ግእዝን እንማር ·Follow

❖ ፊደልና የፊደላት ትርጉም

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞🙏

፩. ፊደል ➙ የሚለው ቃል ➙ <ፈደለ> ጻፈ ፣ አመለከተ ከሚለው ሥርወ ግስ የተገኘ ሲሆን ፊደል ማለት ጽሕፈት /ምልክት/ ማለት ነው።

➙ ፊደል ስያሜው ዘመድ ዘር ነው።

➙ ፊደል የነገርና የቃል ምልክት ነው።

➙ የግእዝ ፊደል ደግሞ ጽሕፈት ሲጀመር አብሮ የኖረና ከእብራይስጡ ፊደል ጋር ተመሳስሎ ብዙ ሲሰራበት የኖረ ነው።

➙ የግእዝ ፊደል በጥታዊነቱ የታወቀና ከእብራይስጥ እና ከአረማይክ ፊደላት ጋር በቀዳሚነት ሲያገለግል እንደነበረ ይነገራል።

፩.፩ የግእዝ ፊደላት እድገት /አቀማመጥ/

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

➤ የግእዝ ፊደላት ከቅረጻቸው አንጻር ሦስት ደረጃወች አሉት።

አነሱም፦

ሀ, የመጀመሪያው /የአ-በ-ገ-ደ-/ ቅደም ተከተል

ለ, የተቀየረው/ የ ሀ-ለ-ሐ-መ/ ቅደም ተከተል

ሐ, ለማስተማሪያነት እንዲያገለግል ቅጥያዎች የተጨመሩለት /አ-ቡ -ጊ-ዳ-ሄ -ው -ዞ/ በሚል አካሄድ የተዘገጀው ነው።

ሀ, የመጀመሪያው አቀማመጥ በግእዝ ቋንቋ የሚታወቀው የመጀመሪያ የመጀመሪያ ፊደል ብቻ ነበር።

ማለትም ➙ አ – በ – ገ – ደ እያለ ከላይ ወደታች ያለው ፊደል ብቻ ነበር።

ግእዝ የተባለውም ለዚህ ነው።

ግእዝ ማለት መጀመሪያ ማለት ስለሆነ።

➙ ለምሳሌ ፦ መኮነን የሚባል ስም በጥንቱ አጻጻፍ

➙ መከነነ ይባላል ማለት ነው።

ይህም በጥንታዊ መካነ መቃብራት ላይ ተጽፎ ይገኛል። “ዘ ሐወለተ ዘአገበረ አገዘአ ለአበሀ” የሚል ጽሑፍ ይገኛል። በአሁኑ አጻጻፍ

➙ “ዝ ሐውልት ዘአግበሮ እግዚኡ ለአቡሁ” ለማለት ነው።

ይህ ምንአልባት በጣም ጥንታዊ ከመሆኑ የተነሳ በመካነ መቃብሮችና ድንጋዮች ላይ ከልሆነ በብራና ጽሑፍ ላይ ብዙም አይገኝም።

ይህም ከጊዜ በኋላ ስድስት ቅጥያዎች ወደጎን ተጨምረውለት አሁን የምነገለገልበት የፊደል ገበታ ሁኗል።

ምሳሌ ፦

➙ አ ኡ ኢ ኣ ኤ እ ኦ

➙ በ ቡ ቢ ባ ቤ ብ ቦ

➙ ገ ጉ ጊ ጋ ጌ ግ ጎ

➙ ደ ዱ ዲ ዳ ዴ ድ ዶ

ቀሪዎቹን ከፊደል ተመልከት።

ለ, የተቀየረው /የ ሀ-ለ-ሐ-መ/ ቅደም ተከተል

ይህ ደግሞ ከ/አ-በ -ገ -ደ/ ወደ /ሀ-ለ-ሐ-መ/ የተቀየረው የፊደል ገበታ ነው።

➙ የተቀየረውም በከሣቴ ብርሃን እና አብረውት በነበሩት ጽርአውያንና ቅብጣውያን እንደሆነ ይነገራል።

➙ በዚህ ጊዜ አጻጻፋ እንደ ሱርስት ፣ እንደ ዐረብና እንደ ዕብራይስጥ ከቀኝ ወደ ግራ የነበረው እንደ ቅብጥና እንደ ጽርእ ከግራ ወደ ቀኝ ተቀይሯል።

➙ የግሱንም አካሄድ ቀይረው መነሻውን መድረሻ መጨረሻውን ደግሞ መነሻ አድርገውታል።

➙ በዚህም የተነሳ አ-በ-ገ-ደ ቅደም ተከተል እየተረሳ ሀ-ለ-ሐ-መ ቅደም ተከተል እየሰፋ ሂዷል።

ምሳሌ፦

➙ ሀ ሁ ሂ ሃ ሄ ህ ሆ

➙ ለ ሉ ሊ ላ ሌ ል ሎ

➙ ሐ ሑ ሒ ሓ ሔ ሕ ሖ

➙ መ ሙ ሚ ማ ሜ ም ሞ

❖ የግሱንም አካሄድ ለምሳሌ

➤ የ “ሀ” ነጠላ ግስ

➙ ሀለለ ➙ በራ

➙ ሐመለ ➙ ለቀመ

➙ ኀመሰ ➙ አምስት አደረገ

➙ ሐረሰ ➙ አረሰ

➙ ሀደሰ ➙ አደሰ ወዘተ እያለ መሄድ ሲገባው “ሀ” ን በመጨረሻው እያደረገ ይሄዳል።

ለምሳሌ፦ የ”ሀ” ነጠላ ግስ

➙ ሀለሀ = ወደረ

➙ ለህሀ = ቀዳ

➙ መርሐ = መራ

➙ ሞርቅሀ = ላጠ

➙ ሠርሐ = አሰናበተ

➙ ሠርሀ = ሠራ ወዘተ እያለ ከ”ሀ” –“ፐ ” ይዘልቃል። ይህም ከሌሎች መዝገበ ቃላት የተለየ አካሄድ እንዲኖረው አደርጎታል።

ሐ, ሦስተኛው የፊደል ገበታ ደግሞ ከጊዜ በኋላ ሁሉንም ፊደላት በሠንጠረዥ መልክ ለማስተማር

ይጠቅም ዘንድ የተዘጋጀው አቀማመጥ ነው።

➙ አካሄዱም በሰያፍ መልክ ሲሆን ለማስተማሪያነት ተመራጭ ያደርገዋል።

❖ ለምሳሌ ፦

➙ አ ቡ ጊ ዳ ሄ ው ዞ

➙ በ ጉ ዲ ሃ ዌ ዝ ሖ

➙ ገ ዱ ሂ ዋ ዜ ሕ ጦ

➙ ደ ሁ ዊ ዛ ሔ ጥ ዮ

፩. ፫ ስመ ፊደላት ወትርጓሜሆን

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

❖ የግእዝ ፊደላት መነሻ ትርጉማቸው ሥጋዊ እና መንፈሳዊ ተብለው ይከፈላሉ።

ሀ, በሥጋዊ ትርጉምና አፈታት ሁሉም የፍጥረታት ስሞች ናቸው።

➤ ፊደል ➤ እብራይት ➤ ትርጉም

❖ አ ➙ አልፍ ➙ ቀንድ

❖ በ ➙ ቤት ➙ በቁሙ

❖ ገ ➙ ገምል ➙ ግመል

❖ ደ ➙ ድልት ➙ መዝጊያ

❖ ሀ ➙ ሆይ ➙ ኗሪ

❖ ወ ➙ ዋዌ ➙ ወገል

❖ ዘ ➙ ዛይ ➙ ጌጥ

❖ ሐ ➙ ሐውት ➙ ሕይወት

❖ ኀ ➙ ኀርም ➙ ልዩ

❖ ጠ ➙ ጠይት ➙ ሥን/ጥበብ

❖ የ ➙ የማን ➙ ቀጅ እጅ

❖ ከ ➙ ካፍ ➙ ከሃሊ

❖ ለ ➙ ለዊ ➙ ጠማማ

❖ መ ➙ ማይ ➙ ውሃ

❖ ነ ➙ ነሐስ ➙ ሽቦ

❖ ሠ ➙ ሠውት ➙ ሰብል

❖ ዐ ➙ ዐይን ➙ ምንጭ

❖ ፈ ➙ ፌ ➙ አፋፍ

❖ ጸ ➙ ጸደይ ➙ የዘር ወራት

❖ ፀ ➙ ፀጳ ➙ እሳታዊ

❖ ቀ ➙ ቆፍ ➙ ዝንጀሮ

❖ ረ ➙ ሬስ ➙ ሰዐት

❖ ተ ➙ ታው ➙ ትምህርተ መስቀል

❖ ጰ ➙ ጰይት ➙ ቤት

❖ ፐ ➙ ፔ ➙ ፌ

❖ ፊደላተ ግእዝ በበ አርባዕቱ

➤ አ በ ገ ደ ➤ ኀ ጠ የ ከ ➤ ዐ ፈ ጸ ፀ

➤ ሀ ወ ዘ ሐ ➤ ለ መ ነ ሠ ➤ ቀ ረ ሰ ተ

➤ ጰ ፐ

ለ, በመንፈሳዊ ትርጉም ሁሉም ፊደላት የፈጣሪ ስሞች ናቸው።

ለምሳሌ፦

➙ ሀ ብሂል ሀልዎቱ ለአብ እምቅድመ ዓለም

➙ ለ ብሂል ለብሰ ሥጋነ ወጾረ ሕማመነ

➙ ሐ ብሂል ሐመ ወሞተ ወተቀብረ

➙ መ ብሂል መጽአ ኀቤነ ወአድኀነነ እያለ ይቀጥላል።

************** ❖ ምልማድ **************

፩, የግእዝ ቋንቋ መስራች ፊደላት ስንት ናቸው?

፪, ጽሕፈት መቸ እና እንዴት እንደተጀመረ ከመረጃ ጋር አብራራ

፫, የግእዝ ፊደላትን ከ አ-በ-ገ-ደ ወደ ሀ-ለ-ሐ-መ ቅደም ተከተል የተቀየሩት በማን ነው?

ለምን? ምክንያቱን ዘርዝር

፬, አሁን ያለው የፊደል ገበታ ስንት ደረጃዎች አሉት?

፩. ፬ ስያሜ ሰብዑ ፊደላት

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

➤ የግእዝ ቋንቋ ፊደላት ስድስት ቅጥያዎች ወደጎን ከተጨመረላቸው በኋላ ቅጥያዎቹ ለየራሳቸው ስያሜ ተሰጥቷቸዋል። እነዚህም በቅደም ተከተል ተገልጸዋል።

ምሳሌ ፩,

❖ ፊደል ❖ ስያሜ ❖ ትርጒም

፩ኛ ➙ አ ➙ ግእዝ ➙ መጀመሪያ

፪ኛ ➙ ኡ ➙ ካዕብ ➙ ሁለተኛ

፫ኛ ➙ ኢ ➙ ሣልስ ➙ ሦስተኛ

፬ኛ ➙ ኣ ➙ ራብዕ ➙ አራተኛ

፭ኛ ➙ ኤ ➙ ኀምስ ➙ አምስተኛ

፮ኛ ➙ እ ➙ ሳድስ ➙ ስድስተኛ

፯ኛ ➙ ኦ ➙ ሳብዕ ➙ ሰባተኛ

ምሳሌ ፪

❖ ፊደል ❖ ስያሜ ❖ ትርጒም

፩ኛ ➙ ሀ ➙ ግእዝ ➙ አንደኛ

፪ኛ ➙ ሁ ➙ ካእብ ➙ ሁለተኛ

፫ኛ ➙ ሂ ➙ ሣልስ ➙ ሦስተኛ

፬ኛ ➙ ሃ ➙ ራብዕ ➙ አራተኛ

፭ኛ ➙ ሄ ➙ ኀምስ ➙ አምስተኛ

፮ኛ ➙ ህ ➙ ሳድስ ➙ ስድስተኛ

፯ኛ ➙ ሆ ➙ ሳብዕ ➙ ሰባተኛ

፩. ፭ ጠባይዐ ሰብዐቱ ፊደላት

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

➤ የሰብዐቱ ፊደላት ጠባይ ከሚፈጠሩት አንጻር የተለያየ ጠባይ አላቸው።

➙ የግእዝ ጠባዩ በቀላሉ አፍ ማስከፈት ነው።

➙ የካዕብ ጠባዩ ልክ እንደ ፋጨት ከንፈር እንዲያሞጠሙጥ ማድረግ ነው።

➙ የሣልስ ጠባዩ ልክ እንደ ሣቅ አፍ ማስለቀቅ ነው።

➙ የራብዕ ጠባዩ ከመጠን በላይ አፍን ማስከፈት ነው።

➙ የኀምስ ጠባዩ ወደ ጎን ሆኖ እንደ ሣልስ አፍ ማስለቀቅ ነው።

➙ የሳድስ ጠባዩ ቀለል ያለ ሆኖ ልክ እንደ ትንፋሽ ነው።

➙ የሳብዕ ጠባዩ እንደ ፋጨት ከንፈር ክብ ማድረግ ነው።

➤ በዚህም የተነሣ የሚፈጠሩበትን ማወቅ ይቻላል።

➤ መካነ ፍጥረት ➤ ብዛት ➤ ፊደላት

❖ የጒሮሮ ድምፆች ➙ ፭ ➙ አ ፣ ዐ ፣ ሀ ፣ ሐ ፣ ኀ

❖ የትናጋ ድምፆች ➙ ፬ ➙ ገ ፣ የ ፣ ከ ፣ ቀ

❖ የከንፈር ድምፆች ➙ ፮ ➙ በ ፣ ወ ፣ መ ፣ ፈ ፣ ጰ ፣ ፐ

❖ የጥርስ ድምፆች ➙ ፮ ➙ ዘ ፣ ሠ ፣ ሰ ፣ ጸ ፣ ፀ ፣ ረ

❖ የምላስ ድምፆች ➙ ፭ ➙ ደ ፣ ጠ ፣ ለ ፣ ነ ፣ ተ

➤ በተጨማሪም እነዚህን ሰብዐቱ ስያሜዎች ሦስቱ ወራሾች ፣ ሦስቱ ተወራሾች እና አንዱ ወራሽም ተወራሽም ያልሆነ ብለንእንከፍላቸዋለን።

❖ ሦስቱ ወራሾች፦

➙ ግእዝ

➙ ኀምስ

➙ ሳብዕ

❖ ሦስቱ ተወራሾች፦

➙ ሳድስ

➙ ሣልስ

➙ ካእብ

❖ ወራሽም ተወራሽ ያልሆነ፦

➙ ራብዕ ናቸው።

ማለትም ግእዝ ሳድሱን ፣ ኀምስ ሣልሱን እና ሳብዕ ካእቡን ይወርሱታል።

➤ ለበለጠ ገቢርና ተገብሮ ላይ ስንደርስ እንማረዋለን።

፩. ፮ ተሰዐቱ ተሞክሳዪያት ፊደላት ወትርጓሜሆን

✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞✞

➤ የግእዝ ቋንቋ ከ ፳፮ቱ ፊደላት ውስጥ ዘጠኙ ፊደላት በሞክሸነት ይታወቃሉ።

ነገር ግን እነዚህ ፊደላት ከጊዜ ብዛት የተነሣ ድምፀታቸው እየጠፋ ወደ ተመሳሳይነት መጡ እንጅ በንበታቸውም በትርጒማቸውም እንዲሁም በቅርፃቸው ፍጹም የተለያዩ ናቸው።

እነዚህም ፊደላት የሚከተሉት ናቸው

➤ ሦስቱ “ሀ”ዎች ➙ ሀ ፣ ሐ ፣ ኀ

➤ ሁለቱ “አ” ዎች ➙ አ ፣ ዐ

➤ ሁለቱ “ሠ”ዎች ➙ ሠ ፣ ሰ

➤ ሁለቱ “ጸ” ዎች ➙ ጸ ፣ ፀ

እነዚህ ፊደላት ከላይ እንደ አየናቸው በቅርፃቸው በጣም የተለያዩ ናቸው።

➙ የንበት ወይም የድምፅ ልዩነታቸው

❖ ከ “አ” ድምፅ የ”ዐ” ድምፅ ይበረታል

❖ ከ “ሰ” ድምፅ የ”ሠ” ድምፅ ይበረታል

❖ ከ “ሀ” ድምፅ የ”ሐ” እና” ኀ” ድምፅ ይበረታል

❖ ከ “ጸ” ድምፅ የ”ፀ” ድምፅ ይበረታል

➙ የትርጒም ልዩነታቸው

እነዚህ ፊደላት በግእዝ ቋንቋ ሥርዓት ሰፊ የሆነ የትርጒም ልዩነት አላቸው።

ለምሳሌ፦

፩ኛ የሦስቱ” ሀ”ዎች ትርጉም ልዩነት

ሀ ➙ መሀረ = አስተማረ ➙ ምሁር

ሐ ➙ መሐረ = ይቅር አለ ➙ ምሑረ

ኀ ➙ ኀለየ = ዘፈነ/አመሰገነ ➙ ማኅሌት

ሐ ➙ ሐለየ = አሰበ ➙ሕሊና/ማሕሌት

፪ኛ የሁለቱ “አ”ዎች ትርጉም ልዩነት

አ ➙ ሰአለ = ለመነ ➙ ሰኣሊ = ለማኝ

ዐ ➙ ሠዐለ = ሣለ ➙ ሠዓሊ = ሥልሣዪ

አ ➙ አመት = አገልጋይ /ለሴት/

ዐ ➙ ዐመት = ዘመን / ጊዜ

አ ➙ ገአዘ = ጀመረ

አ ➙ ግእዝ = መጀመሪያ/አንደኛ

ዐ ➙ ገዐዘ = ተጓዘ / ነፃ ወጣ

ዐ ➙ ግዕዝ = ነፃ መውጣት ወዘተ

፫ኛ የሁለቱ “ሰ”ዎች ትርጉም ልዩነት

ሠ ➙ ሠረቀ = ወጣ ➙ ምሥራቅ

ሰ ➙ ሰረቀ = ሰረቀ ➙ ምስራቅ

ሠ ➙ ሠዐለ = ሥል ሣለ

ሰ ➙ ሰአለ = ለመነ

ሠ ➙ ሠርሐ= ሠራ ➙ ሥራሕ = ሥራ

ሰ ➙ ሰርሐ = አከናወነ /ር/ ይጠብቃል

፬ኛ የሁለቱ “ጸ” ዎች ትርጉም ልዩነት

ጸ ➙ ነጸረ = አየ/ጠብቆ/ ➙ ነጽር = እይ

ፀ ➙ ነፀረ = ለየ ➙ ነፅር = ለይ

ጸ ➙ ፈጸመ = ጨረሰ ➙ ፍጻሜ

ፀ ➙ ፈፀመ = ነጨ ➙ ፍፅም = ግንባር

እነዚህን የምንለያቸው ከመዝገበ ቃላት በትክክል የተጻፋትን በመለየት ነው።

➤ በተጨማሪም እነዚህ ፊደላት ለየራሳቸው መጠሪያ ስም አላቸው።

➤ ፊደላቱ ➤ መጠሪያቸው

❖ ሀ ➙ ሃሌታው ሀ

❖ ሐ ➙ ሐመሩ ሐ

❖ ኀ ➙ ብዙኃኑ ኀ

❖ አ ➙ አልፋው አ

❖ ዐ ➙ ዐይኑ ዐ

❖ ሠ ➙ ንጉሡ ሠ

❖ ሰ ➙ እሳቱ ሰ

❖ ጸ ➙ ጸሎቱ ጸ

❖ ፀ ➙ ፀሐዩ ፀ

በመባል ይታወቃሉ።

************* ➤ ምልማድ ***************

➤ ምልማድ ፩

❖የሚከተሉትን ጥያቄዎች በማንበብ ትክክለኛ መልስ የያዘውን ፊደል ምረጡ

፩, አፍ በጣም የሚያስከፍተው የቀለም ዐይነት _______ ቀለም ነው።

ሀ, ግእዝ ለ, ካዕብ ሐ, ራብዕ መ, ሳድስ

፪, ከሚከተሉት አንዱ የግእዝ አጻጻፍ ሥርዓትን አልተከተለም

ሀ, ጸሎተ ሃይማኖት ሐ, ቅብዐ ሜሮን

ለ, ቤተ እስራኤል መ, ቃለ ኅይወት

፫, “ዉ” ይህ ፊደል መጠሪያው ምን ይባላል?

ሀ, ሳድስ ለ, ሣልስ ሐ, ካዕብ መ, ግእዝ

፬, “ሐ” እና “አ” ድምፆች መካነ ፍጥረታቸው ____ ነው።

ሀ, ድምፀ ከንፈር ሐ, ድምፀ ልሳን

ለ, ድምፀ ጒርዔ መ, ድምፀ ስን

፭, ከሚከተሉተት አንዱ ወራሽም ተወራሽም አይደለም።

ሀ, ግእዝ ለ, ካዕብ ሐ, ራብዕ መ, ሣልስ

፮, ግእዝ የሚወርሰው ቀለም ____ ነው።

ሀ, ሳድስን ለ, ራብዑን ሐ, ካዕቡን መ, ሣልስን

፯, “ኀ” ይህ ፊደል በግእዝ አጠራር ምን ይባላል?

ሀ, ሐመሩ ለ, ብዙኃኑ ሐ, ሃሌታው መ, ሀገሩ

**************************

************* ➤ ምልማድ ፪***************

➤ የሚከተሉትን የግእዝ ጥምር ቃላት በትክክለኛ የግእዝ አጻጻፍ ከተጻፉ “ርቱዕ” ካልተጻፉ ደግሞ ” ኢርቱዕ” በማለት መልሱ።

➤ የግእዝ ቃላት ➤ ርቱዕ / ኢርቱዕ

➙ ሕገ መንግስት ➙ ____

➙ ሰማየ ሰማያት ➙ ___

➙ ደብረ መዊዕ ➙ ____

➙ ጸኀየ ፅድቅ ➙ ____

➙ ምሥራቀ ፀሐይ ➙ ___

➙ መላዕክት ➙ ____

➙ ባህልና ትውፊት ➙ ___

➙ አምደ ሐይማኖት ➙ ___

➙ ፍቅረ ሰብዕ ➙ ____

➙ ሐረገ ወይን ➙ _____

➙ ድምፀ አራዊት ➙ _____

➙ ሐገረ እግዚአብሄር ➙ ___

**************************

************* ➤ ምልማድ ***************

ምልማድ ፫

➤የሚከተሉትን ጥያቄዎች አብራሩ

፩, እንደሚታወቀው ሞክሸ ፊደላት ይቀነሱ የሚሉ ምሁራን አሉ ይቀነሱ ያሉበትን ምክንያት በዝርዝር አስቀምጡ።