ፍልስጤማውያን የታሰሩ ቤተሰቦቻቻውን መፈታት ዜና እየተጠባበቁ

ከ 5 ሰአት በፊት

እስራኤል ከ600 የሚበልጡ የፍልስጤም እስረኞችን መፈታት ላልተወሰነ ጊዜ ማዘግየቷን መግለጿን ተከትሎ፣ የተኩስ አቁም ሂደት ውስጥ ሌላ እንቅፋት ፈጥሯል።

እስራኤል ይህን ያለቸው እ.አ.አ ጥቅምት 7/2023 በሃማስ ጥቃት ታግተው የተወሰዱ አራት ሰዎችን ጨምሮ ስድስት የእስራኤል ታጋቾች ቅዳሜ ዕለት ከተለቀቁ በኋላ ነው።

የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ፣ ሃማስ ቀጣይ የታገቱት እስረኞችን እንደሚለቅ ዋስትና እስኪሰጥ ድረስ የፍልስጤም እስረኞችን መልቀቅ ይዘገያል ብለዋል።

በመጀመርያው የተኩስ አቁም ስምምነት አንድ ተጨማሪ የታጋቾች ርክክብ ይቀራል፤ ይህም በእገታ ላይ ሳሉ ከሞቱት እስራኤላውያን መካከል አራቱን ያካትታል።

በሁለተኛው ምዕራፍ የተኩስ አቁም ስምምነት ለሚካሄደው ሌሎች ታጋቾችን ማስለቀቅ ምንም ዝግጅት አልተደረገም።

አደራዳሪዎች ስምምነቱን ወደ ትክክለኛው መንገድ ለመመለስ እና የተኩስ አቁም ስምምነቱን ለመታደግ ቀን ተሌት ይሰራሉ።

ኔታንያሁ “ታጋቾቹን ለፕሮፓጋንዳ ዓላማ ማዋልን ጨምሮ” ሃማስን “በተደጋጋሚ የመብት ጥሰት” በመፈጸም ይከስሳሉ።

የኔታንያሁ መግለጫ የወጣው በኖቫ የሙዚቃ ፌስቲቫል ላይ ታግተው የነበሩት አራት ታጋቾች – ታል ሾሃም፣ ኦመር ሸም ቶቭ፣ ኢሊያ ኮሄን እና ኦመር ዌንከርት – ቅዳሜ እለት ከተለቀቁ በኋላ ነው።

የተፈቱት ሁለቱ ሌሎች ታጋቾች አቬራ መንግስቱ እና ሂሻም አል ሰይድ በጋዛ ለዓመታት ቆይተዋል። አቬራ መንግስቱ እ.አ.አ ከ2014 እና ሻሂም አል ሰይድ ደግሞ እ.አ.አ ከ2015 ጀምሮ ታግተዋል።

ስድስቱ የእስራኤል ታጋቾች በመጪው ቅዳሜ ይጠናቀቃል ተብሎ በተዘጋጀው የተኩስ አቁም ስምምነት የመጀመሪያ ምዕራፍ አካል ሆነው በሕይወት የሚመለሱት የመጨረሻ ታጋቾች ናቸው።

አቬራ መንግስቱ ከቤተሰቡ ጋር ሲቀላቀል

Skip podcast promotion and continue reading

የቢቢሲ አማርኛ ዋትስአፕ ቻናል

የቢቢሲ አማርኛ ዋትስአፕ ቻናል

ዜና፣ ትንታኔ እና ታሪኮችን በቀጥታ በዋትስአፕ ለማግኘት

ይህን በመጫን የቻናላችን አባል ይሁኑ!

End of podcast promotion

ይህ በእንዲህ እንዳለ በእስራኤል ቁጥጥር ስር ባለው ዌስት ባንክ ከኦፈር እስር ቤት ውጭ፣ ቤተሰብ እና ወዳጆች የፍልስጤም እስረኞች እስኪፈቱ ድረስ ሲጠብቁ ነበር።

በጋዛ ካን ዮኒስ የሚኖሩ የ80 ዓመት አዛውንት እናት፣ ልጃቸው ከ33 ዓመታት እስራት በኋላ ነፃ እንደሚወጣ “ማመን አልችልም” ሲሉ ለኤኤፍፒ የዜና ወኪል ተናግረዋል።

ማምሻውን ላይ ሃማስ እስራኤል እስረኞችን መፍታትን አዘግይታለች በማለት ስምምነቱን ጥሳለች ሲል ከስሷል።

ለኔታንያሁ መግለጫ ከሃማስ የተሰጠ ምላሽ የለም።

የፍልስጤም ባለስልጣናት እንደሚሉት፣ ከእስር ሊፈቱ ከነበሩት እስረኞች 50ዎቹ የዕድሜ ልክ እስራት፣ 60ዎቹ ረጅም እስራት የተፈረደባቸው እና 445ቱ በእስራኤል ከጥቅምት 7 ጀምሮ የታሰሩ ናቸው።

እ.ኤ.አ. ጥቅምት 7 2023 በሃማስ ቁጥጥር ስር ያሉ 62 ታጋቾች አሉ፤ ከእነዚህም ውስጥ ግማሽ ያህሉ በህይወት እንዳሉ ይታመናል።

በእስራኤል እና በሐማስ መካከል በተደረገው የሦስት ምዕራፍ የተኩስ አቁም በሚቀጥለው በመጋቢት 1 በሚጀምረው ምዕራፍ ተጨማሪ ታጋቾች ሊለቀቁ ተዘጋጅተዋል።

ሃማስ የተኩስ አቁም ስምምነት ጥር 19 ቀን ተግባራዊ ከሆነ በኋላ በፍልስጤም እስረኞች ምትክ በቀይ መስቀል አመቻችነት ታጋቾችን መልቀቅ ጀመሯል።

ቅዳሜ እለት፣ የ40 አመቱ ታል ሾሃም እና የ39 አመቱ አቬራ መንግስቱ ወደ እስራኤል መከላከያ ሰራዊት (አይዲኤፍ) ከመዛወራቸው በፊት በደቡብ ጋዛ ራፋህ ወደሚገኘው ቀይ መስቀል ተላልፈዋል።

ሚስተር ሾሃም እ.ኤ.አ. በጥቅምት 2023 በኪቡዝ ቢኤሪ ቤተሰቡን እየጎበኘ ሳለ እሱ እና ሌሎች ሚስቱን እና ሁለት ልጆቹን ጨምሮ በሀማስ ታግተዋል።

የተያዙት የቤተሰቡ አባላት ከ50 ቀናት በኋላ ተለቅቀዋል።

በመግለጫው ላይ ቤተሰቦቹ “ይህ የማይረሳ ጊዜ ነው፣ ሁሉም ስሜቶች በፍጥነት የሚቀላቀሉበት፣ የእኛ ታል ከእኛ ጋር ነው” ብለዋል።

ኢትዮጵያዊ-እስራኤላዊው አቶ አቬራ መንግስቱ እ.አ.አ 2014 ጀምሮ ወደ ሰሜናዊ ጋዛ ከተሻገረ በኋላ በሃማስ በእስር ላይ ነበር።

ሂሻም አል ሰይድ ከእስር የተፈታው ቅዳሜ ዕለት በጋዛ ከተማ ውስጥ ነው።

ቤተሰቦቹ በመግለጫቸው “ሂሻም ወደ እኛ እንዲመለስ ለአስር አመታት ከተካሄደው ትግል በኋላ በጉጉት የሚጠበቀው ጊዜ ደርሷል” ብለዋል።

“በእነዚህ ቀናት ሂሻምን እና እራሳችንን መንከባከብ እንድንጀምር ለሂሻም እና ለመላው ቤተሰብ ግላዊነት እንፈልጋለን።”

በማዕከላዊ ጋዛ ኑሴይራት፣ የ22 ዓመቱ ሻም ቶቭ፣ የ27 ዓመቱ ኮኸን እና የ23 ዓመቱ ዌንከርት ከእስር ተፈትተዋል።

ሶስቱም በኖቫ የሙዚቃ ፌስቲቫል ላይ የታገቱ ናቸው።

ሼም ቶቭ የሐማስ ተዋጊዎች በበዓሉ ላይ ሲወርዱ መጀመሪያ በመኪና አምልጦ የነበረ ቢሆንም፣ ነገር ግን ጓደኞቹን ለማዳን ተመልሶ በሄደበት ጊዜ ተይዟል።

ኮኸን በበዓሉ ላይ ከሴት ጓደኛው ዚቭ አቡድ ጋር በአንድ መጠለያ ውስጥ ተደብቆ ነበር፣ ነገር ግን ተገኝቶ ታገተ። መጠለያው በቦምብ ቢደበደብም፣ ዚቩ አቡድ ግን ተርፋ አመለጠች።

ዌንከርት በበዓል ታዳሚዎች ላይ ጥቃት ሲሰነዘርባቸው ወደ ቤተሰቡ የጽሑፍ መልእክት መላክ ችሏል፤ ደህንነቱ ወደተጠበቀ መጠለያ እንደሚሄድ የነገራቸው ቢሆንም ግንኙነታቸው ተቋርጧል።

በቴል አቪቭ የታጋቾች አደባባይ የተሰበሰበው ሕዝብ የተለቀቁትን በቀጥታ ስርጭት ሲመለከት በደስታ ተቀብሏቸዋል።

ስድስቱ ሰዎች መመለሳቸውን ያከበሩ ቤተሰቦች የቀሩት ታጋቾች በሙሉ እንዲፈቱ ጠይቀዋል።

የሾሃም ቤተሰብ “የእኛ ብቸኛ ጥያቄ ይህንን እድል ተጠቅመን ስምምነትን… ሁሉንም ታጋቾች ወደ ቤታቸው መመለስ ነው።”

ከቀሪዎቹ ታጋቾች መካከል በጥቅምት 7 የተማረኩት የ21 ዓመቱ እስራኤላዊ-አሜሪካዊ ወታደር ኤዳን አሌክሳንደር ይገኙበታል።

የቅዳሜውን ታጋቾች ሲፈቱ የተመለከቱት እናቱ ያኤል አሌክሳንደር ለቢቢሲ እንደተናገሩት ሲፈቱ ማየት አስደናቂ ነገር ቢሆንም ለቤተሰቡ ግን መጠበቅ በጣም ከባድ ነው።

“እንደ ልጄ በሕይወት ያሉ ከደርዘን በላይ ወጣቶች አሁንም ለመፈታት በመጠባበቅ ላይ ይገኛሉ” ብለዋል። “አሁን ዋናው ግብ በሕይወት ያሉ ሰዎችን ከጋዛ ማስለቀቅ ነው”

የቅዳሜው አስደሳች ትዕይንቶች በዚህ ሳምንት መጀመሪያ ላይ፣ የታጋቾቹ ሺሪ ቢባስ አስከሬን፣ የሁለቱ ወጣት ልጆቿ እና የሌላ እስረኛ ኦዴድ ሊፍሺትዝ ወደ እስራኤል ከተመለሱበት ጊዜ ጋር ተቃራኒ ነበር።

እ.ኤ.አ. በጥቅምት 7 2023 በሃማስ ጥቃት 1,200 ሰዎች – በአብዛኛው ሲቪሎች – ተገድለዋል እና ሌሎች 251 ሌሎች ደግሞ ታግተው ወደ ጋዛ ተወስደዋል።

እስራኤል በምላሹ በሃማስ ላይ መጠነ ሰፊ ወታደራዊ ዘመቻ የከፈተች ሲሆን ይህም ቢያንስ 48,319 ፍልስጤማውያን በተለይ ሲቪሎች መገደላቸውን በሃማስ የሚመራ የጤና ጥበቃ ሚኒስቴር ገልጿል።