01/19/2017

ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው

ለሀገር ጥቅም ሲባል ተቃዋሚዎች ከወያኔ ጋር የሚያደርጉትን ድርድር

በአስቸኳይ ያቁሙ!


ወያኔ ከገባበት ጭንቅ ለመውጣት ያልሞከረው መላ የለም ማለት ይቻላል፡፡ ጥልቅ ተሐድሶ በማለት መታደሳችንን ያሳይልናል!” ያሉትን አታላይና ደላይ የተለያዩ የብዙኃን መገናኛ ዝግጅቶችና ከሕዝብ ጋር የተደረጉ ውይይቶችን፣ የደሞዝ ጭማሪን፣ አቅምና ደጋፊ ለሌላቸው ወገኖች የመመገቢያ ጣቢያዎችን በማደራጀት ለመመገብ መታሰቡን፣ከተቃዋሚዎች ጋር ድርድርን፣ አሁን ደግሞ በመጨረሻ አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝንና አቶ ሽፈራው ሽጉጤን ተዋናይ በማድረግ አቶ ኃይለማርያምን ከብአዴን ጋር አቶ ሽፈራውን ደግሞ ከሕወሀት ጋር በማሰለፍ አሥጊና የተጋጋለ ሽኩቻ ያለ በማስመሰል ሕዝቡ በራሱ እያደረገው ያለውን ትግል ትቶ ይሄ የተጋጋለ የተባለውን ሽኩቻ ይገላግለናን!” ብሎ ተስፋ አድርጎ እንዲጠብቅ ለማድረግ የተፈጠረ የውሸት የፀብ ድራማ (ትዕይንተ ኩነት) ደርሰው እያራገቡት ይገኛሉ፡፡

ይህ የውሸት ፀብ ሕዝቡ እውነት መስሎት እያደረገ ያለውን ተቃውሞና ትግል ትቶ የዚህን የውሸት ፀብ ውጤት እንዲጠባበቅ በማድረግ እያደረገ ካለው ተቃውሞና ትግል እንዲወጣ እንዲርቅ እንዲተው ለማድረግ የተፈጠረ መላ መሆኑን የሚያረጋግጠው 1. ይሄ አለ የተባለውን የተጋጋለ ሽኩቻ ዜናን በተመሳሳይ ሰዓት በማኅበራዊ የብዙኃን መገናኛው ይፋ ያደረጉት የወያኔ ካድሬዎችና ደጋፊዎች መሆናቸው ሲሆን 2. የሚወሩት የሽኩቻው ድርጊቶች ለአቶ ኃይለማርያምና ለአቶ ሽፈራው የተጋነነና ፈጽሞ የማይመስል አቅም የሰጡ መሆኑ ወዘተረፈ. ናቸው፡፡
እንግዲህ ወያኔ ከገጠመው ሕዝባዊ ዐመፅ፣ እምቢተኝነትና ተቃውሞ ለማምለጥ ለመትረፍ በሚያደርገው መንፈራገጥ እነኝህንና እነኝህን የመሳሰሉ የማስመሰል ተግባራትን እየፈጸመ ይገኛል፡፡ በእነኚህ የወያኔ የጭንቅ ጊዜ የማምለጫ ዘዴዎች ተስፋ የጣለ ዜጋ ቢኖር ከይቅርታ ጋር የመጨረሻ ቂል መሆኑን ልነግረው እወዳለሁ፡፡

ከዚህ ቀደም በተደጋጋሚ እንደገለጽኩት ወያኔ ተገዶ ተሸንፎ ካልሆነ በስተቀር በሰላማዊ የትግል አማራጮች ሥልጣንን እንዳይለቅ እንዳያስረክብ ሦስት ዋና ዋና ጉዳዮች ይከለክሉታል

1. የሚከተለው ርዕዮተዓለም፡፡ የወያኔ ርዕዮተዓለም መሠረት ያደረገው ጎሳን ነው፡፡ ርዕዮተዓለምን ጎሳ ላይመመሥረት ከባድ ድንቁርና ነው፡፡ ምክንያቱም ጎሳ ወይም ብሔረሰብ ሐሳባዊ ነው፡፡ የሰው ልጆች ምንጫቸው አንድ በመሆኑ አንዱ ከሌላው የተለየ ደምና የተለየ የሰውነት ዋጋ ይኖረው ይመስል ከጊዜ በኋላ ተጨባጭነት በሌለው ምክንያት አንድ ቋንቋና ባሕል ያለውን ሕዝብ ሁሉ በጎሳ መክፈል ሐሳባዊ እንጅ ተጨባጭ ባለመሆኑ ነው ርዕዮተዓለምን ጎሳ ወይም ብሔረሰብ ላይ መመሠረት ድንቁርናና ኋላቀርነት የሚሆነው፡፡ ወያኔ ርዕዮተዓለሙን ጎሳ ላይ በመመሥረቱ ምክንያት ሀገርንና የኢትዮጵያን ሕዝብ ቅድሚያ ትኩረት ነፍጓቸዋል፣ እንዲነፈጋቸውም አድርጓል፡፡


በወያኔ የአገዛዝ ዘመን ወያኔ የጎሳውን ጥቅም ለማስከበር ለማስጠበቅ ሲል በርካታ ሀገርንና ሕዝብን የሚጎዱ ነገሮች ተፈጽሟል፣ የራሱና የጎሳው ጥቅም የሚጎዳ መስሎ ሲታየው በርካታ ሊጠበቁ ሊከበሩ የሚገባቸውን የሀገርንና የሕዝቧን ጥቅሞች እንዳይሆኑ አድርጓቸዋል፣ አጥፍቷቸዋል፣ ጎድቷቸዋል፣ አስቀርቷቸዋል፡፡

ይህ ርዕዮተዓለሙ ወያኔን የሀገርንና የሕዝቧን ጥቅም ካስቀደሙ ሀገር አቀፍ የፖለቲካ ፓርቲዎች (የእምነተ አሥተዳደር ቡድኖች) ጋር በአገዛዝ ዘመኑ ሁሉ በምን ጉዳይ ላይ እንዳይስማማና እንዳይግባባ አድርጎት ቆይቷል፡፡ ወያኔ ከገጠመው ጭንቅ ለመውጣት አታሎ ለማለፍ አስመስሎ ይጫወት ይሆናል እንጅ ርዕዮተዓለሙ በተለይም ሀገር አቀፍ ከሆኑ ፓርቺዎች (ቡድኖች) ጋር በምንም ጉዳይ ላይ እንዲግባባ ፈጽሞ የሚፈቅድለት አይደለም፡፡

2. ዕኩይ ተፈጥሮው፡፡ ወያኔ የአጋንንት እንጅ የሰው ተፈጥሮ የለውም፡፡ ይህ ዕኩይ ተፈጥሮው ነው ወያኔን የፖለቲካ ደንቆሮና ሀገርን ለመምራት የማይመጥን ያደረገው፡፡ ሀገርን እመራለሁ ከሚል አካል በፍጹም በማይጠበቅ መልኩ በመቃብራችን ላይ ካልሆነ በስተቀር!” የሚል አመክንዮን (logic) እና በገዥ ሐሳብ በምክንያት የመመሥረትን በጎ ፈቃድ (Rationality) አንቅሮ ተፍቶ ባዶ ግትርነትን የነገሮች ሁሉ መቋጫው እንዲያደርግ ያደረገው ዕኩይ ተፈጥሮው ነው፡፡ ወያኔ በተፈጥሮው እንዲህ ዓይነት እስከሆነ ጊዜ ድረስ ከገጠመው ጭንቅ ለማምለጥ በማስመሰል ሊጫወት ይችል ይሆናል እንጅ ከልቡ ትርጉም ያለው ወይም መሠረታዊ ለውጥ ሊያስገኝ በሚያስችል መልኩ የሚያደርገው አንዳችም ነገር አይኖርም፡፡

3. መቸም ጊዜ ቢሆን የሕግ የበላይነት መረጋገጡ የግድ ነውና ወያኔ በሀገርና በሕዝብ ላይ የፈጸማቸው ክህደቶች፣ ኢሰብአዊ አረመኔያዊ ግፎችና በደሎች ሥልጣን ባስረከበ ማግሥት እያሳነቀ ለፍርድ እንደሚያቀርበው ጠቅቆ ማወቁ የፈጠረበት ሥጋት የሚሉት ናቸው፡፡ በእነኝህ ምክንያቶች ወያኔ በምንም ተአምር ሥልጣን ከሱ እጅ ወጥቶ ወደ ሌላ አካል እንዲተላለፍ አይፈቅድም፣ አይፈልግም እንጅ እሽ!” ብሎ ላስረክብ ተረከቡኝ!”ቢል እንኳ ከወያኔ ጋር በዚህ መልኩ በሰላም መለያየት የሀገርንና የሕዝብን ጥቅም በእጅጉ የሚጎዳ በመሆኑ ተቃዋሚ ነን የሚሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሁሉ ድርድር ያሉትን ጨዋታ በአስቸኳይ እንዲያቆሙ በግሌ እጠይቃለሁ!

ወያኔ በኃይል መወገድ ይኖርበታል እንጅ ከሱ ጋር በሰላም መለያየቱ ለሀገርና ለሕዝቧ ጥቅም የማያዋጣና በከፍተኛ ደረጃ ጎጅ የሚሆንበት ምክንያት አስቀድሜ ከዓመታት በፊት እንደገለጽኩት ወያኔ ሥልጣንን በሕዝብ ይሁንታና ምርጫ ሳይሆን በኃይል እንደመያዙና ሲጀመር ጀምሮ በኢትዮጵያ ሕዝብ እጅግ የተጠላ የማይፈለግ እንደመሆኑ መጠን እንደ አሰብንና ባድሜን ለሸአቢያ አሳልፎ የሰጠበት፣ ከጎንደር እስከ ጋምቤላ የሚደርሰውን ሰፊ የሀገር ግማድ መሬት ለሱዳን አሳልፎ የሰጠበት፣ የዓባይን ወንዝ ለመስኖ መጠቀምን የሚከለክል ስምምነት ከግብጽ ጋር ያደረገበትን የመሳሰሉ የሀገርንና የሕዝብን ብሔራዊና ሉዓላዊ ጥቅሞች አሳልፎ የሰጠባቸው በ26 ዓመታቱ የአገዛዝ ዘመኑ የተፈራረማቸው ውሎችና ስምምነቶች የኢትዮጵያ ሕዝብ ውክልና፣ ይሁንታና ዕውቅና ሳይኖረው፣ ሳይሰጠው፣ ሳያገኝ
በክህደትና በማንአለብኝነት የፈጸማቸው ሕገወጥ ውሎችንና ስምምነቶች ስለሆኑና የኢትዮጵያ ሕዝብ ዕውቅና፣ ውክልናና ይሁንታ ባልሰጠውና እራሱን በኃይል ባስቀመጠው አካል ለተፈረሙ የሀገርንና የሕዝቧን ብሔራዊና ሉዓላዊ ጥቅሞች አሳልፈው ለሰጡ ውሎችና ስምምነቶች የመገዛት ግዴታ ስለሌለበትና ሊኖርበትም ስለማይችል እነኝህን ክህደት  የተፈጸመባቸውን ውሎችና ስምምነቶች ወዳቂ ወይም ቀሪ ማድረግና ሁኔታዎችን የሀገርና የሕዝብ ብሔራዊ ጥቅምና ሉዓላዊነት ለማስከበር ወደሚቻልበት ሁኔታ መመለስ የምንችልበትን መብትና ፖለቲካዊ ምኅዳር ማግኘት ወይም መፍጠር የምንችለው ወያኔን በገባበት ሁኔታ ቀጥቅጠን በኃይል ካስወገድነው፣ ወደመቃብሩ ካወረድነው ብቻና ብቻ ነው፡፡

በመሆኑም ለሀገርና ለሕዝቧ ሉዓላዊና ብሔራዊ ጥቅሞቻችን ሲባል ከወያኔ ጋር ድርድር እናደርጋለን የምትሉ የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ ብሔራዊ ዕርቅ ጠያቂ የሀገር ሽማግሌዎችና የእምነት አባቶች ሁሉ ከድርጊቶቻቹህ ታቅባቹህ ወያኔ በኃይል በሚወገድበት ጉዳይ ላይ ትረባረቡ ዘንድ እንደ ዜጋ አበክሬ ማሳሰብ እወዳለሁ! ለግል ጥቅም በመጓጓት፣ ሊደርስ የሚችልን የሀገርና የሕዝብን ዘላቂና ቋሚ ከፍተኛ ጉዳት ከምንም ባለመቁጠር ድርድራቹህንና ስምምነታቹህን ከወያኔ ጋር ቀጥላቹህ ሰላማዊ የሥልጣን ሽግግር እንዲደረግ ብታደርጉ ግን ይህ ድርጊታቹህ ሀገራችንን በወያኔ ያጣቻቸውን
ብሔራዊና ሉዓላዊ ጥቅሞች እንዳጣች ትቅር!” ብሎ ማለት ስለሆነ በታሪክና በኢትዮጵያ ሕዝብ ፊት ከወያኔ በከፋ 
መልኩ ተጠያቂ መሆናቹህን እንድታውቁ!

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!! ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!

ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው

amsalugkidan@gmail.com