
March 7, 2025
ቀን የካቲት 2017
በአንዳርጋቸው ጽጌ
- ከአጻጻፍና ከይዘት ጋር የተያያዙ ጉዳዮች

ሀ) የቅርጽ ጉዳይ
የማንበብ ባህል እየተዳከመ መጥቷል። በመሆኑም ሰፊ ትንታኔ የሚጠይቁ ጉዳዮችን በአጭሩ ጨምቆ ማቅረብ እንደሚያስፈልግ ተረድቻለሁ። የአማራ ህዝብ የሚገኝበት ሃገረ ኢትዮጵያና፣ ሃገረ ኢትዮጵያ የምትገኝበት ቀጠና ከየትኛው አካባቢ የበለጠ የተወሳሰቡ ዘርፈ ብዙ የሆኑ ችግሮች ያሉበት ነው። በዛ ላይ እየተወሳሰበ የመጣው የቅርብና የሩቅ መንግስታትና ሃገራት እንዲሁም የአለም አቀፍ ኩባንያዎች ጂኦ ፖለቲካዊና ኢኮኖሚያዊ ፍላጎት የቀጠናውን ችግር በማባባስ የሚጫወተው ሚና አለ። እንዲህ አይነት የተወሳሰቡ ሃገራዊ፣ ቀጠናዊና አለምአቀፋዊ ተጽእኖዎች ባሉበት አካባቢ የአማራ ህዝብ የሚያደርገውን የህልውና ትግል በሚገባ ለመተንተን እንኳን ረጃጃም ጽሁፎች አይደለም የዳጎሱ መጽሃፍትም ቅም የሚሉት አይደለም።
ችግሩ ግን በሚገባ ያልተማረው ብቻ ሳይሆን የተማረ የምንለውም፣ መጽሃፍ አይደለም ረጃጃም ጽሁፎችን ማንበብ ካቆመ ቆይቷል። ቀደም ብሎም ቢሆን ማንበብ መጻፍ የማይሆንለት የኢትዮጵያ ሆነ የአማራ ምሁር፣ እድሜ ለማህበራዊ ሚድያ መጻፉንም ማንበቡን እርግፍ አድርጎ ትቶታል።
ምሁሩ ሳይቀር ከሙያው ውጭ የቀረችውን የማወቅ ፍላጎት የሚያረካው ዘመን ያመጣቸውን የተግባቦት መሳሪያዎች ከድንቁርና በመጣ ድፍረት ተቆጣጥረው ያሻቸውን የሚናገሩበትን የዩትዩብ፣ የቲክቶክ የትዊተር፣ የፊስቡክና የኢንስተግራም ሸቃጮችን በማዳመጥ ሆኗል። ይህ ሁኔታ፣ እጅግ አደገኛ የሆነ ከእውቀት የተጣላ በስሜት የሚነዳ፣ የግብስብስ መረጃዎች ሱሰኛ (የጃንክ መረጃዎች ጃንኪ a junkie for junk information ) ፈጥሯል። ይህን ባህል ግምት ውስጥ በማስገባትና ፈረንጆቹ “ለአሮጌ ውሻ አዲስ ትሪክ ማስተማር አይቻልም” የሚሉትንም ብሂል በመጋፋት እኔም በተቻለ መጠን የወቅቱን የአማራ ህዝብ የህልውና አደጋ ምልከታዎቼን የራሳቸው አርስት ባላቸው አጫጭር ጽሁፎች አማካይነት ለማቅረብ ተገድጃለሁ።
ለ) ጽሁፍ ለማን የተጻፈ ነው?
ይህ ጽሁፍ የተጻፈው በአማሮች መሃከል መደረግ ለሚገባው ውይይት ነው። የታሪክና የግል ህይወት ምጸት በሚመስል መልኩ እነዚህን ቃላቶች የዛሬ 32 አመት “ የአማራ ህዝብ ከየት ወዴት” በሚል ርእስ ባሳተምኳት ትንሽ መጣጥፍ ውስጥ መገኘታቸው አስገርሞኛል። በገጽ 5 መጨረሻ ላይ” የዚህ ጽሁፍ አላማ አንድና አንድ ብቻ ነው። ዛሬ በሃገራችን ውስጥ ባለው ሁኔታ በተለይም የአማራውን ህዝብ በሚመለከቱ ጉዳዮች ላይ በአማራውና በአማራው ውስጥ ብቻ መደረግ ላላበት ውይይት የራሳችንን መንደርደሪያ ሃሳቦች ለማቅረብ ነው” ይላል። በዚህ ጽሁፍ ላይ አማራ ያልሆኑ አስተያየት ቢሰጡበት ማስቆም አይቻልም። በበኩሌ ከጽሁፉ ጋር በተያያዘ የሚነሱ ጥያቄዎች እና አስተያየቶች ካሉ ምላሽ የምሰጠው ከአማሮች ለሚመጡት ብቻ ነው።
አማሮች ስል በአማራ ፋኖ የሚመራው የአማራን የህልውና ትግል ፍትሃዊ ነው ብሎ የሚያምን ማንኛውም ሰው ማለቴ ነው። እንዲህ ከሆነ ማኛውም ኢትዮጵያዊ የአማራን የህልውና ትግል ፍትሃዊነት ከተቀበለ አማራ ነው። የአማራ ቁስል ቁስሌ፣ ህመሙ ህመሜ ነው በማለት በድርጊቱ እኔም አማራ ነኝ እያለን ስለሆነ። እንዲህ አይነቱ ግለሰብ ጥያቄ ቢጠይቀኝ ለመመለስ ቢሞግተኝ ለመሞገት ዝግጁ ነኝ። ከዚህ ውጭ አንድ ግለሰብ ዘርማንዘሩ እስከምንጅላቱ አማራ መሆኑን ሊቆጥር ይችላል። በድርጊት ግን እንደ ዳንኤል ክብረት፣ ዳኛቸው አሰፋ፣ በለጠ ሞላ፣ አረጋ ከበደ፣ ተመስገን ጥሩነህ፣ አገኘሁ ተሻገር፣ ብናልፍ አንዱ አለም እና ሌሎችም የንጉስ አብይ አህመድ የቤተ መንግስት ባሪያ ሆኖ እስከመጣ ድረስ አማራ ሊሆን አይችልም። በእንዲህ አይነቱ ፍጥረት ለመጠየቅም ወይም ለመሞገትም ፈቃደኛ አይደለሁም።
ንጉስ አብይ ባቋቋማቸው፣ ለሆዳቸው ባደሩ ባሪያ የሚድያ ጄነራሎቹም በሚመሩ የማህበራዊ ሚድያዎችና ሰራዊቶቻቸውም ለመጠይቅ ፈቃደኛ አይደለሁም። ይህ ጽሁፍ በዋንኛነት ማንን ቀንድ ሊያስበቅል እንደሚችል ሰለማውቅ የኦሮሞ ብልጽግና የሚድያ ሰራዊት እና ጸረ አማራና ኢትዮጵያ ሃይሎች የአማራ ስም እየተጠቅሙ ዘመቻ እንደሚከፍቱበት ግልጽ ነው።
እንደተለመደው የኢትዮጵያ ህዝብ በተለይ ደግሞ የአማራ ህዝብ “ደሃ እንጂ ደደብ አይደለም” በሚል የህዝብ መተማመን ላይ ቆሜ እውነትን በድፍረት መጻፍ ግድ የሚል ሆኖ አግኝቸዋለሁ ።
በበኩሌ የዚህን ጽሁፍ ጉዳይ “በአማሮችና በአማራ ወዳጆች መሃል ለሚደረግ ውይይት” በሚል ያጠርኩት ከማንም ለሚነሳ ማናቸውም ጥያቄ ወይም አስተያየት ምላሹን መስጠት ወይም ሃሳቡን ማስተናገድ ከባድ ስለሆነ አይደለም። ያለንበት አዋካቢና አሰቃቂ ሁኔታ የሚያቀናጣ የትኩረትና የጊዜ የተትረፈረፉ እድሎች ስለማይሰጠን ብቻ ነው።
የሚገርመውና አሁንም የታሪክና የግል ህይወት ምጸት ይመስል፣ ቀደም ብዬ በጠቀስኳት መጣጥፍ ላይ የዛሬ 32 አመት፣ የአማራ ህዝብ ወከባ ውስጥ መሆኑን፣ በፍጥነት መንቀሳቅስ እንዳለብን የሚገልጽ ቃላቶች መጠቀሜ ራሴን አስገርሞኛል። ያች ትንሽ መጣጥፍ እዛው ገጽ 5 ላይ “የአማራ ህዝብ ……… ራሱን በፍጥነት ማዘጋጀት ካልቻለ፣ ይህ ህዝብ በሚሊዮኖች በረሃብ የሚረግፉበት፣ በሚሊዮኖች የሚሰደድብት፣ እንደ ህዝብ ክብሩ፣ ነጻነቱና ህልውናው ከማይጠበቅበት ሁኔታ ውስጥ እንደሚገባ መጠራጠር አይኖርብንም” ብላ ነበር። ህልውና የምትለውን ቃል ልብ በሏት።
አሁንም ልክ እንደ ዛሬ 32 አመቱ የአማራ ህዝብና ከዚህ ህዝብ አብራክ ነው የወጣሁት ብሎ የሚያስብ ምሁር፣ ትኩረትን ሳይበታትኑ እንደሌዘር አነጣጥሮ ስራን እየለዩ አድምቶ መስራት የሚጠይቅ እጅግ አሳሳቢ የሆነ ዘመን ውስጥ መገኘነቱን መረዳት አለበት።
በ32 አመታት ውስጥ ለአማራው በበጎ መልኩ የተቀየረ ነገር የለም። የባሰ እንጂ። በመሆኑም ነው እርባና በሌላቸው፣ መሬት ላይ ያለውን በአማራ ህልውና ላይ ያሰፈሰፈውን መአት በፍጥነት መፍትሄ በመስጠት አስተዋጽኦ በሌላቸው የትኛዎቹም አጀንዳዎች ላይ፣ ማንኛውም ህልወናዬ አደጋ ላይ ወድቋል ብሎ የሚያምን አማራ መጠመድ የለበትም የምለው። “በጉንጭ እና ብእር አልፋ ምልልሶች የሚጠፋ ጊዜ ሊኖረን አይገባም ።
ሐ) የጽሁፉ ይዘት በተመለከተ
ይህ ጽሁፍ ራሳቸውን በቻሉ የተለያዩ፣ ነገር ግን ተያያዥነት ባላቸው ጉዳዮች ላይ ያተኩራል። ሁሉም ጉዳዮች ላይ የተሰጡ ምልከታዎች የግልና የምር ናቸው። አንዳቸውም ለማምታታትና ለማሳመን (to confuse and convince) የተጻፉ አይደሉም። ሁሉም ጉዳዮች ሰፊ ትልልቅ ርእስ የተሰጣቸው ቢምስልም አሁን በቀጥታ የአማራ ህዝብ ከሚያደርገው የህልውና ትግል ጋር በተያያዘ ቅኝት የተጻፉ ናቸው። የሃሳብ ቦርጭ እንዳይኖራቸው አድርጌ ለማቅረብ ሞክሪያለሁ። ጽሁፉ በሚከተሉት 13 ርእሶች የተከፋፈለ ነው።
- ያለፈው እና መጪው ዘመን ለአማራ፤
- የአማራ የህልወና ትግል የአማራ ታጋዮች የጋራ ግንዛቤ፤
- የአማራ ትግልና የፋኖ ማኒፌስቶ
- የአማራ የህልውና ትግል፣ አማራ ልሂቅ፣ አማራነትና ኢትዮጵያዊነት
- የ1960ዎቹ ትውልድና አማራነት የአማራ ህልውና ትግል
- ህብረ ብሄራዊ የሆነው የጸረ ወያኔ ትግል እና አዲሶቹ የአማራ ብሄረተኞች
- በአማራ አሸናፊነት ላይ የተመሰረተ የአማራ ህዝብ የህልውና ማስከበር ክንውን፣ ሃገራዊ ቀጠናዊና አህጉራዊ አንደምታው
- ወዳጅ ማብዛት ጠላትን መቀነስ የአማራ ስትራተጂ
- የአማራ ህዝብ የህልወና አደጋ ምንጮች ብዙ ናቸው። ሁሉን አደጋዎች በአንድ ጊዜ መጋፈጥ አይቻልም።
- የፋኖ አመራር አንድነት፣ የዳይስፖራ ድጋፍና አንድነት ትስስር
- የአማራ የህልወና ትግል በጤነኛ እና በታመሙ ብሄረተኞች እንቃስቃሴ ላይ ያሳደረው ተጽእኖና አንደምታው።
- የአማራ ህዝብ ለህልውና መከበር የሚያደርገው ትግልና ኤርትራ፣
- የአማራ ህዝብ የህልውና ትግል የመጠንም የአይነትም እመርታ እንዲያሳይ፤
ለሚቀጥሉት 13 ተከታታይ ቀናት ከዚህ በላይ በዘረዘርኳቸው ርእሶች የጻፍኳቸውን ጽሁፎች በፌስቡክና በትዊተር ገጼ አጋራችኋለሁ ተከታተሉ። ለሌሎችም አጋሩ
የአማራን የህልውና አደጋ ከመከላከል ትግል ጋር የተያያዙ የተመጠኑ የግል ምልከታዎች!
March 8, 2025
ቀን የካቲት 2017
በአንዳርጋቸው ጽጌ
ክፍል ፡2 ያለፈው እና መጪው ዘመን ለአማራ፤
ነብይ፣ ጠንቋይ፣ ሳንቲስት መሆንን አይጠይቅም። ያለፉትን መቶ ለመሙላት ጥቂት አመታት የቀረውን ዘመን በደንብ ማጤን ብቻ በቂ ነው። የውጭና የሃገር ውስጥ የአማራ ጠላቶች ተቀናጅተው አማራውን በማንነቱ ለይተው የመከራ ዶፍ አውርደውበታል።
አማራ ባላፉት መቶ አመታት ውስጥ በማንነቱ ላይ ጥቃት ሳይደርስበት ያለፉ ዘመናት ቢኖሩ መንግስታዊ ስርአቱን የተቆጣጠሩት አካላት ማንነታቸውን በኢትዮጵያዊነት የሚገልጹ በሆኑበት ዘመን ብቻ ነው። የኢትዮጵያዊ ገዥዎች ኢትዮጵያውያን በነበሩበት ዘመንም ቢሆን የአማራ ህዝብ በማንነቱ ላይ ያነጣጠረ ጥቃት አይድረስበት እንጂ ከፍቶት ካመጸ በገዥዎች እሳትና ብረት ተቀጥቅጧል።
በተለይ ግን ኢትዮጵያዊ በ1983 አ/ም ጸረ ኢትዮጵያና ጸረ አማራ በሆኑ ጽንፈኛ ብሄረተኞች እጅ ከወደቀች ጊዜ ጀመሮ የአማራ እጣ፣ ስቃይ፣ ሰቆቃ፣ ዋይታ፣ በአሰቃቂ ሁኔታ መገደል፣ መፈናቅል መሰደድ መዋረድ ሆኗል። የ27 አመቱ የወያኔ አገዛዝ የአማራ ህዝብ በማንነቱ ተለይቶ እንዲጠቃ ህገመንግስታዊ፣ አስተዳደራዊ፣ ፖለቲካዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ማህበረሰባዊና ዲፕሎማሲያዊ መደላደሎችን አመቻችቷል። ደግመ ደጋግመን በአማራ ጥላቻ ዙሪያ ወያኔ ስለቀረጸው የ1967 አ.ምቱ ፕሮግራሙ ማላዘን አያስፈልገንም።
ወያኔ ከስልጣን ከወረደ በኋላም ከመቼውም ዘመን በላይ የአማራ ህዝብ መጨፍጨፍና መፈናቀል ገጥሞታል። የጸረ አማራ አመለካከት የሚጋሩ ሃይሎች በህብረት የፈጸሙት ነው። ሆኖም ግን አሁን የአማራ ህዝብና ወንድሙና እህቱ የሆነው የትግራይ ህዝብ ያሉበትን አሰቃቂ ሁኔታ ግምት ውስጥ አስገብተን ወደ ኋላ እየተመለስን መካሰሱ ለማንም እንደማይበጅ ማወቅ አለብን።
የትግራይ ህዝብና የአማራ ህዝብ ዛሬ የሚገኙበት በህልውና ስጋት፣ በሰቆቃ በስቃይ የተሳሰረ የጋራ እጣ፣ ቀድሞም በታሪክ በባህል በቋንቋ በእምነት የተሳስሩትን ያህል ተመሳሳይ መሆኑን እያየን ነው። በበኩሌ ከወያኔ ጋር በተያያዘ የአማራ ህዝብ ያለፈበትን እጅግ አስዛኝና በመከራ የተሞላ ምእራፍ ለታሪክ ጸሃፊዎችና የተረጋጋና ጤነኛ የፖለቲካ አየር ለሚሰፍንባት የሂሳብ ማወራረድ ዘመን ከመተው ውጭ አማራጭ ያለን አይመስለኝም። በትንሹም ቢሆን በጥቅምት 2021 አ.ም በአምስት ክፍል በተከፋፈለ የፌስ ቡክ ጽሁፌ ሂሳብ ሲወራረድ ከአማራ ልሂቅ ይልቅ እዳ ያለበት የትግራይ ልሂቅ መሆኑን በሚገባ ማሳየት ችያለሁ። ይህን አንብቦ አሉላ ስለሞን ሳይቀር “እውነት ነው” የሚል ዳርዳርታ ያለው ንግግር ሲናገር ሰምቸዋለሁ።
መጪው ዘመን ለሁለቱም ህዝቦች ያረገዘው አደጋ ካለፈው የባሰ ነው። ይህ በጋራ የዘመናት ባህልና እሴት መተሳሰር ብቻ ሳይሆን በመጪው አስከፊ ዘመን የጋራ እጣ ጭምር መተሳሰራችን መቀበል፣ መናገር የአንድ ወገን፣ የአማራ ብቻ ስራ መሆን አይችልም። አማራው ይህ የገባው ይመስላል። ፋኖዎች በእስር ቤት ያገኗቸውን 16 የትግራይ ወታደራዊ መኮንኖች ሁኔታዎችን አመቻችተው ወደ ትግራይ የላኩት ይህ ገብቷቸው ነው። የትግራይ ህዝብ እንደሚገባው የሚያጠያይቅ አይደለም። የትግራይ ልሂቅ ግን ይህን መረዳት ይችል ይሆን የሚል ጥያቄ ምላሽ የሚያስፈልገው ነው።
አማራውን በተመለከተ መጪው ዘመን በአደጋና በመልካም እድል የተሞላ ነው። አደጋው አማራው እስከዛሬ ድረስ አይቶት የማያውቀው ጭፍጨፋ፣ እስራት እንግልት መፈናቀል መሰድድ ሊያጋጥመው የሚችልበት እድል እየጨመረ የሚሄድ መሆኑ ነው። ባለፉት ስድስት አመታት የአብይ አህመድ አገዛዝ ከመቼውም ዘመን ከፍቶ እንድናየው ያደረገ የአማራ ህዝብ እልቂት ምን እንደሚመስል አሳይቶናል። ያየነው እልቂት የአማራ ስቃይ ቅምሻ እንጂ፣ በዘረኝነት የተለከፉት የአማራ ጠላቶች ለአማራው የደገሱለት ዋናው ድግስ አይደለም። ድግሱ ምን እንደሚመስል በሰሞኑ አብይ አህመድ አዲስ አባባን ጠቅልሎ፣ ወደመተከል እና ወደ ወሎ እያማተረ የኦሮሞን ግዛት በዘር ማጽዳት ፍጅት ለማስፋት እየተዘጋጀ እንደሆነ በኦፌኮና በኦነግ ቃል አቀባዮቹ በኩል ነግሮናል።
እንዲህ አይነቱ የአብይ አህመድ ትልም የአበደ፣ ሃገር መምራት የተሳነው የአንድ ሰው የእውር ድንብር ጉዞ አድርጎ ማየት ትልቅ ስህተት ነው። በሃሰት ትርክትና በአማራ ጥላቻ አእምሯቸው የተቃወሰ አክራሪ የኦሮሞ ልሂቅ በሙሉ የሚጋራው ነው። ጥላቻን የፖለቲካ ነዳጅ አድርገው የግል ስልጣን እና ጥቅም ማስጠበቂያ ያደረጉ ጽንፈኞችን ከዚህ የተለየ ነገር ማሰብ ይችላሉ ብሎ መቃዠት አያስፈልግም። እነዚህ ሃይሎች በህግ፣ በሰላማዊ ድርድር ከአማራ ጀርባ ላይ ይወርዳሉ ብሎ ማሰብ የኔ ትውልድ ከፈጸመው ጥፋት የከፋ በአዲሱ የአማራ ትውልድ የሚደገም ትልቅ ታሪካዊ ጥፋት ይሆናል።
የአማራ የህልውና አደጋ ዋናው መመከቻ፣ የአማራ ህዝብ ክንድ ብቻ ነው። ስልጡን ፖለቲካ የሚባል ነገር በማይታወቅበት ሃገርና ቀጠና፣ የፖለቲካ ጉልበት ገና ለዘመናት የጥሬ ጉልበት ውጤት ሆኖ በሚቀጥልበት ሃገርና ቀጠና አማራ ትጥቁንና አንድነቱን አላልቶ ህልውናውን ከቶውኑ ማስከበር እንደማይችል መታወቅ አለበት።
መልካም አጋጣሚ ሊሆን የሚችለው ነገር አንድ ነገር ብቻ ነው። የአማራ ህዝብ የተደቀነበትን አደጋ መረዳቱ፣ ይህን አደጋ ለመቀልበስ መሳሪያ ያነሱበትን ሃይሎች ለመከላከል እንደ ህዝብ መሳሪያ ማንሳቱና የመሳሪያ ጉልበቱ በከፈተኛ ደረጃ ላይ የደረሰ መሆኑ ነው። ይህ መልካም አጋጣሚ ግን የበለጠ እንዲጎለብት፣ የጎደሉት በርካታ ነገሮች ገና መሟላት ይገባቸዋል። ፋኖን ብቻ አይደለም፣ በሚሊዮኖች የሚቆጠር አማራ እንደ አንድ ወታደር በጋራ ካልቆመ፣ እንደአንድ ወታደር የአማራ የህልውናን አደጋ ግዙፍነት የተረዳ ንቃተ ህሊና ከሌለው፣ ይህን ግዙፍ አደጋ የሚመጥን ጠንካራ መሪ ድርጅት ከሌለው፣ አንድ ወጥ የሆነ የረቀቀ የፖለቲካ፣ ወታደራዊ፣ ዲፕሎማሲያው ስትራተጂና ታክቲክ ከሌለው፣ ይህ የመልካም እድል ጅማሮ ሊጨናገፍ፣ የተፈራው ከፍተኛ የህልወና አደጋ እውን መሆን ይችላል።
የዚህን ጽሁፍ ክፍል 1 እና 2ን በንባብ ያቀረበልንን EMS አመሰግናለሁ። ለመዳዳመጥ የሚከተልውን ማስፈንጠሪያ ይጫኑ
የአማራን የህልውና አደጋ ከመከላከል ትግል ጋር የተያያዙ የተመጠኑ የግል ምልከታዎች!
March 10, 2025
ቀን የካቲት 2017
በአንዳርጋቸው ጽጌ

ክፍል ፡ 3 የአማራ የህልወና ትግል የአማራ ታጋዮች የጋራ ግንዛቤ፤
- የአማራ የህልወና አደጋ እንዲህ በቀላሉ በዋዛ ፈዛዛ የሚቃለል እንዳልሆነ መታወቅ አለበት። አማራን ስትራተጂያዊ ጠላታቸው አድረገው የሚያዩ አለምአቀፍ፣ ቀጠናዊና ሃገራዊ አካላት አሉ። እነዚህ አካላት ከፍተኛ ሃብት ወታደራዊ ጉልበት፣ ስነልቦናዊ ዝግጅት አላቸው። የአማራ ህዝብ ትግል ይመለከተኛል የሚል ማንኛውም አካል እነዚህ አካላት እነማናቸው የሚለውን ጠንቅቆ ማወቅ ይኖርበታል። ማወቅ ማለት ግን በሚድያ የመናገር ወይም ጽሁፍ ጽፎ ማሰራጨት የሚችልበት አጋጣሚ በተፈጠረ ቁጥር ነጋ ጠባ የአማራ ጠላቶች እነዚህ ናቸው እያሉ ማንቧረቅ ማለት አይደለም።
- አሁን የአማራ ህዝብ የሚገኝበትን የህልወና አደጋና የመከላከል አቅሙ ደረጃ በቅድሚያ አንድና አንድ ነገር ላይ ብቻ እንዲያተኩር ያስገድደዋል። የሃገሪቱን ታንክና ባንክ ተቆጣጥሮ በአማራ ህዝብ ላይ ከዚህ ዘመን በፊት ታይቶ በማይታወቅ ደረጃ የዘር ፍጅት እያደረሰበት ካለው የአብይ አህመድ አገዛዝ በላይ አማራ ጠላት የለውም። ከዚህ ጸረ አማራ አገዛዝ ጋር ለሆዳቸው አድረው በተላላኪነት ከሚያገለግሉ የአማራ ክልል ከፍተኛ ባለስልጣናትና የአብይ አደግዳጊ ባንዳ ምሁራን በላይ ጠላት የለውም።
- በትግል ወቅት የጠላትነትም ሆነ የወዳጅነት ደረጃዎች መታወቅ አለባቸው። ሁለት እግር አለኝ ብሎ ሁለት ዛፍ እንደማይወጣ ሁሉ የተወሰነ ሰራዊት አለኝ ተብሎ ከዋናው ጠላት እኩል ሊወዳደሩ ከማይችሉ፣ ጉልበት ሲደረጅ ልዩነትን በውይይት ወይም በድርድር መፍታት ከሚችሉ መለስተኛና አነስተኛ ጠላቶች ጋር ሁሉ “ኑ ግጠሙኝ” የሚል መልእክት ማስተላለፍ አደገኛ እንደሆነ መታወቅ አለበት።
- አማራው የራሱን የቤት ስራ ሳይሰራ፣ እራሱን ከህልውና አደጋ መከላከል የሚያስችል ጥርት ያለ ሁሉንም አማራ የሚገዛ ርእዮተአለምና ማንም ጉልበተኛ አደብ ማስገዛት የሚያስችል አንድ ወጥ ወታደራዊ ቁመና ሳይላበስ በቀጥታ ከህልውናው ትግል ጋር ግኙነት በሌላቸው የሃገራት፣ የቀጠናው የአፍሪካና የአለም ጉዳዮች ላይ የሚጨነቅብት ምንም አይነት አመክንዮ ማቅረብ አይቻልም። አማራው በኢትዮጵያ በቀጠናው በአለም ጉዳዮች ላይ መሳተፍ የሚችለው ህልወናው ማረጋገጥ የሚያስትል ዋስትና በጁ ሲገባ ነው። አሁን አማራው ያለበት ሁኔታ ይህን ዋስትና ከማግኘት እጅግ የራቀ ነው።
- የአማራ ህዝብ የህልውና ትግል ጥንካሬውን እድገቱን ግምት ውስጥ ያላስገባ ፋይዳቢስ ከሆነ የትኛውም ግዜን ጉልበትን እውቀትን አባካኝ ከሆነ ማንኛውም አይነት የሃገር ውስጥ ተሳትፎ መታቀብ ይኖርበታል። አማራ ይህን የሚያደረግው፣ እንደሌሎች የሃገራችን አክራሪ ብሄረተኞች በጥላቻ ላይ የተገነባ፣ ሌሎች በኢትዮጵያ ውስጥ የሚገኙ ማህበረሰቦችን መቅረብ ሰለማይፈልግ ወይም ኢትዮጵያ የምትባል ሃገር ብትንትኗ ቢወጣ ደንታ ስለሌለው አይደለም። ከሃገረ ኢትዮጵያ ጋር ጠብ ስላለው እንዳልሆነ መታወቅ አለበት። ይህን ሃቅ እያወቁ አማራ “ዝንጀሮ መጀመሪያ መቀመጫየን አለች” በሚል ትክክለኛ ብሂል በመመራት፣ እንደ ህዝብ ሊያጠፋው የመጣውን ማንኛውን ጸረ አማራ ሃይል መመከት የቅድሚያ ተግባሩ ስላደረገ፣ አማራ ስለሌሎች ኢትዮጵያዊ ወንድምና እህቶቹ ደንታ እንደሌለው፣ እንደሌሎች ጽንፈኛ ብሄረተኞች ኢትዮጵያን ለማፍረስ የሚነቀሳቅስ አድርገው ለሚስሉት የትኞቹም አካላት ምላሽ በመስጠት ጊዜውን ማጥፋት፣ በተከላካይነት ስሜት መቆም የለበትም። ይህን አስተያየት በአማራው ላይ መሰንዘር የጀመሩት በምንጅላት ታሪካቸው የባንዳ እዳ ያለባቸው ጸረ ኢትዮጵያ ሃይሎች መሆናቸው መገንዝብ ተገቢ ነው። አማራ ማንነቱን የሚያውቅ በራሱ የሚተማመን በኢትዮጵያ ውስጥ ላሉ የትኞቹም ማህበረሰቦች ሆነ ለኢትዮጵያ ጥላቻ የሌለው ስልጡን ህዝብ ነው።
- ጽንፈኛ ብሄረተኞች ዘመናትን ያስቆጠረ በህግ በባንክና በታንክ ያሰራጩት የአማራ ጥላቻ በተዘራባት ኢትዮጵያ፣ ዛሬ አብዛኛዎቹ የኢትዮጵያ ማህበረሰቦች የአማራ የህልውና ተጋድሎ መሳካት፣ የእነሱ ህልወና ዋስትና እንደሆነ የተረዱበት ሰአት ላይ መድረሳቸውን አማራው ተገንዝቧል። ይህ ሃቅ አማራ በአማራነቱ ተደራጅቶ የሚያደርገውን ትግል ለማንኳሰስ ለሚፈልጉ የአማራ ሆነ የሌሎች ብሄረሰብ ልሂቃን፣ የአማራ ታጋዮች መልስ መስጠት የሌለባቸው እንደሆነ የሚያሳይ መረጃ ነው። “ሙያ በልብ ነው” እዚህ ላይ ይሰራል።
- አማራ እራሱን ሳያድን ኢትዮጵያ እንደማትድን አውቆ ያለምንም መሳቀቅ በሙሉ ልባምነት እራሱን ለማዳን ማድረግ የሚገባውን ሁሉ ማድረግ ይገባዋል። አለም የሚያውቀው ሃቅ አማራ ላይ ለዘመናት ተጠናክሮ የቀጠለው የጥላቻ ትርክትና የማያቋርጥ ጥቃት ምክንያቱ አማራ ሌላ ወንጀል ኖሮበት አይደለም። ኢትዮጵያን እንደሃገር ለማስቀጠል በከፈለው ወሳኝ መስዋእትነት፣ ኢትዮጵያን ለማፍረስ እቅድ የነበራቸውን የውስጥና የወጭ ጠላቶች ህልም በማምከኑ ነው። የአማራው ህልውና የሚከበርበት ሁኔታ ከመጣ በኢትዮጵያ ላይ ያንዣበበው የህልውና አደጋ የሚያበቃለት መሆኑን መጠራጠር አያስፈልግም።
- ጸሃይ የሞቀው ሃቅ ዛሬ ኢትዮጵያ ለምትገኝበት ትልቅ ምስቅልቅል ዋናው ምክንያት፣ ከዚህ ምስቅልቅል በዋንኛነት ሊታደጋት ይችል የነበረው የአማራ ህዝብና ልሂቅ፣ ጸረ ኢትዮጵያና ጸረ አማራ ሃይሎች በሰሩት የሚያስገርም የፖለቲካ ስርጀሪ በሃገሪቱ ፖለቲካዊ ኢኮኖሚያዊ ማህበራዊ ወታደራዊና ዲፕሎማሲያዊ ህይወት ውስጥ ሚና እንዳይኖረው መድረጉ ነው። ሁለንተናዊ አቅሙ እንዲቀጭጭ የተሴረበት በመሆኑ ነው። በዚህ ልዩ የፖለቲካ ቀዶ ጥገና አማራው፣ እንኳን ለሃገር ለራሱም መቆም እንዳይችል ማድረጋቸው ነው።
- ትልቁ ጥያቄ እንደህዝብ እንዲቀጭጭ የተደረገ ህዝብ፣ እንደህዝብ ወደ ትንሳኤ የሚወስደው ትክክለኛና ፈጣን መንገድ የትኛው እንደሆነ መለየት ነው። እውን ይህ መንገድ ዘረኞች ባንክና ታንኩን ተቆጣጥረው ባለፉት 35 አመታት ለሃገራዊ የፖለቲካ አደረጃጀትና እንቅስቃሴ ግጥም አድርገው የዘጉትን የፖለቲካ ምህዳር እንዳልተዘጋ እያስመስሉ፣ ዛሬም እርባና የሌላቸውን ሃገራዊ ፓርቲዎች እናጠናክር ወይም እንደ አዲስ እንፍጠር የሚል ጥሪ ማድመጥ ነው? እስከዛሬ ሲደርግ እንደነበረው በስም ኢትዮጵያዊ በአባላት ይዘታቸው በአማራ የተሞሉ ድርጅቶች እየፈጠሩ፣ በየትኛውም ክልል እንደልብ ተንቀሳቅሶ አባል መመልመል ቢሮ መክፈት በማይቻልበት ሁኔታ መባዘን ነው መፍትሄው? ይህ አካሄድ ከወያኔ ዘመን ጀመሮ በአማራ ህዝብ ላይ የተፈጸምው ግፍ ማስቆም ያልቻለ አካሄድ ነው። ከወያኔ ከልስጣን መገለል በኋላ በመጣውና ከወያኔ ዘመን የባሰውን እጅግ አሰቃቂ የአማራ ህዝብ ፍጅት መፈናቀል፣ በገፍ መታሰር መዋረድ ማስቀረት ያልቻለ ነው። ዛሬስ የአማራ ህጻናትና አረጋውያንን በድሮን እንዳይጨፈጨፉ ማድረግ ችሏል ወይ? እነዚህ ሃገራዊ ድርጅቶች መግለጫ ከማውጣት አልፈው ለአማራው ምን ፈየዱ፣ እንደ ኢዜማ አይነቶቹ በአማራ ህዝብ ደምና አጥንት ላይ ህልውናቸውን የመሰረቱ የፖለቲካ ድርጅቶች ከአብይ አገዛዝ ጋር ተደምረው አማራን የሚጨፈጭፍ ህግ አብይ ሲያወጣ የድጋፍ ድምጻቸውን አልሰጡም?
- ዘመኑ የሚጠይቀው አካሄድ ማንኛውም አማራ በተለይ እንደ ኢዜማ ከመሰሉ በአማራ እልቂት ከኦሮሞ ብልጽግና እኩል ተጠያቂ የሆኑ መሪዎች ካሉት ድርጅት መልቀቅ፣ የአማራን ትግል በአማራነቱ ተቀላቅሎ ማገዝ ነው። በሌሎችም ሃገራዊ ድርጅቶች ውስጥ የሚንቀሳቅሱ አማሮች “ሆድ ሲያውቅ ዶሮ ማታ” የሚለውን የአማራ ተረት ልብ ሊሉ ይገባል። ስልፋቸውን ከአማራው የህልውና ትግል ጋር ማሳመር ብቻ ነው የሃገራዊ ፖለቲካ ህልማቸውን ማሳካት የሚችሉት።
- በኢትዮጵያ ውስጥ ማንም ዜጋ እንዳሸው እንዳይደራጅ፣ በዘረኞች የተዘጋውን የፖለቲካ ምህዳር መከፈት የሚችለው፣ አማራው የህልውናውን አደጋ ለመቀልበስ በሚያደርገው ትግል ብቻ ነው። ሌላ አማራጭ የለም። የዚህ ትግል አደረጃጅት፣ ለመንቃት፣ ለመደራጀት ለመታጠቅ ምቹና ፈጣን እድል የሚሰጠው አማራዊ አደረጃጀት ብቻ ነው። ፖለቲካ የሚሆኑ ነገሮች ጥበብ ነው የሚባለውን ከብዙ የፖለቲካ ተመክሮች ላይ ተመስርቶ የተቀመረውን አባባል የሚረዳ ማንኛውም አማራ፣ ትክክለኛው አማራጭ በአማራነት መደራጀት እንደሆነ ሊስተው አይገባም። ይህ ሃቅ ነው የአማራን የህልውና ትግል ሃገር አፍራሽ፣ ዘረኝነትን አባባሸ አድረግው የሚያዩ አካላት ከተሳሳተ አመለካከታቸው ታርመው፣ አማራ ለህልውና መከበር የሚያደረገውን ትግል በሙሉ ልባቸው እንዲደግፉት ግዴታ የሚጭንባቸው። ይህን ሃቅ በተለይ ለአማራው ከዛም ለኢትዮጵያ እናስባለን የሚሉ ሌሎች ዜጎች በሙሉ ሊያጤኑት ይገባል።
የአማራን የህልውና አደጋ ከመከላከል ትግል ጋር የተያያዙ የተመጠኑ የግል ምልከታዎች!
March 11, 2025
ቀን የካቲት 2017
በአንዳርጋቸው ጽጌ
ክፍል 4 ፡የአማራ ትግልና የፋኖ ማኒፌስቶ
- በተደጋጋሚ አማራ የትግል ማኒፌስቶ የለውም የሚለው ጉዳይ ይነሳል። አዎ የለውም። ይህ ማለት ሁሉም በሃገር ውስጥና ከሃገር ውጭ የሚገኙ የፋኖ ቡድኖች ማኒፌስቶ መጻፍ ተስኗቸዋል ማለት አይደለም። እጅግ በርካታ ማኒፌስቶዎች ተጽፈዋል። ማኒፌስቶ መጻፍ በጣም ቀላል ነገር ነው። በተለይ የአማራ ህዝብ የትግል ማኒፌስቶ። የጎጃሙ የፋኖ አመራር አባል የሆነው አርበኛ አስረስ እንዳለው በቀን 5 ማኒፌስቶ መጻፍ ይቻላል። አርበኛ አስረስ ሁለት አይነት ማኒፌስቶዎች እንዳሉት ገብቶታል። እየተፈለገ ያለው ማኒፌስቶ ዝርዘር የፖለቲካ ፕሮግራምና ፖሊሲዎች እንዴት በተግባር ሊተርጎሙ እንደሚችሉ የሚያሳይ ለምርጫ እየዘጋጁ ያሉ ፓርቲዎች የሚያቀርቡት አይነት ሰንድ አይደለም። ይህ አንዱ አይነት ማኒፌስቶ ነው። ይህ አይነት ማኒፌስቶ የሚዘጋጅበት ሁኔታ የተለየ ነው። ማዘጋጀቱም ዝርዝር ጥናት የሚጠይቅ፤ ሰነዱም በጣም ብዙ ዝርዝር ነገሮችን ያካተተ ነው። ሌላው ማኒፌስቶ በጣም ጥቅል ጉድዮችን የሚያነሳ ነው። የድሮው አብቅቶለት፣ በአዲስ አተያይ በአዲስ አካሄድ ወደ አዲስ ዘመን የሚውስድ ነገር መምጣቱን የሚያበሰር ጥቅል የሆነ መነሻና መዳረሻን የሚያመላክት ማኒፌስቶ ነው።
- አንዳንድ ማኒፌስቶች ጥቅል ሆነውም ረጅም ሊሆኑ ይችላሉ። ዝነኛውና በ1848 በካርል ማርክስ በፍሬድሪክ ኤንግልስ የተጻፈው የኮምኒስት ማኒፌስቶ እንደዚህ አይነት ነው። በትንሽ መጽሃፍ መልኩ የተሰነደ ነው። ይህ የሆነው ሰፊ የንድፈሃሳብ ይዘት ስለነበረው ነበር። አንዳንድ ማኒፌስቶች በጥቂት ገጾች ብቻ የሚጠቃለሉ ናቸው። ሱራሊዝም የሚባለው በ1924 አዲሱን የምስል አሳሳል ፈለግና ንድፈ ሃሳብ ለማመላከት የተጻፈው ሰነድ ስደት ገጾች ርዝመት ነበረው። በተግባራዊ ፖለቲካ በስፋት የሚታወቀው፣ በሩሲያው ንጉሰ ነገስት በኒኮላስ ሁለተኛው ተፈርሞ በ1907 አ.ም የታተመው የጥቅምቱ ማኒፌስቶ በሚባል የሚታወቀው ሰነድ ብዙ መሰረታዊ የፖለቲካ ቁምነገሮችን አካቶ በአንድ ገጽ ተኩል ላይ ብቻ ያረፈ ነበር። ንጉሰ ነገስት ኒኮላይ የአገሩን ፖለቲካ ለመቀየር የሚወስዳቸውን አዳዲስና ጥቅል እርምጃዎችን የሚያመላክት ሰንድ ነው። ዝርዝር ውስጥ አይገባም። የአማራ ህዝብ ካላበት የፖለቲካና በተለይ ወታደራዊ አቅም ደረጃ ሲታይ ዝርዝር ውስጥ የሚገባ ማኒፌስቶ አያስፈልገውም። በጥቅሉ ምን ትግሉን እንደቀሰቀሰው ትግሉ በየት አልፎ የት መድረስ እንደሚፈልግ፣ የሚያመላክት ሊሆን ይችላል። ለአማራ ለተቀረው የኢትዮጵያ ህዝብ ለቀጠናውና ለአለም ማህበረስብ የሚያውጀው ነገር ይኖረዋል። አበቃ። በጣም ዝርዝር ውስጥ የሚገባ ማኒፌስቶ የውጭ አካላትን ማሳመን ቅርቶ በፋኖዎችም መሃከል ስምምነት እንዳይኖር ሊያደርግ ይችላል። ማኒፌስቶው ጥቅል የሆኑ ነገሮችን ያካተተ እንዲሆን የሚመከረው ለዚህ ነው።
- ሌላው ትልቁ ቁም ነገር ማኒፌስቶ ማዘጋጀቱ ሳይሆን ማኒፌስቶውን ሁሉም የአማራ ፋኖዎች በጋር የተቀበሉትና ያጸደቁት መሆኑ ነው። ይህ እስካልሆነ ድረስ የተለያዩ ማኒፌስቶዎች በተለያዩ ቡድኖች መዘጋጀታቸው ብቻ፣ አማራ ትግሉን በተመለከተ ማኒፌስቶ የለውም የሚለውን ክስ ማስቆም አይቻልም። ስለሆነም ትልቁ አንገብጋቢ ጥያቄ ማኒፌስቶ ሳይሆን የህልወናውን አደጋ የጋራ አጀንዳና መሰባስቢያ አድረጎ አንድ የአማራ ፋኖዎች የጋራ የፖለቲካና ወታደራዊ አደረጃጀት መፍጠር ነው። ይህ አደረጃጀት በተፈጠረ ማግስት የማኒፌስቶ ችግር ብቻ ሳይሆን፣ በፋይናንስ፣ በሎጂስቲክ፣ በዲፕሎማሲ፣ በህዝብ ግንኙነትና በሌሎችም የስራ ዘርፎች የአማራ የህልውና ትግል የገጠሙትን ሌሎችንም ችግሮች በቀላሉ መቅረፍ ይቻላል።
- ፋኖ የጋራ አመራር ከፈጠረ በኋላ በማኒፌስቶ ላይ ከሚቀርቡ ጥቅል ከሆኑ ጉዳዮች ወደ ዝርዝርዝ ጉዳዮች መግባት ይችላል። እነዚህ ዝርዝር ጉዳዮችም ቢሆኑ የአስፈላጊነት ቅደም ተከተል ያላቸው የፋኖን የፖለቲካና ወታደራዊ አደረጃጀት እድገትና ጥንካሬ ግምት ውስጥ በማስገባት የሚሰሩ ናቸው። ከማኒፌስቶ በፊት ከሌላም ጉዳይ በፊት፣ የአማራ ፋኖ የስራዎች ሁሉ እናት የሆነው ስራው አንድ ፖለቲካዊና ወታደራዊ የጋራ አመራር ባስችኳይ የማቆም ስራ ነው። የአማራን የህልውና ትግል የሚደግፍ ማንኛው የአማራ ህዝብ ወዳጅ፣ ጉልበቱን እውቀቱን ሃብቱን ስራ ላይ ማዋል የሚገባው ይህ የጋራ አመራር በፍጥነት እንዲፈጠር በመጣር ስራ ላይ ነው። ይህ እንዳይፈጠር የሚፈልግ ወይም የሚጥር አማራ ከዋናዎቹ የአማራ ጠላቶች ልዩነት ያለው መሆን አይችልም።
