ንጎንግ ሮድ

14 መጋቢት 2025, 14:44 EAT

በናይሮቢ መንገድ ላይ እየተጓዘ የነበረ የዩናይትድ ኪንግደም ዜጋ በኬንያው ፕሬዝዳንት ዊልያም ሩቶ አጃቢዎች ተገጭቶ መገደሉ ተገለጸ።

ኤድጋር ቻርልስ ፍሬድሪክ የተባለው የ79 ዓመት ግለሰብ ሐሙስ ዕለት ንጎንግ ሮድ የተባለ አካባቢ ተገጭቶ ነው ሕይወቱ ያለፈው።

አንድ አሽከርካሪ በፖሊስ ተይዞ የነበረ ቢሆንም በዋስ ተለቋል።

የፕሬዝዳንት ሩቶን መኪና አጅበው ሲጓዙ ከነበሩ ተሽከርካሪዎች አንዱን እየነዳ እንደነበር ተገልጿል።

የፖሊስ ቃል አቀባይ ማይክል ሙቺሪ እንዳሉት፣ የሞተው ግለሰብ ኬንያ የምትኖር እህቱንና የእህቱን ልጅ ሊጠይቅ ነበር ወደ ናይሮቢ የተጓዘው።

ሕልፈቱ ለቤተሰቦቹ የተገለጸ ሲሆን፣ የአስከሬን ምርመራም ይደረጋል።

ሰውየው ከተገጩ በኋላ አሽከርካሪውን ያላቆመው ሹፌር ከምርመራ በኋላ ፍርድ ቤት ይቀርባል ተብሏል።

በኬንያ የዩኬ ከፍተኛ ኮሚሽን ባለሥልጣን ስለ ጉዳዩ እንደሚያውቁ ተናግረዋል።

በማኅበራዊ ሚዲያ ላይ የታዩ ተንቀሳቃሽ ምሥሎች ሰማያዊ ጅንስ ሱሪና ካናቴራ ያደረገ ሰው መንገድ ላይ ወድቆና በደም ተነክሮ ያሳያሉ።

ሌሎች ምሥሎች ደግሞ ግለሰቡ በባህላዊው የኬንያ ልብስ ማሳይ ሹካ ሰውነቱ ተሸፍኖ ያሳያሉ።

የገጨው መኪና የከተማ መስተዳድሩ ንብረት እንደሆነ የፖሊስ ቃል አቀባዩ ተናግረዋል።

ፕሬዝዳንት ሩቶ በአካባቢው የሥራ ጉብኝት እያደረጉ ነበር።