Haileyesus Adamu ·Follow
“የኦሮሞ መንግስት” እያለ ራሱን የሚጠራው ብልፅግና ማህበራዊ መሰረቱ የት ነው?
1 . የብልፅግና ማህበራዊ መሰረቶች የት ናቸው?
ከለውጡ ግዜ ጀምሮ ሚዛኑን እና የፖለቲካ መካከለኝነቱን ለመጠበቅ ሲቸገር የነበረው ብልፅግና “ኢትዮጵያዊነት ሱስ ነው” ከሚለው አቋሙ ወደ “ኦሮሞ ተረኛ ነው ” የሚል ሌላ ዋልታ ረገጥ የፖለቲካ መስመር መግባቱን እያየን ነው።
ብልፅግና “የኦሮሞ ተረኛ መንግስት ነኝ ” በማለት ማህበራዊ መሰረቱን ኦሮሞ ላይ ለመትከል እየሞከረ ቢሆንም አሁን ላይ በተጨባጭ የብልፅግና ማህበራዊ መሰረቶች የሚከተሉት ይመስሉኛል ።
ኦሮሚያ ክልል ውስጥ ፦
፨ የሸዋ ኦሮሞ ፦ አብዛኛው የሸዋ ኦሮሞ ልሂቅ በብልፅግና ዙሪያ እየተሰባሰበ ይገኛል
፨ የጅማ ኦሮሞ ፦ ይህ የጠቅላይ ሚኒስትሩ የትውልድ አካባቢ ሲሆን በአመዛኙ ለብልፅግና ድጋፍ የሚሰጥ ነው።
ደቡብ ኢትዮጵያ ውስጥ ፦
፨ የደቡብ ኢትዮጵያ የፕሮቴስታንት አማኝ ማህበረሰብ ፦ በሃድያ እና በሌሎች የደቡብ ኢትዮጵያ አካባቢ ያለው የፕሮቴስታንት አማኝ ጠ/ሚሩ ፕሮቴስታንት ስለሆኑ እና ፓርቲው በብልፅግና ወንጌል አራማጆች እየተመራ ነው ብለው በማሰብ ድጋፍ እያደረጉለት ነው።
አማራ ክልል ውስጥ ፦
፨ ደቡብ ወሎ በዋናነት ደሴ ፣ ኮምቦልቻና ከሚሴ አካባቢ ያሉ ሙስሊሞች ፦ እነዚህ አካላት ፋኖን ከክርስትና ጋር በማያያዝ የሚፈሩና ብልፅግናን የሚደግፉ ናቸው።
፨ ወልቃይት ጠገዴ ፦ እዚህ አካባቢ የወልቃይት ህዝብ በብልፅግና ዘመን በአንፃራዊነት ራሴን በራሴ ማስተዳደር ችያለሁ በሚልና በቀጣይም ከህወሓት ስጋት አለብኝ በሚል እምነት ለብልፅግና ድጋፍ እየሰጠ ያለ ነው።
ሶማሌ ክልል ፦
፨ የክልሉ ፕሬዝዳንት አንፃራዊ መረጋጋትና ልማት ለማምጣት ስለሞከረ ከተወሰኑ ጎሳዎች ውጭ በአመዛኙ ለብልፅግና ድጋፍ ያደርጋል።
2. የብልፅግና ተቀዋሚዎች ማህበራዊ መሰረት የት ነው?
ኦሮሚያ ክልል ፦
፨ አርሲ ፣ ሐረርጌና ባሌ ፦ እዚህ አካባቢ ያለው በአብዛኛው ሙስሊም ኦሮሞ ከበፊትም የነ ጃዋር ጠንካራ ህዝባዊ መሰረት ነው። በብልፅግና የረባ የፖለቲካ ስልጣንም ሆነ የኢኮኖሚ ተጠቃሚነት አላገኘንም ብሎ ያስባል።
፨ ወለጋ ፦ ይህ አስቀድሞ የኦነግ ጠንካራ ቀጠና ሲሆን አሁን ላይም የኦላ ማህበራዊ ድጋፍ መሰረት ነው።
አማራ ክልል ፦
የፋኖ ትጥቅ የሚደረግበት አብዛኛው የገጠር ቀበሌ ከብልፅግና ቁጥጥር ውጭ የሆነበት ክልል ነው።
፨ ጎጃም ፦ ሙሉ በሙሉ በሚባል ደረጃ ብልፅግናን የሚቃወም ነው። የፋኖ የፖለቲካ አስኳል ነው ተብሎ ይታመናል።
፨ ወሎ (ቤተ አማራ) ፦ ከላይ ከተጠቀሱት የወሎ አካባቢዎች ውጭ አብዛኛው የቤተ አማራ አካባቢ ብልፅግናን አይደግፍም ። ጠንካራ የፋኖ ሰራዊት ያለበትና የፋኖ ወታደራዊ እምብርት ተደርጎ ይወሰዳል።
፨ ጎንደር ፦ ከወልቃይት ውጭ አብዛኛው የጎንደር አካባቢ ብልፅግናን የሚቃወም ነው። በቁጥር ደረጃ ብዙ የፋኖ ሰራዊት ያለበት ነው።
፨ ሸዋ ፦ አብዛኛው የሸዋ አማራ የብልፅግና ተቃዋሚ ነው። በመንዝ አካባቢም ጠንካራ የፋኖ ሀይል አለ።
ትግራይ ክልል ፦
፨ ሙሉ በሙሉ የብልጽግና ተቃዋሚ ነው። ህወሓትን በሚመለከት በድጋፍና በተቃውሞ የተሰለፈ አቋም በአካባቢው ልሂቅን በኩል ሲንፀባረቅ ይታያል። ቲዲፍን ግን በአብዛኛው ይደግፉታል።
ጋምቤላ እና ቤንሻንጉል ፦
፨ የተለያዩ የትጥቅ ትግል እንቅስቃሴ ያለባቸው አካባቢዎች ናቸው።
አፋር ፦
፨ የተወሰኑ የተቃውሞ ድምፆች ይሰማሉ።
ደቡብ ኢትዮጵያ ፦
፨ ከፕሮቴስታንቶች ውጭ በአመዛኙ የብልጽግና ተቃዋሚ ነው።
የኦርቶዶክስ አማኞች ፦
፨ አብዛኛው የኦርቶዶክስ አማኝ የብልፅግና ተቃዋሚ ነው።
ለመደምደም ያህል ፦
ብልፅግና በአማራ ብልፅግና ጥፋት ሚዛኑን ስቶ በትርክት ደረጃ ወደ ኦሮሞ ተረኛ መንግስትነት ቢቀየርም በተጨባጭ ግን ሙሉውን የኦሮሞ ማህበረሰብ በደጋፊነት ማሰለፍ አልቻለም ። በሌላ በኩል ከደቡብ ኢትዮጵያ የፕሮቴስታንት አማኞች አካባቢ ድጋፍ ለማግኘት ሲሞክር የሚታይ ሲሆን በአማራ ክልል ውስጥ ደግሞ ከሙስሊሙ ድጋፍ ለማግኘት እየሰራ ይገኛል ።
ብልፅግና የብሔርና የሀይማኖት አሰላለፍን እየቀላቀለ አሁን በሚከተለው “የኦሮሞ ተረኛ መንግስት” የሚል ዋልታ ረገጥ የፖለቲካ መስመር ሀገሪቱን አረጋግቶ ለመምራት አይችልም ። ሁሉንም የኢትዮጵያ ብሔሮች እና የእምነት ተከታዮች በዜግነትና በእኩልነት የማያስተናግድ ስርዓተ ማህበር አሁን ያለውን የርስበርስ ጦርነት ከማባባስ እና የበለጠ እልቂት ከመፍጠር የዘለለ ውጤት አይኖረውም ።
