June 13, 2017 

 

ድርቅ

በሶማሌ ክልል በድርቅ በተመታ አክባቢ ነዋሪዎች መካከል

ድርቅ ወደ ከፋ ችግር እንደሚቀየር የግብረ ሰናይ ደርጅቶች እየወተወቱ ነው። ሮይተርስ መንግስትም ሆነ የግብረ ሰናይ ድርጅቶች አረጋግጠውልኛል እንዳለው ከአንድ ወር ባነሰ ጊዜ የሚላስ የሚቀመስ የለም ሲል በስፍራው ተግኝቶ ዘግቧል። መንግስት በቂ ክምችት አለ ይላል። በሌላ በኩል እስከ ሐምሌ ባዶ ጎተራዎችን ለመሙላት የሚሆን ገንዘብ ጠይቆ አለማግኘቱ ታውቋል።

የዓለም ዓቀፍ ገብረሰናይ ድርጅት ሃላፊዎች ” ክፉው ቀን ከፊታችን ነው፣ የከፋው አደጋ ላያችን ላይ ሊወድቅ ነው፣ የምግብ አቅርቦቱ መስመር ተናግቷል፣ባዶ ጎተራ ነን….. እያሉ እየጮሁ ነው” ኢትዮጵያ ደሃ አገር በመሆኗ ዓለም ሊተባበር እንደሚገባ አሳስበዋል። ሮይተርስ ሁሉን አይቶና ገምግሞ የከፋው ጊዜ ከፊት በቅርብ መሆኑንን ሲዘግብ፣ ያ – ጊዜ እሩቅ አይደለም አለመሆኑንን በማመልከት ነው። ከአንድ ወራ በሚያንስ ጊዜ የሚበላ እንደማይኖርም አበክረው ያስታወቁትን ክፍሎችና ሰላባዎች ጠቅሶ ነው የጻፈው።

የዋርደሩ ተፈናቃይ መሀመድ ዱበት ድርቁ ህይወታቸውንና አካባቢውን ክፉኛ እንደመታው ተናግሯል። የሚሄዱበት መሸሻ እንደሌላም አስታውቋል። የሚመኩባቸው ከብቶቻቸው በግጦሽ ሽግር አለቀዋል። ከጉዳት የሚያተርፍ አንድም ምልክት የለም።

ሌላዋ ሴት ” በህይወት ዘመኔ እንዲህ ያለ ነገር አይቼ አላውቅም” ሲሉ ከብቶቻቸው እንዳለቁት ሁሉ የእነሱም እድል ፈንታ ሞት እነድሆነ ተናግረዋል። ባዶ ጎተራ፣ የገንዘብ ችግር፣ ተደራራቢ ጉዳት፣ አሁንም የዝናብ ተስፋ አለመኖር እና ፖለቲካዊ ችግር ወዴት ያመራ ይሆን? ወዳጅ አገሮችስ? ምነው ዝም አሉ? ለምን? ለየመን የተሰጠ ትኩረት ለኢትዮጵያ እንዴት? መንግስት የእህል ከምችቴ አልተሟጠጠብኝም ሲል የበኩሉን እያደረገና ለወደፊትም እየተዘጋጀ መሆኑን በመጠቆም ፋና ይህንን ዘግቧል

መንግስት ለድርቅ ተጎጂዎች የሚቀርበው እርዳታ ከሰኔ ወር አይሻገርም በሚል የተሰራጨው ዘገባ ሀሰት መሆኑን ገለፀ

በተለያዩ የሃገሪቱ ክፍሎች የተከሰተውን ድርቅ ተከትሎ የእለት ደራሽ እርዳታ የሚያስፈልጋቸው 7 ነጥብ 78 ሚሊየን ዜጎች ከክረምቱ መግባት ጋር ተያይዞ የእርዳታ አቅርቦት እንዳይቋረጥባቸው ቀድሞ የማከማቸት ተግባር እየተከናወነ መሆኑን ከሰሞኑ የብሄራዊ አደጋ ስጋት ስራ አመራር ኮሚሽን ገልጿል።

ይሁንና የተለያዩ አለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃን ለአጠቃላይ ተረጂዎቹ የሚደረገው የእርዳታ አቅርቦት የያዝነውን የሰኔ ወር የማይሻገር መሆኑን አለም አቀፍ ለጋሾችን በመጥቀስ እየዘገቡ ይገኛሉ። በጉዳዩ ዙሪያ ከፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት ጋር ቆይታ ያደረጉት የመንግስት ኮሙዩኒኬሽን ጉዳዮች ፅህፈት ቤት ሃላፊ ሚኒስትር ዶክተር ነገሪ ሌንጮ፥ ከሰሞኑ በአንዳንድ መገናኛ ብዙሃን ሲሰራጭ የነበረው መረጃ ትክክለኛ አይደለም ብለዋል።

መንግስት ድጋፍ የሚያስፈልጋቸውን ዜጎች ቁጥር ለኢትዮጵያ ህዝብም ሆነ ለአለም ህዝብ ግልፅ አድርጎ አስፈላጊውን ምላሽ ሲሰጥ መቆየቱን ነው ኃላፊ ሚኒስትሩ ያስታወሱት። የእለት ደራሽ እርዳታ ከሚያስፈልጋቸው ዜጎች ውስጥ መንግስት ለ4 ነጥብ 7 ሚሊየኑ በራሱ ብቻ ድጋፍ ሲያደርግ መቆየቱን ያነሱት ዶክተር ነገሪ፥ 1 ነጥብ 7 ሚሊየን ዜጎች ደግሞ በዓለም ምግብ ፕሮግራም አማካኝነት ድጋፍ እየተደረገላቸው ነው ብለዋል።

ቀሪ 1 ነጥብ 4 ሚሊየን የእለት ደራሽ እርዳታ ፈላጊ ዜጎችም የካቶሊክ የእርዳታ ድርጅት በሚያስተባብረው የለጋሽ ተቋማት እርዳታ እየቀረበላቸው እንደሚገኝ ጠቁመዋል። የዓለም ምግብ ድርጅት ያለበትን እጥረት ለመሙላት ድጋፍ ለማግኘት የሰጠው መረጃ መገናኛ ብዙሃኑ አሳስቶ 7 ነጥብ 78 ሚሊየን የሚሆኑ ዜጎች የሚደረግላቸው ድጋፍ ሰኔ ወር ላይ ያልቃል የሚል የተሳሳተ መረጃ እንዲያቀርቡ አድርጓል ነው ያሉት ዶክተር ነገሪ።

ድርጅቱ ለ1 ነጥብ 7 ሚሊየን ዜጎች የሚያደርገው ድጋፍ እንዳይቋረጥ ለለጋሽ ድርጅቶች ያቀረበው ጥሪ በመገናኛ ብዙሃኑ በአጠቃላይ በሀገሪቱ መንግስት እና በሌሎች ለጋሽ ድርጅቶች ድጋፍ የሚደረግላቸውን ዜጎችም ጭምር ከሰኔ ወር በኋላ እርዳታ ይቋረጥባቸዋል በሚል በስህተት ተዘግቧል ብለዋል ሚኒስትሩ። የዓለም ምግብ ድርጅት ዋነኛ ድጋፍ የሚያደርግለት የአሜሪካ የተራድኦ ድርጅት እና የአውሮፓ ሀገራት ናቸው።

በድርጅቱ በኩል ለእርዳታ የሚውል በጀት በአሜሪካ የተመደበ ባለመሆኑ ከስጋት በመነጨ ችግሩን ማሳወቁን የጠቆሙት ዶክተር ነገሪ፥ የዓለም ምግብ ድርጅት ስጋቱን ከመግለፁ ውጭ መንግስትም ሆነ ለጋሽ ድርጅቶች የእርዳታ እጥረት አላጋጠማቸውም ብለዋል። በመንግስት በኩል ለዜጎች አስፈላጊውን ድጋፍ ለማድረግ ዝግጅት መደረጉንም ነው የገለጹት።

መንግስት የእለት ደራሽ ድጋፍ ለሚሹ ዜጎች የምግብ፣ የውሃ እና የመጠለያ ድጋፍ ከማድረግ ባሻገር ድርቁን በዘላቂነት ለመፍታት እየሰራ መሆኑን ጠቁመዋል። ድርቅ ባጋጠማቸው የተወሰኑ አካባቢዎች የተገኘውን ዝናብ ተጠቅሞ ምርት ለማምረት ስራዎች ተጀምረዋል ነው ያሉት ዶክተር ነገሪ።

በአጠቃላይ የእለት እርዳታ የሚሹት ዜጎች ምንም አይነት ድጋፍ አይቋረጥባቸውም፤ በተለያዩ መገናኛ ብዙሃን ለድርቅ ተጎጂዎች የሚደረገው የእርዳታ አቅርቦት ከሰኔ ወር አይሻገርም በሚል የሚናፈሰው ዘገባም ሀሰት ነው ብለዋል።