርፍ ከፍተኛ ፈተና የሚደቅን በመሆኑ፣ በሒደት በማስተማርና በማሻሻል ሚዛኑን የጠበቀ ቁጥጥር ለማድረግ የባለድርሻ አካላት ዕገዛ እንደሚያስፈልግ አየለ (ዶ/ር) አክለዋል፡፡
‹‹ቀደም ሲል የጤና ሥርዓቱን እየፈተነው የነበረው የመረጃ እጥረት ነበር፤›› ያሉት ሚኒስትር ደኤታው፣ በአሁኑ ወቅት ደግሞ መረጃዎች ከአቅም በላይ እየሆኑ ተዓማኒነታቸው ያልተረጋገጠ ስለሚሆን፣ በቀጣይ ችግሩን የሚቃኝና ከመረጃ ሥርዓቱ እስከ አገልግሎት አሰጣጡ የሚያሻሽል፣ እንዲሁም ተጠያቂነት የሚያሰፍን መመርያ እየተዘጋጀ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡
ግለሰቦች ሚዲያ በመጠቀም በባህላዊም ሆነ በሃይማኖታዊ መንገድ ታማሚዎች የጀመሩትን መድኃኒት እንዲያቆሙና እንዲሞቱ፣ እንዲሁም ቤተሰብ እንዲበተን እያደረጉ እንደሆነ የተናገሩት አየለ (ዶ/ር)፣ ይህ ከባድ ወንጀል መሆኑን ማወቅ ይኖርባቸዋል ብለዋል፡፡
ከዚህ ባሻገር አንዳንድ የጤና ተቋማት የሌላቸውን የሕክምና መሣሪያ እንዳላቸው በማስመሰል ሚዲያውን ተጠቅመው ተገልጋዮችን የማታለልና የማጭበርበር ድርጊት እንደሚፈጽሙ ጠቁመዋል፡፡
ይህንንና መሰል ተግባራትን ሲያከናውኑ የተገኙ የጤና ተቋማት የማሸግና ከሥራ የማገድ ቅጣት እንደተጣለባቸው አየለ (ዶ/ር) ገልጸዋል፡፡