By ሳተናው

March 31, 2017 14:27

የደሃ ቁርጥ ብቻ ሳትሆን የቁርጥ ቀን ምግብ የሆነችው ቲማቲም አዲሳባ ላይ ዋጋዋ አልቅመስ ብሏል። አንድ ኪሎ እሰከ ሃምሳ ብር እየተሸመተች እና እያልተሸመተች ነው። በተለይ ለኦርቶዶክስ ክርስትና እምነት ተከታዮች በዚህን ወቅት ቲማቲም እንዲህ ቅብርር ማለቷ የሚያቀባብር አይደለም።

ዛሬ የገባሁበት የሸመታ አዳራሽ ውስጥ ቲማቲም ተኮልኩሎ ሳገኘው ቆይማ ላዲሳባ ህዝብ ልበቀልለት ብዬ በርከት አድርጌ ገዛሁ። ሂሳቡን ሳየው አንዱ ኪሎ አንድ ፓውንድ ከ ስድሳ ሳንቲም ነው። ይሄኔ የሃምሳ ብሩን የአዲሳባ አቻውን እያሰብኩ… ትካዜ ውስጥ ከመግባቴ በፊት እስቲ ፓውንዱን ወደ ኢትዮጵያ ብር ልቀይረው ብዬ መታሁት። በዛሬው ገበያ 1 ፓውንድ በ 28.47 የኢትዮጵያ ብር ይመነዘራል። እንግዲህ 1.6 ሲባዛ በ 28.47 አርባ ሁለት ብር ከ ሃምሳ ያልፋል። ስለዚህ የአዲሳባው ቲማቲም ከ አርባ እስከ ሃምሳ ብር ግዙኝ የሚለው አለም አቀፍ ገበያውን አጥንቶ ነው ማለት ነው ስል አሰብኩ… አስቤም እንደዛ ከሆነማ ችግር የለም ብዬ ልቀጥል ስል… ችግር እማ እለ ብሎ ደሞዝ ከፊት ለፊቴ ገጭ አለ።

ደሞዝ እዚህ ሃገር አንድ የቀን ሰራተኛ (ሙያተኛ ያልሆነ ሰው) በሰዓት 7.2 ይከፈለዋል። በቀን ስምንት ሰዓት ቢሰራ፤ ሃምሳ ሰባት ፓውንድ ይከፈለዋል ማለት ነው፡፤ ከዝች ላይ 1.6 ቲማቲም ቢገዛ ምንም አይደል።

አዲሳባ አንድ የቀን ሰራተኛ (ሙያተኛ ያልሆነ) በቀን ምን ያክል ይከፈለዋል ? ወዳጆቼ እንደነገሩኝ በአሁኑ ሰዓት በአማካይ 85 ብር ይከፈለዋል። እና ከዚች ክፍያ አንድ ኪሎ ቲማቲም ሲገዛ ቢፈልግ የቀን ውሎውን ደሞዝ ግማሹን መክፈል ሊኖርበት ነው።

በል እንዲህ እያልክ ሰዉን ለሰደት አነሳሳው የሚል አስተያየት አልቀበልም)

መንግስት ግን ሰዎች በሃገራቸው እንዲኖሩ ገበያው ከደምወዛቸው ጋር እንዲመጣጠን የማድረግ ሃላፊነት አለበት!

አልሰማም ካለ ህዝብ ”ኡ ኡ” ብሎ መጮህ አለበት! (አንተ ውጪ ሃገር ተቀምጠህ ሰውን ጩሁ ትላለህ አይደል… መባል አለ ደሞ) እሺ በቃ መንግስት አልሰማም ካለ ህዝቡ ቲማቲም የመብላት ባህሉን ማቆም አለበት። ወይ ደግሞ ልክ እንደ ፓርላማው ቲማቲም በተወካዮች አማካይነት እየበላን እንኑር ማለት ነው!?

የጨነቀ ነገር ሆነብን እኮ!