By ሳተናውJanuary 3, 2017 07:09
  • ከሰሞኑ አዲስ የፉርኖ ዱቄት እጥረት ተከስቷል፡፡
  • ባለሱቆች ስኳር የሚሸጡለትን ዜጋ ሙሉ አድራሻ እንዲይዙ ተነግሯቸዋል
  • የቀበሌ መታወቂያ ወይም ፓስፖርት የሌላቸው ዜጎች ስኳር መግዛት አይችሉም


ዋዜማ ራዲዮ- ከአውድ ዓመት መቃረብ ጋር ተያይዞ ለስኳርና ዘይት ግዢ በየወረዳው የሚገኙ የሸማች ማኅበራት ሱቆች ታይቶ የማይታወቅ ረዣዥም ሰልፎችን እያስተናገዱ ይገኛሉ፡፡ በአንዳንዶቹ የኅብረት ሱቆች ወረፋ ከሌሊት ጀምሮ መያዝ እየተለመደ መጥቷል፡፡ በጎላ ሚካኤል ሸማቾች ማኅበር ሰልፍ ከሌሊቱ 11 ሰዓት የሚጀምር ሲኾን የሸማቾች ማኅበር ሱቅ የሚከፈተው ደግሞ ከጠዋቱ 2፡30 በኋላ ነው፡፡

ስኳር ከሸማቾች ማኅበር ዉጭ ባለ ጥቁር ገበያ እስከ 26 ብር በኪሎ ይሸጣል፡፡ ኾኖም ባለሱቆች በዚህ ዋጋ መሸጣቸው በሕግ እንደሚያስጠይቃቸው ስለሚረዱ ለማያውቁት ደንበኛ በየትኛውም ዉድ ዋጋ ስኳር ለመሸጥ አይፈቅዱም፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ደግሞ ባለሱቆች ስኳር የሸጡለትን ሰው ሙሉ ስም፣ የቤት ቁጥርና ሙሉ የስልክ አድራሻውን መዝግበው እንዲይዙ ከወረዳ ኃላፊዎችና ደንብ አስከባሪዎች ታዘናል ብለዋል፡፡

በአሁኑ ሰዓት በየወረዳው ከ5 እስከ 10 የሸማች ማኅበራት ሱቆች ቢኖሩም ከስኳር ፈላጊው ዜጋ ቁጥር ጋር ሊመጣጠኑ አልቻሉም፡፡