Dr. Fikre Tolesas’s book comments…
የአማራውንና የኦሮሞውን ሕዝብ እውነተኛ ወንድማማችነት በማስረጃ ለማሳየት ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶለሳ በቅርብ ጊዜ ባሳተሙት ‘የታሪክ መጽሐፍ’ ላይ አንጋፋ ፕሮፌሰሮችና ሌሎችም ነቀፋ እያቀረቡበት ነው። ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶለሳም ሥራቸው (ከ40 በላይ በሚሆኑ ዋቢ መጻሕፍት የተደገፈ)፣ ለአምስት አመታት ያህል የተደከመበት ጥናታዊ ሥራ መሆኑን በመግለጽ ሽንጣቸውን ገትረው እየተከራከሩ ነው። እንዲያውም ካንዳንድ ፕሮፌሰሮች ጋር የሚደረገው የጽሑፍ ልውውጥ፣ ለመማማርና ለመተራረም ከሚደረግ ትምህርታዊ (academic) ትችት አልፎ ወደተራ ውርክብ ተለውጧል። ደስ አይልም።
እድል አጋጥሞኝ እኔም የፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶለሳን መጽሐፍ አንብቤዋለሁ። መጽሐፉን አንብቤ ስጨርስ (ከመጽሐፉ በስተኋላ) በዐይነ ህሊናዬ ለማየት የቻልኩት የፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶሎሳን የሚንቦገቦግ የሀገር ፍቅር ነው። ፕሮፌሰር ፍቅሬ ቶለሳ ኢትዮጵያዊያን ሁሉ በሰላምና በእኩልነት አብረው እንዲኖሩ ያላቸው ጉጉት በመጽሐፋቸው ውስጥ ይታያል። ሀገራቸውን ስለሚወዱ ሰበብ እየፈለጉ የኢትዮጵያን ታሪክ (በተለይ የጥንቱን ታሪክ) በኃያልነትም፣ በቆዳ ስፋትም ከዓለም ሀገሮች ሁሉ የላቀ አርገው ያጐኑታል። ኦሮሞው ሕዝብ (በባህል፣ በኢኮኖሚ፣ በውትድርና፣ ባመራር፣ ወ.ዘ.ተ.) ለኢትዮጵያ ከፍተኛ አስተዋጽዖ ሲያደርግ የኖረ መሆኑን በሰፊው ያብራራሉ። አማራው ሕዝብም በኢኮኖሚው መስክም ሆነ በቋንቋና በሃይማኖቱ ጨቋኝ ሁኖ እንደማያውቅ ያትታሉ። ጽሐፊው ሁለቱም ጐሳዎች (አማራና ኦሮሞ) ባንድ ላይ ለሀገራቸው የየበኩላቸውን አስተዋጽዖ ማበርከታቸውን ለማሳየት ጥረዋል። ባሁኑ ጊዜ (አንዳንድ የጐሳ መሪዎች ነን የሚሉ) በዳግማዊ አፄ ምኒልክ ላይ የሚሰነዘሩትን የቅኝ ገዥነትና የጨካኝነት ክስ አጥብቀው ያስተባብላሉ።