የኤፍቢአይ ቢሮ

ከ 3 ሰአት በፊት

የአሜሪካ ቁልፍ መስሪያ ቤቶች ቱጃሩ ኤለን መስክ ሳምንታዊ ስኬታችሁን ላኩልኝ በሚል ለጠየቀው ጥያቄ ሰራተኞቻቸው ምላሽ ከመስጠት እንዲቆጠቡ አዘዙ።

ኤለን መስክ ወጪ መቆጠብ በሚል ጅማሮ በተለያየ መስሪያ ተቀጥረው ያሉ ሰራተኞች ሳምንታዊ ስኬታቸውን በዝርዝር እንዲልኩለት ጠይቋል።

ምላሽ አትስጡ የሚል ትዕዛዝ ካስተላለፉት መካከል የፌደራል ምርመራ ቢሮ (ኤፍቢአይ)፣ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር እና ፔንታጎን ይገኙበታል።

ሌሎች የመስሪያ ቤት ኃላፊዎች ከመስክ ለተላከው ኢሜይል ምላሽ እንዲሰጡ የመከሩ ሲሆን ሌሎች ደግሞ ምላሽ ከመስጠታቸው በፊት ተጨማሪ መመሪያ እንዲጠብቁ ተነግሯቸዋል።

መስክ ሰራተኞች እስከ ሰኞ እኩለ ሌሊት ድረስ ምላሽ ካልሰጡ እንደለቀቁ ይቆጠራል ሲል አስጠንቅቋል።

ኤለን መስክ ቅዳሜ ምሽት በሚሊዮን ለሚቆጠሩ የፌደራሉ ሰራተኞች ኢሜይል ከመላኩ በፊት “ባለፈው ሳምንት ያከናወኗችኋቸውን ተግባራት እንዲገልጹ የሚጠይቅ ኢሜይል ይደርሳችል” የሚል መልዕክት በኤክስ ገጹ አስፍሮ ነበር።

የአሜሪካው ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ መስክ በላከው ኢሜይል የሰጡት ምላሽ የለም።

ቢቢሲ በደረሰው የኢሜይል ግልባጭ ሰራተኞች ሚስጥራዊ መረጃዎችን ይፋ ሳያደርጉ ባለፈው ሳምንት ያከኗወኗቸውን ዋና ዋና ተግባራት በአምስት ነጥቦች እንዲዘረዝሩ ተጠይቀዋል።

የፌደራል መንግሥት የሰራተኞች አስተዳደር ቢሮ የኢሜይሉን ትክክለኛነት አረጋግጧል።

የተላከው ኢሜይል ሰራተኞች ምላሽ አንሰጥም ቢሉ ስራቸው ምን ይሆናል በሚለው ላይ ግልጽ ነገር ባይዝም መስክ “ምላሽ አለመስጠት ስራ እንደለቀቃችሁ ያስቆጥራል” በሚል ማህበራዊ ሚዲያ ገጹ ላይ አስፍሯል።

አዲስ የተሾሙት የኤፍቢአይ ዳይሬክተር ካሽ ፓቴል ሰራተኞቻቸው “ምላሽ ከመስጠት እንዲታቀቡ” በኢሜይል መልዕክታቸው አሳስበዋል።

“የኤፍቢአይ ሰራተኞች ከመንግሥት ሰራተኞች አስተዳደር ቢሮ መረጃዎችን የሚጠይቅ ኢሜይል ደርሷችሁ ይሆናል” ማለታቸውን ሲቢኤስ ያጋራው የፓቴል መልዕክት ያትታል።

“ኤፍቢአይ በዳይሬክተሩ በኩል ሁሉንም የግምገማ ሂደቶቻችንን ይቆጣጠራል። እናም የመስሪያ ቤታችን መመሪያ ተከትለን ግምገማ እናካሂዳለን ይላል።

የውጭ ጉዳይ መስሪያ ቤትም ተመሳሳይ መልዕክት የላከ ሲሆን አመራሩ ምላሽ ይሰጣል ብሏል።

“ማንኛውም ሰራተኛ ተግባራቸውን በተመለከተ ከመስሪያ ቤቱ የትዕዛዝ ሰንሰለት ውጭ ሪፖርት የማድረግ ግዴታ የለበትም” ሲል የመስሪያ ቤቱ ጊዜያዊ ጸሐፉ ቲቦር ናጊ በላኩት መልዕክት አስፍረዋል።

ፔንታጎን በበኩሉ “አስፈላጊ በሚሆንበት ወቅት መስሪያ ቤቱ ምላሽ የሚሰጥ ይሆናል” ሲል ለሰራተኞቹ በላከው ኢሜይል አስፍሯል።

የሃገር ውስጥ ደህንነት መምሪያ እና የፌደራል ድንገተኛ አደጋዎች መከላከል ኤጀንሲ ለሰራተኞቻቸው ተመሳሰይ መመሪያ መስጠታቸውን ዘገባዎች ጠቁመዋል።