May 12, 2017 06:40 am By Editor

የ“ፍትህ” ወይስ የጨለማ ሳምንት?
(ርዕሰ አንቀጽ)
“ገንዘብ ሲናገር ፍትህ ጸጥ ይላል!” ይህ የተጻፈው በአንድ የጎንደር እስር ቤት ውስጥ ነው። የተጻፈው በግድግዳ ላይ ሲሆን በብዕር ወይም በቀለም አይደለም። ፍትህ ከተጓደለባቸው አንዱ የእጁን ጣት በመብጣጥ በደሙ ነው። ፍትህ የተዛባባቸው ይህንኑ አባባል ልክ እስር ቤት እንደገቡ ይሳለሙታል። በብዙ የአገሪቱ ማጎሪያዎች ውስጥ ተመሳሳይ ስሜት ገላጭ ሃረጎች ይጻፋሉ። ፍትህን አደባባይ ሰቅለው በምስኪኖች ህይወት ለሚጫወቱ ይህ ሁሉ ስላቅ ነው። ፍትህን አደባባይ ሰቅለዋት፣ በፍትህ ስም እየማሉ በድግስ ሊያሽካኩ ይወዳሉ።
ፍትህ የዜጎች ሁለንተናዊ ህይወታቸው ትርጉም የሚያገኝበት ውድ ጉዳይ ነው። ይህንን ሃቅ የበረሃው አባዜው አልለቅ ያለው ህወሃት ጥንቅቆ ያውቀዋል። ሊክደውም አይችልም። ለዚህም ነው “ህገ መንግስት፣ ህግ፣ አዋጅ፣ የሰብዓዊ መብት፣ የብሔር ብሔረሰቦች መብት…” እያለ ህግ ሲያረቅና አዋጅ ሲያመርት የሚኖረው። በተግባር የሚታየው ግን ኢትዮጵያ ውስጥ “ፍትህ” የህወሓትን ልዕለ ሥልጣን ለመጠበቅ የተቋቋመ መሳሪያ፣ በ“ህግ” እና “አዋጅ” ስም የጠሉትን መምቻ፣ የተቃውሞ ድምጽ ማፈኛ መሆኑ ነው። ኢ-ፍትሐዊነት በ“ፍትህ” ካባ ጀቡነው የዓይነ ደረቅ ጨዋታ መጫወት ይሏል ይህ ነው። ይህ እንደ ሚዲያ እኛ የምንለው ሳይሆን ህዝብ በአደባባይ በየቀኑ የሚታዘበው እውነት ነው።
ላለፉት ሃያ ስድስት ዓመታት ዘውጋዊ መድሎንና የዘር ማጽዳትን የተገበረ፣ ያለተጠያቂነት የአገሪቱን የፍትህ ሥርዓት በፓርቲ ፖለቲካ ታማኝነት የጨፈለቀ፣ ሙስናን በአደባባይ ያነገሰ፣ በገዛ ዜጎቹ ላይ ጦርነት አውጆ በሺህ የሚቆጠሩ ንፁሃንን ከገጠር እስከ ከተማ የረሸነ፣ የአካል ጉዳተኛ ያደረገ፣ በአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስም በአሥር ሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎችን በጅምላ ቀፍድዶ የሚያሰቃይ፣ በእስረኞች ላይ ዘግናኝ የምርመራ ወንጀል የሚፈጽም፣ አውሬያዊነት የተጠናወተው አገዛዝ፤ . . . አገሪቱን በኦፊሴል ወደ ወታደራዊ የአፈና መዋቅር አሻግሯት ባለበት በዚህ ዘመን “የፍትህ ሳምንት” ለማክበር በሚል መጀመሩን የፕሮፓጋንዳ አታሞ በሚደልቅባቸው ሚዲያዎቹ አዋጅ እያስደለቀ ነው።
አገር እንድትበታተን የሚጋብዙ የፖለቲካ አጀንዳዎች በስትራቴጂ ደረጃ ቀርፆ የሚሰራው ህወሓት፤ ትግራይን እንደአገር እየሰራ፣ ዳሩን መሀል እያደረገ፤ መሀሉን እያፈረሰ ባለበት ሁኔታ “የህግ የበላይነት ለዘላቂ ሰላምና ለህዝቦች አንድነት” በሚል መሪ ቃል የዘንድሮውን የ“ፍትህ” በዓል (ከሚያዚያ 30 – ግንቦት 06) ማክበር ጀምሯል። በቀደመው ዓመትና በያዝነው ዓመት የመጀመሪያዎቹ ወራት በተነሳው ህዝባዊ ተቃውሞ ከአገዛዙ ቅልብ ወታደሮች በተተኮሱ ጥይቶች ጎዳናው ላይ የወደቁ ንፁሃን ዜጎች፣ ለአካል ጉዳት የተዳረጉ ወገኖች፣ በእስር የማቀቁና የሚማቅቁ ኢትዮጵያዊያን ፍትህ ባላገኙበት ሁኔታ አገዛዙ የሚያከብረው የ“ፍትህ” ሳምንት ለመከረኛው የኢትዮጵያ ህዝብ “የጨለማ ሳምንት ክብረ በዓል” ቢሆን ህወሃትን ይመጥነዋል። ለጠጣው ደምና ለበላቸው ንጹሃን ዜጎችም ደግ መታሰቢያም በሆነ ነበር።
እኛ እንደ ሚዲያ፣ ዜጎች እንደ ህዝብ የአንድ ሥርዓት ምቹነት መመዘኛው የፍትሃዊነት መኖር ወይም ያለመኖር ጉዳይ ስለመሆኑ አያከራክርም። አገርን የሚያስተዳድር መንግስት ካለ ፍትህ ከቶውንም ሊጓድል አይገባም። ቢጓደልም አሁን ባለበት ደረጃ ሊሆን አይችልም። ፍትህን ላልተገባ ወይም ለፖለቲካዊ ዓላማ ማዋል ከወንጀሎች ሁሉ የከፋው ወንጀል ነው። ህወሃት ይህንን እያደረገ ያለና ግብሩ ሁሉ ፍትህ ላይ ቆሞ የመደነስ በመሆኑ እንዲህ ያለውን የሚያበራ መሪ ቃል ተሸክሞ ህዝብ ፊት ስለ ፍትህ ሊናገር አይችልም። ሞራል የለውም እንጂ ስለ ፍትህ ሲያወራ ሃፍረት የጨው ዓምድ ባደረገው ነበር።
የሕጎችና አዋጆች መጽደቅ ዋናው ግብ የዜጎችን ደህንነት ለመጠበቅ ቢሆንም ከዚህ በተቃራኒው ሲተገበር መመልከት ለኢትዮጵያዊያን እንግዳ ክስተት አይደለም። በቁጥር የበዙ ኢትዮጵያዊያን ህግ እነርሱን ለማጥቃት እንጂ ለመከላከል እንዳልቆመ በውል ያውቃሉ። በተለይም ከመንግስታዊ “ክሶች” አኳያ “ህግ” የአገዛዙን ዕድሜ ለማራዘም መጠቀሚያ ሲሆን ማየት የፍትህ ሥርዓቱን መበስበስ አመላካች እንደሆነ በጽናት እናምናለን። ይህ እምነታችን ደግሞ በደፈናው ወይም በቅጽበት የመጣ ሳይሆን የህወሃት ግብር አስረግጦ ያስተማረን ነው።
የህግ የበላይነት ተጨፍልቆ ጥቂቶች ከህግ የበላይ ሲሆኑ መመልከትም የአንድን አገዛዝ ፍፃሜ አመላካች ነው። ከጥንቶቹ ገናና መንግስታት እስከ ቅርቦቹ ድረስ፣ አገዛዞች መውደቂያቸው ሲቃረብ የፍትህ ሥርዓታቸው የተበላሸ እንደነበር ታሪክ ይነግረናል። ከታላቁ የሮማውያን ግዛት ጀምሮ እስከ አረቡ የፀደይ አብዮት ድረስ የህዝብ ማዕበል ጠራርጎ የወሰዳቸው አምባገነን መንግስታት የአወዳደቃቸው መንስኤ የአገዛዙ ተጠቃሚዎችና አባላት ህግጋቱን ለገዛ (ግላዊና ቡድናዊ) ፍላጎታቸው በማዋላቸው ነው። የዘፈቀደ ጅምላ እስርና ግድያ መለያው የሆነው ህወሓት/ኢህአዴግ ከዚህ የተለየ ዕጣ እንደማይገጥመው ሳይታለም የተፈታ ጉዳይ ነው።
ከሩብ ክፍለ ዘመን የአገዛዙ ጉዞ የታየው እውነታም አገዛዙ “እታመንለታለሁ” በሚል ከሚመፃደቅበት “ሕገ – መንግስቱ” ላይ የተቀመጡትን ህጎች በአደባባይ ከመጣስ ጀምሮ በተለያዩ አዋጆች የገዛ ዜጎቹን እስከመበቀል ደርሷል። በምርጫ 97 ድንጋጤ ማግስት፣ የአገዛዙን ምሰሶ የነቀነቁትን ዘርፎች ለማሽመድመድ በሚል ያወጣቸው የተሻሻለው የፕሬስ አዋጅ፣ የፀረ-ሽብር አዋጅ፣ የበጎ አድራጎት (መያዶች) አዋጅ አተገባበር የአገሪቱን የፍትህ ስርዓት በማሽመድመድ ተጠቃሽ አዋጆች ናቸው።
እነዚህ አዋጆች በረቂቅ ደረጃ እንዳሉ በብዙ ምሁራንና ፖለቲከኞች እንደተገመተውም ተቃዋሚውን ኃይልና ሞጋቹን ማህበረሰብ ለማፈንና ለማዳከም በማጥቂያነት የተቀመሩ በመሆናቸው፣ ዛሬም ድረስ ያለ አንዳች ተጨባጭ ማስረጃ ከነዚህ የማጥቂያ አዋጆች ቀዳሚ የሆነው የፀረ ሽብር አዋጁ እየተጠቀሰባቸው ወደ አስከፊ እስር የሚወረወሩ ዜጎች በርክተዋል። ከሁሉም በላይ የከፋውና ዜጎችን የባይተዋርነት ስሜት ውስጥ የሚከተው ድርጊት፣ በተጠርጣሪነት በተያዙበት ሁኔታ ውስጥ ህጉ ያስቀመጠላቸውን መብቶች መነፈጋቸው ነው። የሽብርተኝነት ታፔላ እየተለጠፈባቸው ወደ እስር የሚጋዙ ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች፣ ሞጋች ወጣቶች፣ . . . ከመሰረታዊው በ48 ሰዓት ፍርድ ቤት የመቅረብ መብት አንስቶ እስከ ዋስትና መከልከል እንዲሁም የቤተሰብ፣ ወዳጅ፣ ዘመድ እንዲሁም በኃይማኖት አባትና በጠበቃ እንዳይጎበኙ ክልከላ ማድረግ፣ በእስር ቆይታ የከፋ አያያዝ እና በድብደባ ማሳመን የመሳሰሉ ከፍተኛ ኢ-ሰብዓዊ በደሎች ይፈፀሙባቸዋል። ከዚህ አልፎ ተርፎም ድራማዊ የሆኑ የሐሰት ምስክሮች ይዘጋጁባቸዋል። የካንጋሮው ፍርድ ቤት የሚቀርቡለትን “መንግስታዊ ክሶች” በሙሉ ከባባድ የፍርድ ውሳኔዎች በመስጠት ወደ ማጎሪያ ይወረውራቸዋል።
ቁጥሩ የበዛ ኢትዮጵያዊ ለፍትህ ተቋማትና አገልጋዮች ያለው አመኔታ ተሟጥጦ አልቋል። በእስከአሁኑ ተሞክሮ ህወሓት/ኢህአዴግ በወንጀል ጠርጥሮ ካሰራቸው ግለሰቦች መካከል በፍርድ ክርክር ሂደት ነፃ ተብሎ የተለቀቀ አንድም ኢትዮጵያዊ ዜጋ የለም። ከእስር ጀምሮ ያሉ የፍርድ ቤት ክርክሮች በህወሓት አቃቢያነ ህግ የበላይነት የሚደመደሙ ናቸው። “ተለቀቁ” ተብለው ሲፈቱም በተፈለገ ቀን ወደ እስር ቤት ለመክተት የሚያገለግል “ወንጀል” በአደራ ተቀምጦ ነው።
ህወሓት/ኢህአዴግ “አሸባሪ” ብሎ ያሰራቸው ግለሰቦች ፍትህ እናገኛለን ከሚሏቸው የፌዴራልም ሆነ ጠቅላይ ፍርድ ቤት የጥፋተኝነት ውሳኔ በቀላሉ ሲሰጥ ማየታቸው ከእነርሱ አልፎ ሌሎች ዜጎች በፍትህ ሥርዓቱ ላይ ያላቸው አመኔታ ወደዜሮ የወረደ እንዲሆን አድርጎታል።
ህወሓት/ኢህአዴግ “አሸባሪ” ብሎ ያሰራቸው ፖለቲከኞች፣ ጋዜጠኞች፣ ሞጋች የህብረተሰብ ክፍሎች፣ … የፍትህ ሥርዓቱን መበስበስ እየወቁ እንኳ ጠበቃ ከማቆምና ከመከራከር ሲሰንፉ አንመለከትም። እንዲህ ያለው ጉዳይ በዶ/ር መረራ፣ በቀለ ገርባ፣ ለወልቃይት የማንነት ጥያቄ አስተባባሪ የኮሚቴ አባላትና በመሰል የ“ሽብር ወንጀል” ለታሰሩ ዜጎች የተሰወረ እውነት ባይሆንም ጠበቃ የማቆም አስፈላጊነት የህወሓት/ኢህአዴግን ኢፍትሃዊነት በኢትዮጵያ የታሪክ ምዕራፍ በጉልህ መዝግቦ ለማስቀረት እንደሆነ የቀደሙት ግፉአን የፍርድ ሂደት የሚነግረን እውነት አለ።
አንደበተ ርትዑው ፖለቲከኛ፣ አንዷለም አራጌ የህወሓት/ኢህአዴግን ሃሳዊ “የሽብር ወንጀል የክስ ሂደት” ጠበቃ አቁሞ ሲከራከር ከቆየ በኋላ ለማመን በሚከብድ ፖለቲካዊ “የፍርድ ውሳኔ” የዕድሜ ልክ ፅኑ አስራት የተፈረደበት ዕለት፣ ከፍርዱ በፊት የፍርድ ማቅለያ ሃሳብ እንዳለው በካንጋሮው ፍርድ ቤት ሲጠየቅ “እኔን እዚህ ያቆመኝ የነፃነት ናፍቆት ነው። በኢትዮጵያ ፍርድ ቤቶች ፍትህን ለምኜ ስነፈግ ይሄ የመጀመሪያዬ አይደለም። ከሳሾቼ እንድጠጣው የሚፈልጉትን የግፍ ፅዋ በፀጋ ከመጠጣት ውጭ ባልፈፀምኩት ወንጀል ማቅለያ የመጠየቅን አማራጭ ህሊናዬ ስላልተቀበለው አልጠይቅም…” ማለቱን እናስታውሳለን። የአንዷለምን ምርጫ የሚጋሩ ብዙ ግፉአን ፍርደኞች የኢትዮጵያን እስር ቤቶች አጣብበውታል።
እንደ እኛ እምነት የኢትዮጵያ የፍትህ ሥርዓት ሲበዛ በስብሷል። በጉልበተኛ ገዥዎች መዳፍ ስር የወደቀው የፍትህ ሥርዓት አገዛዙ ሥልጣን ላይ እስካለ ድረስ ከቶውንም ሊቃና አይችልም። የፍትህ እጦት አመጽ መውለዱ አይቀሬ ነበርና በቀደመው ዓመት የተነሳው ህዝባዊ ተቃውሞ ዛሬ ላይ በረድ ያለ ቢመስልም በደፈጣ የጦር መሳሪያ ጥቃት የታጀበ አገዛዛዊ ውድመት ወደ ማድረስ ተሸጋግሯል።
ለኢትዮጵያ የሚበጀው ሰላማዊ ሽግግር መሆኑን አጥብቀን እናምናለን። ደርግ ኢ-ፍትሃዊ ነው በሚል “ብሶት ወለደኝ” ያለው የያኔው የደፈጣ ተዋጊ ቡድን ዛሬ ወንበሩ ላይ ሲቀመጥ ከጣለው አገዛዝ በላይ የከፋ ሆኖ ተገኝቷል። የደርግን መደባዊ ጭፍጨፋ ወደ ዘውጋዊ ጭፍጨፋና የዘር ማጽዳት ደረጃ ያሻገረው ህወሓት ኢ-ፍትሃዊነትን በፍትህ ካባ ሸፍኖ የገዛ ዜጎቹን መበቀያ መሳሪያ አድርጎታል።
የዘፈቀደ ግድያና አፈና በ“ህግ” ሽፋን “ፍትህን የማስፈን” ዕውቅና ይቸረው ከጀመረ በአገዛዙ ዕድሜ ዘመን ልክ ይቆጠራል። ሰላማዊውን መንገድ “የፍርሃት” አድርጎ የሚቆጥረው ህወሃት “ጦርነትን መሥራት እችላለሁ” እያለ ቢደነፋም በሕዝባዊ እምቢተኝነት የተነሳው ተቃውሞ ከገጠር ተጋድሎ ወደ ከተማ አብዮት የመቀየር ፍንጮችን በገሃድ እያሳየ ነው። ከራሱ ተሞክሮ እንደሚያውቀው ይህ ዓይነቱ አካሄድ  ሥርዓተ አገዛዙን በመናድ ዕድሜውን የሚያሳጥር ብቸኛ አማራጭ ሆኖ ቀርቧል።
ይህ ሳምንት ለህወሓታዊያን “የፍትህ ሳምንት” በሚል የፕሮፓጋንዳ አታሞ መምቻ ሲሆን፤ ለግፉአን ኢትዮጵያዊያን ደግሞ በአገዛዙ ወደር የለሽ የጭካኔ ተግባር በሞት ያጣናቸውን፣ የአካል ጉዳት የደረሰባቸውን፣ የደረሱበት ያልታወቁትን፣ በማዕከላዊ እስር ቤትና ለህዝብ ይፋ ባልሆኑ ድብቅ ማጎሪያ ቤቶች በአሰቃቂ የእስር ምርመራ እየማቀቁ ያሉ ውድ ወገኖቻችንን ስቃይ ይበልጥ የምንጋራበት የጨለማ ሳምንት ነው።
ፍትህ የህገ-ኅልዮት ሰንደቅ ነች!
ፍትህን ይኖሯታል እንጅ አይነግዱባትም!
ይህ ርዕሰ አንቀጽ የ“ጎልጉል: የድረገጽ ጋዜጣ®” አቋም ነው፡፡