
ከ 5 ሰአት በፊት
ሐጅ በመላው ዓለም የሚገኙ ሁለት ሚሊዮን የሚሆኑ ሙስሊሞች በየዓመቱ ሳዑዲ አረቢያ ወደሚገኘው መካ የሚያደርጉት መንፈሳዊ ጉዞ ነው።
ከአምስቱ የእስልምና መሠረቶች መካከል አንዱ የሆነው የሐጅ ጉዞ፣ የአካል እና የኢኮኖሚ አቅሙ ጠንካራ የሆነ የእምነቱ ተከታይ በዓመት ቢያንስ አንድ ጊዜ እንዲያደርገው ይጠበቃል።
ሐጅ ከመላው ዓለም የሚገኙ የእምነቱን ተከታዮች የሚያሰባስብ ትልቅ ዓመታዊ ሥነ ሥርዓት ነው።
መካ የነብዩ ሙሐመድ የትውልድ ቦታ እና ቅዱስ ቁርዓን የተቀበሉበት ስፍራ ነው።
ከዚህም በተጨማሪ አራት መዓዘን ቅርጽ ያለው እና ጥቁር መጎናፀፍያ የለበሰው፣ አል ሃራም መስጂድ እምብርት ላይ የተተከለው ካዓባ መገኛም ነው።
የሙስሊሞች ቅዱስ ሥፍራ ተደርጎ የሚቆጠረው ይህ መስጂድ የመካ ታላቁ መስጂድ በመባልም ይታወቃል።
ምናልባት ስለ ሐጅ የማያውቋቸው አምስት ነጥቦች እነሆ።

ካዓባ – በነቢዩ ኢብራሂም እንደተጀመረ ይታመናል
ዓመታዊ የሐጅ ጉዞ ከእስልምና መሠረቶች መካከል አንዱ ነው።
ነገር ግን አንድ ሰው የሃይማኖቱ መሥራች ከሆኑት ከነብዩ ሙሐመድ ጋር ብቻ የተያያዘ ነው ብሎ ቢያምን ይቅርታ ሊደረግለት ይችላል።
እውነታው ሥርዓቱ የተጀመረው በነቢዩ ኢብራሂም ሲሆን፣ በእስልምና እምነት መሠረት ካዓባ ከመገንባቱ ጀርባ እንደነበሩ ይታመናል።
የሐጅ ሥነ ሥርዓት ልጁን አላህን በመታዘዝ ለመስዋዕትነት ማቅረቡን ያስታውሳል፤ የቀረበው መስዋዕት በመለኮታዊ ጣልቃ ገብነት ተጠናቅቋል።
በክርስትና እና በአይሁድ እምነት አብርሃም በመባል የሚታወቁት ነቢዩ ኢብራሂም የሁለቱም እምነት ዋና አካል ናቸው።

በፆታ መለያየት የለም
እንደሌሎች እስልማና እምነት ሥርዓቶች በሐጅ ጊዜ በፆታ የተነሳ መለያየት የለም።
ለምሳሌ በአብዛኞቹ መስጂዶች ውስጥ ለወንዶች እና ለሴቶች የተለያዩ በሮች ወይም የተለያዩ የፀሎት ቦታዎችን ያሉ ቢሆንም፤ በሐጅ ወቅት ግን ወንዶች እና ሴቶች በተመሳሳይ ቦታ ተመሳሳይ የእምነቱን ሥርዓት ጎን ለጎን በመሆን ይፈጽማሉ።
የተለየ የአለባባስ ሥርዓት

የሐጅ ተጓዦች የመንፈሳዊ እኩልነት እና ትህትናን የሚያሳዩ የአለባበስ ሥርዓቶችን ይከተላሉ።
ወንድ የሐጅ ተጓዦች ኢህራም ተብሎ የሚታወቀውን እና ከየትኛውም ማኅበራዊ ወይንም ምጣኔ ሃብታዊ ዳራ የሚመጡ የእምነቱ ተከታዩች በእኩል የሚታዩበትን ቀለል ያለ ነጭ ልብስ ይለብሳሉ።
ሴቶች ደግሞ እንደ ወንዶቹ ነጭ እንዲለብሱ የማይፈቀድ ሲሆን ከዚያ ይልቅ ለቀቅ ያለ፣ አካላቸውን የሚሸፍን አልባሳት እንዲያደርጉ ይፈቀድላቸዋል።
ፀጉራቸውን በሂጃብ እንዲሸፍኑ የሚጠበቅ ሲሆን፣ በሐጂ ወቅት ግን ፊታቸውን መሸፈን አይኖርባቸውም።
ተራራ መውጣት
የሐጅ ሥነ ሥርዓቶች በጣም ከሚታወቁት አንዱ ጠዋፍ ሲሆን፣ ምዕመናን ካዓባውን ከግራ ወደ ቀኝ አቅጣጫ በሐጅ መጀመሪያ እና መጨረሻ ላይ ሰባት ጊዜ ይዞራሉ።
ነገር ግን ሌላው ቁልፍ ሥነ ሥርዓት በሁለት ኮረብታዎች መካከል መራመድን ያካትታል።
የሐጅ አካል የሆነው በአል-ሃራም መስጂድ ውስጥ በሚገኙት በሰፋ እና በመርዋ ኮረብታዎች መካከል ሰባት ጊዜ መመላለስን እና በእግር መጓዝን ያካትታል።
ይህም የነብዩ ኢብራሂም ባለቤት ሀጀር፣ በሁለቱ ኮረብታዎች መካከል በመሮጥ ለጨቅላ ልጇ ውሃ ለመፈለግ ያደረገችው ጥረት እና ትዕግስትን ለማስታወስ የሚደረግ ተግባር ነው።
አረፋት ተራራ

ምንም እንኳ የሐጅ ጉዞ ማዕከሉ ከአባው ቢሆንም፣ መንፈሳዊ ከፍታው ግን ከመካ ውጪ በሚገኘው የአረፋት ተራራ ላይ ወጥቶ መፀለይን ያካትታል።
በዚህ ስፍራ በርካታ የእምነቱ ተከታዩች ከፀሐይ መውጣት እስከ መጥለቅ ድረስ ተሰባስበው ይፀልያሉ፤ ቁርዓን ይቀራሉ።
ይህ ቅዱስ ስፍራ በእስልምና ጥልቅ ትዕምርት ይዟል። በእስልምና እምነት መሠረት ነቢዩ ሙሐመድ የመጨረሻውን ትምህርት ያስተማሩበት ቦታ ነው።