ከስዩም ተሾመ

ኤድዋርድ ሰይድ (Edward Said) የተባለው ምሁር፣ የደቡብ አፍሪካ ነጮች ትላንት የሆነውን፣ ዛሬ እየሆነ ያለውንና ነገ የሚሆነውን፣ እያንዳንዱ ታሪካዊ ክስተት የራሱ የሆነ አሳማኝ ምክንያት አለው። ከቦታ፣ ግዜና ምክንያት አንፃር ድርጊቱ ስለተፈፀመበት ሁኔታ ይበልጥ ባወቅን ቁጥር ድርጊቱን ከመፈፀም በቀር ሌላ ምርጫና አማራጭ እንዳልነበረ እንረዳለን። ለምሳሌ፣ እንደ አይሁዶች ከናዚ ጭፍጨፋ የምትሸሽበት ሀገር፥ የሚሸሽግ መንግስት ከሌለህ ከአይሁዶች አፓርታይድ መስራች “ከዴቪድ ቤንጉሪዮ” (David Ben-Gurion) የባሰ አክራሪ አይሁድ ልትሆን ትችላለህ። ወይም ደግሞ እንደ ደቡብ አፍሪካ ነጮች በማጎሪያ ካምፕ ውስጥ ከጠቅላላ ሕዝቡ 10% በበሽታና ርሃብ ሲሞት ከደቡብ አፍሪካ የአፓርታይድ መስራች “ከዳኒኤል ፍራንኮይስ ማለን” (Daniel Francois Malan) የባሰ አክራሪ ነጭ ልትሆን ትችላለህ።

በመሰረቱ ሕልውናን የማረጋገጥ ጉዳይ (Survival) በሞራል ሆነ በሕግ አግባብ አይዳኝም (Necessity has no law)። ምክንያቱም፣ ከሕግ ወይም ሞራል አንፃር የሚያስከትለው ቅጣት ሕልውናን ከማጣት በላይ አያስፈራም። በዚህ መሰረት፣ በናዚዎችና እንግሊዞች የሕዝባቸው ሕልውና አደጋ ላይ ወድቆ ስለነበር በወቅቱ የተወሰዱ እርምጃዎችን “ትክክል” ወይም ስህተት” ብሎ መፈረጅ አይቻልም። በሁለቱም ሕዝቦች ላይ የተጋረጠው የሕልውና አደጋ ከተወገደ፤ በጀርመን የነበረው የናዚ ፋሽታዊ ስርዓት ከተወገደ እና ደቡብ አፍሪካ ከእንግሊዝ ቀኝ አገዛዝ ስርዓት ነፃ ከወጣች በኋላ ግን ለመሰረታዊ የሕግና ሞራል መርሆች ተገዢ መሆን የግድ ነው።

በዚህ መሰረት፣ በራስ ላይ የተፈፀመን ግፍና በሌሎች ላይ መልሶ መፈፀም ፍፁም “ስህተት” ነው። ምክንያቱም፤ ከሞራል አንፃር – በራስህ ላይ እንዲሆን የማትሻውን ነገር በሌሎች ላይ ማድረግ አግባብ ስላልሆነ፣ ከሕግ አንፃር – ለአንዱ ጥፋት ሌላን ተጠያቂ ማድረግ ስህተት ስለሆነ፣ እንዲሁም ከፖለቲካ አንፃር – የሌሎች ሰቆቃ ለራስ ሰቀቀን ስለሆነ (በሌሎች ላይ የምንፈፅመው ግፍና በደል የእኛን ሕይወትና እንቅስቃሴ በስጋትና ፍርሃት የተሞላ ያደርገዋል)። ስለዚህ፣ በወገንህ፥ ሕዝብህና ሀገርህ ላይ ሲፈፀም በፅናት የታገልከውን ጭቆና መልሶ በሌሎች ላይ መፈፀም ከሞራል፣ ሕግ ወይም ከፖሊቲካ አይታ አንፃር ተቀባይነት የለውም።

ስዩም ተሾመ

ለምሳሌ፣ እንግሊዞች ግፍና ጭፍጨፋ የፈፀሙት በደቡብ አፍሪካ ነጮች ላይ ብቻ አልነበረም። እንግሊዞች በጥቁር ደቡብ አፍሪካዊያን ላይ ተመሣሣይ በደልና ጭፍጨፋ ፈፅመዋል። ከ1889 – 1902 ዓ.ም (እ.አ.አ.) በተደረገው ጦርነት እንግሊዞች የማጎሪያ ካምፖች ውስጥ 28000 ነጮች ሲሞቱ በተመሳሳይ ከ15000 በላይ ጥቁሮች ለሞት ተዳርገዋል። ስለዚህ፣ እንግሊዞች በነጮችና ጥቁሮች ላይ እኩል ግፍና በደል ተፈፅሟል። ነገር ግን፣ እንግሊዝ በ1948 ዓ.ም ከደቡብ አፍሪካ ለቃ ስትወጣ ነጮቹ ተመሳሳይ ግፍና በደል በጥቁሮች ላይ መፈፀም ጀመሩ። ታዲያ በአንድ ጨቋኝ ስርዓት ስር አብረው ሲጨቆኑ የነበሩ ሁለት ሕዝቦች ከነፃነት በኋላ አንዱ ሌላውን የሚጨቁንበት ምክንያት ምንድነው?

እንደ ኤድዋርድ ሰይድ በደቡብ አፍሪካ የእንግሊዝን ቅኝ-አገዛዝ፣ በአልጄሪያ የፈረንሳይን፣ በቦስኒያ ወይም የፍልስጤም የነፃነት ትግል ውስጥ፣ በአጠቃላይ ለነፃነትና እኩልነት በሚደረግ ፍልሚያ መሃል “የትግላችን የመጨረሻ ግብ ምንድነው?” ብሎ መጠይቅ ያስፈልጋል። ለሕዝብ እኩልነትና ነፃነት የሚደረግ የሚደረግ ትግል ዋና ግቡ ጨቋኝ ስርዓትን ከስልጣን ማስወገድ ሳይሆን አዳዲስ ነፍሶችን መፍጠር (Invention of new souls) ነው። ከጨቋኝ ስርዓት ጋር ለሚደረገው ትግል አስፈላጊ የነበረው የወገንተኝነትና ጠላትነት ስሜት ከድል በኋላ በአዲስ ነፍስ – በእኩልነትና ነፃነት – መተካት ያስፈልጋል።

በትግል ወቅት ለሚታገሉለት ሀገርና ሕዝብ ልዩ ፍቅርና ወገንተኝነት፣ ለሚወጉት ጠላት ደግሞ ልዩ ጥላቻና ንቀት መፈጠሩ የማይቀር ነው። ምክንያቱም፣ ጨቋኝ ስርዓትን በጦርነት ለማስወገድ ከፍተኛ የሆነ የሕዝብ ወይም ሀገር ወገንተኝነት፣ ለጭቆናና ጨቋኞች ደግሞ የጠላትነት ስሜት ማስረፅ አስፈላጊ ነው። ነገር ግን፣ ይህ የወገንተኝነት እና ጠላትነት ስሜት የሚያገለግለው በጦርነት ወቅት ብቻ ነው። ጨቋኙ ስርዓት ከስልጣን ከተወገደ በኋላ ግን ፋይዳ-ቢስ ነው። ምክንያቱም፣ የትግሉ ዋና ዓላማ ጨቋኙን ስርዓት ማስወገድ ሳይሆን እኩልነት፣ ነፃነትና ፍትህ የተረጋገጠበት ፖለቲካዊ ስርዓት መገንባት ነው። ስለዚህ፣ የትግሉ መሪዎች ገና በትግል ላይ ሳሉ ጨቋኝ ስርዓትን ካስወገዱ በኋላ ስለሚሰሩት ስራ ማሰብ፣ መናገር፣ መከራከርና ማስተማር አለባቸው። በዚህ መሰረት ጨቋኙ ስርዓት ከተወገደ በኋላ የሁሉም ዜጎች መብትና ነፃነት የተከበረበት ዴሞክራሲያዊ ስርዓት እንዴት መገንባት እንደሚቻል ግልፅ ግንዛቤና የተግባር እቅድ ሊኖራቸው ይገባል።

በአጠቃላይ፣ ከጨቋኝ ስርዓት ነፃ ለመውጣት በሚደረገው ትግል አስፈላጊ የሆነው የህዝብ ወገንተኝነትና የጭቆና ጠላትነት በእኩልነትና ነፃነት መቀየር አለባቸው። ከዚህ ቀደም በተለያየ ደረጃ የተጨቀኑ፣ በደልና ጭቆና ያልደረሰባቸው ወይም ደግሞ የጨቋኙ ስርዓት ደጋፊዎች፣ …ወዘተ የሁሉም መብትና ነፃነት የሚከበርበት ስርዓት መዘርጋትና ይህንንም ከግዜ ወደ ግዜ እያሻሻሉ መሄድ ይጠይቃል። በትግል ወቅት የሰረፀው የወገንተኝነትና ጠላትነት መንፈስ ከትግሉ በኋላ በእኩልነትና ነፃነት መቀየር ካልተቻለ ግን ጨቋኙ ስርዓት በተወገደ ማግስት የእርስ-በእርስ ግጭትና ጦርነት መከሰቱ አይቀርም። ምክንያቱም፣ በትግል ወቅት የሰረፀው የህዝባዊ ወገንተኝነት በሂደት ወደ ፅንፈኛ አክራሪነት ወይም ብሔርተኝነት ይቀየራል።

ቀድሞ ጨቋኙን ስርዓት ለመታገል የሰረፀው የጠላትነት መንፈስ ከትግሉ በኋላ ሌላ ጠላት ይሻል። ይህ የጠላትነት መንፈስ እስካልተቀየረ ድረስ የግድ ጠላት ያስፈልገዋል። ስለዚህ፣ ጨቋኙ ስርዓት ከተወገደ በኋላም በቀድሞ ስርዓት በከፊል የተጨቆኑ፣ ያልተጨቆኑ ወይም ደጋፊ የነበሩትን የሕብረተሰብ ክፍሎች በጠላትነት መፈረጅ ይጀምራል። የጨቋኙ ስርዓት የፈጠረውን ቁስል እያከከ የሚውል የፖለቲካ ቡድን የሚንቀሳቀሰው ትላንት የተፈፀመበትን በደልና ጭቆና እያሰበ፣ የቀድሞ ስርዓት ደጋፊዎችን (ርዝራዦች) እየጠላና ወደፊት ስርዓቱ ተመልሶ ይመጣል በሚል ስጋትና ፍርሃት ነው። ይሄ ደግሞ በሌሎች ላይ እያደረሰ ያለውን በደልና ጭቆና እንዳይገነዘብ ይጋርደዋል።   ለምሳሌ፣ አዶልፍ ሂትለር በ1ኛው የዓለም ጦርነት ማብቂያ ጀርመን ከደረሰባት አሳፋረ ሽንፈትና ውርድት ለማንሳት የነደፈው በፅንፈኝነትና ዘረኝነት ላይ የተመሰረተ ፕሮፓጋንዳ በሂደት ከናዚዎች ቁጥጥር ውጪ ሆነ። ይህ በአይሁዶች ላይ የዘር-ማጥፋት ጭፍጨፋ እና ለ2ኛው የዓለም ጦርነት ምክንያት ሆኗል።

አይሁዶች የተፈፀመባቸውን በደልና ጭፍጨፋ ተከትሎ የራሳቸውን ሀገርና መንግስት በመካከለኛው ምስራቅ ለመመስረት ከተለያዩ የአረብ ሀገሮች ጋር ጦርነት አካሄዱ። እነዚህን ጦርነቶች በድል ለማጠናቀቅ የአይሁዶች ወገንተኝነት እና ለአረቦች የጠላትነት ስሜት ማስረፅ ይጠበቅባቸው ነበር። በጦርነት ወቅት የዳበረ የአይሁዶች የወገንተኝነትና ጠላትነት ስሜት ዛሬ ላይ ለሚታየው የአይሁዶች አክራሪነት እና የጠላትነት መንፈስ በእስራኤል ለተዘረጋው የአፓርታይድ ስርዓት ዋና መሰረት ነው። በናዚዎች ከተፈፀመባቸው ግፍና ጭፍጨፋ የተረፉ የሰቆቃ ልጆች በፍለስጤሞች ላይ ግፍና ጭፍጨፋ የሚፈፅሙበት ይህ የአክራሪነትና ጠላትነት ስሜት ነው። የእስራኤል መንግስት በዌስት ባንክ የሚካሄደውን ሕገ-ወጥ የቤቶች ግንባታ ለማስቆም ያደረገው ጥረትና ከአክራሪ የአይሁዶች የገጠመው ከፍተኛ ተቃውሞ ሊጠቀስ ይችላል። በሀገር ምስረታ ወይም በጦርነት ወቅት የተፈጠረ የወገንተኝነትና የጠላትነት ስሜት በሂደት ወደ ብሔርተኝነት እና ፅነፈኝነት ሊቀየር እንደሚችል ጥሩ ማሳያ ነው።

ልላው ከ27000 የማይበልጥ ተዋጊዎች የነበሯቸው የደቡብ አፍሪካ ነጭ ሰፋሪዎች 500000 ወታደሮች ያሰለፈውን የእንግሊዝ ጦር በውጊያ ለመግጠም በራሱ ከፍተኛ የሆነ የሕዝብ ወገንተኝነትና ቁርጠኝነት ያስፈልጋል። ከዚህ በተጨማሪ፣ ከሚታገሉለት ሕዝብ ውስጥ 10% በማጎሪያ ካምፕ ውስጥ በበሽታና በርሃብ ሲያልቅ የሚፈጥረውን ቁጭትና የጠላትነት ስሜት መገመት ይቻላል። ነገር ግን፣ ይህን በጦርነት ወቅት የተፈጠረን አሮጌ-ስሜት ሳይቀይሩ ሀገርን ማስተዳደር አይቻልም። ምንያቱም ስለ ቀድሞ ስርዓት በደልና ጭቆና ብቻ የሚስብ የፖለቲካ ቡድን ነባራዊ እውነታን በቅጡ መገንዘብ ይሳነዋል። የደቡብ አፍሪካ ነጮች ከእነሱ ጋር እኩል በደልና ጭቆነና ሲደርስባቸወው የነበሩትነን ጥቁሮች በአፓርታይድ ስርዓት መልሰው መጨቆን የጀመሩት በዚህ ምክንያት ነው።

የናዚ ጭፍጨፋ የወለዳቸው የእስራኤል “የሰቆቃ ልጆች” በፍልስጤማዊያን ላይ የፈፅሙት በደልና ጭቆና በተራው ሽብርተኝነትን ወለደ። የአል-ቃይዳ የሽብር ጥቃት ዓለም አቀፉን የፀረ-ሽብር ጦርነት አስከተለ። የኢራቅና አፍጋኒስታን ወረራ እንደ “ISIS” ያሉ አሸባሪ ቡድኖችን ወለደ። በአጠቃላይ፣ ዛሬ ላይ እንደ አሸን ለፈሉት አሸባሪ ድርጅቶች መነሻ ምክንያታቸው በእስራኤል ያለው የአይሁዶች አፓርታይድ ስርዓት ነው። ታላቁ ምሁር አልበርት አንስታይን (Albert Einstein) ፍልስጤምን መልሶ መገንባት የአይሁድ ሕዝቦችን ሕልውና የማረጋገጥ ጉዳይ እንደሆነ ገልፆ ነበር፡-

“Anything we may do for the common purpose is done not merely for our brothers in Palestine, but for the well-being and honour of the whole Jewish people.”  THE WORLD AS I SEE IT፡ Addresses on Reconstruction in Palestine, Part I, Page 65.

ጨቋኞች በራሳቸው የተፈፀመን አሰቃቂ በደልና ጭቆና በሌሎች ላይ የሚደግሙት፣ በዚህም ራሳቸውን ከሰቆቃ አዙሪት ማውጣት የሚሳናቸው ነገሮችን ከአንድ ማዕዘን ብቻ ስለሚመለከቱ ነው። የእነዚህ ወገኖች የፖለቲካ አመለካከት በዋናነት ቀድሞ ከተፈፀመባቸው በደልና ጭቆና አንፃር ብቻ የተቃኘ ነው። ተግባራዊ እንቅስቃሴያቸው የሚመራው፣ የወደፊት አቅጣጫቸውን የሚወስኑት “የቀድሞው ጨቋኝ ስርዓት ተመልሶ ይመጣል” በሚል በስጋት ውስጥ ሆነው ነው። እንዲህ ባለ ስጋትና ፍርሃት የሚያደርጉት ነገር የሌሎችን መብትና ነፃነት ይገድባል። በእነሱ ላይ የደረሰው በደልና ጭቆና ተመልሶ እንዳይመጣ ሲታትሩ በሌሎች ላይ ተመሳሳይ በደልና ጭቆና ይፈፅማሉ። ስላለፈው ሲፈሩ የወደፊት ተስፋን ያጨልማሉ። ይህ በተራው ቂምና ጥላቻ እየተጠራቀመ ሄዶ በመጨረሻ ሌላ ጨቋኝ ስርዓትን ይወልዳል።