ዶ/ር ወርቅነህ አሻርቅ አል አውሳር ከተባለ ሚዲያ ጋር ባደረጉት ቃለ ምልልስ፣ ግብፅ ምላሽ እንድትሰጣት ኢትዮጵያ መጠየቋን አረጋግጠው እስካሁን የተሰጠ ምላሽ አለመኖሩን አስታውቀዋል፡፡

በቅርቡ በተለያዩ የአገሪቱ አካባቢዎች ተከስቶ ከነበረው ተቃውሞና አመፅ ጀርባ የግብፅ ተቋማት እጅ እንዳለበት የተለያዩ መረጃዎች መውጣታቸው ይታወሳል፡፡ በተለይ በኦሮሚያ ክልል የተከሰተውን ተቃውሞና አመፅ የሚያበረታታ ቪዲዮ ላይ የኦነግና የግብፅ ባንዲራዎች፣ እንዲሁም ግብፃዊያን መታየታቸው ከፍተኛ የመነጋገሪያ አጀንዳ እንደነበር አይዘነጋም፡፡

የግብፅ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አህመድ አቡ ዘይድ ግብፅ ምላሿን በአስቸኳይ እንደምትሰጥ ለግብፅ ሚዲያዎች አስታውቀዋል፡፡

ግብፅና ኢትዮጵያ በዓባይ ውኃ ጉዳይ ለዘመናት የቆየ ልዩነት ያላቸው ሲሆን፣ ከዚሁ ጋር በተያያዘ የታላቁ ህዳሴ ግድብ ወደ ግብፅ የሚፈሰውን የውኃ መጠን በመቀነስ ከፍተኛ ጉዳት ያስከትልብኛል በማለት ተቃውሞ ስታሰማ መቆየቷም ይታወሳል፡፡

ይሁንና የተለያዩ ድርድሮች ሲካሄዱ ከቆዩ በኋላ ባለፈው መጋቢት 2007 ዓ.ም. ከሱዳን ጋር በመሆን በፈረሙት የሦስትዮሽ የመግባቢያ ሰነድ ግብፅ ለግድቡ ዕውቅና መስጠቷ አይዘነጋም፡፡

ግብፅ ግድቡ እንዳይገነባ የተለያዩ ተፅዕኖዎችን ስትፈጥር ብትቆይም፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ግን ግድቡ የሚፈጥረው ተፅዕኖ ላይ አተኩራለች፡፡ ሦስቱ አገሮች የግድቡ ተፅዕኖ እንዲጠና ባደረጉት የቅርብ ጊዜ ስምምነት መሠረት ጥናቱን ለማካሄድ የተመረጡት ሁለቱ የፈረንሣይ ኩባንያዎች ቢአርኤልና አርቴሌሊያ በቅርቡ ጥናቱን እንደሚጀምሩ ተገልጿል፡፡ ግብፅ ጥናቱ ቶሎ ላለመጀመሩ ኢትዮጵያን ተጠያቂ ታደርጋለች፡፡ ኢትዮጵያ ግን አትቀበለውም፡፡

ግብፅ ፊት ለፊት በሚደረጉ ድርድሮች ምክንያታዊ ሆና በመቅረብ ከጀርባ ተቃዋሚ ቡድኖችን  በመርዳት ኢትዮጵያ እንዳትረጋጋ ትሠራለች ተብላ ትተቻለች፡፡ ግድቡ ለግብፅ ጭምር ዘርፈ ብዙ ጥቅሞች አሉት የሚሉት ነፃና ገለልተኛ የፖለቲካ ተንታኞች ግን፣ በኢትዮጵያ አለመረጋጋት ግብፅ ዘላቂ ጥቅሟን ማስከበር ስለማትችል ከኢትዮጵያና ከሌሎች የተፋሰሱ አገሮች ጋር ከልቧ በትብብር እንድትሠራ ያሳስባሉ፡፡