June 16, 2017

ጡዘት ላይ የደረሰው የብአዴን እና ሕወሓት የጽሁፍ ግብግብ

~ ብዙ ጊዜ በህውሃት ባለቤትነት የሚንቀሳቀሱትን “Tigray Online” እና “Aiga Forum” የተባሉትን ድረ ገፆች እከታተላለሁኝ ። በእንግሊዚኛም፣ በአማርኛም፣ በትግሪኛም ይፅፋሉ። ሁሉንም አነባለሁኝ። አነባለሁ ከምል መርዝ ጠጥች እወጣለሁ ብል ይሻለኛል ። በነዚህ ድረገፆች የሚሰራጩት ፅሁፍ ሳይሆን መርዝ ነው ማለት ይቻላል ። በአማራ ህዝብ ላይ የሚነዙት የሩዋንዳውን “ሬዲዮ ኮሊንን” ያስንቃል። ህውሃት የሚፈልገውን ካለገደብ የሚያቀረሽባቸው ድረ ገፆች ናቸው። በእነዚህ ድረገፆች ስለአማራ ህዝብ የሚፃፈው ያስደነግጣል። እኔም ሳልታክት ወደ እነዚህ ድረገፆች እየሄድኩ የማነበው የጠነሰሱልንን ፣ የደገሱልንን ሴራቸውን ለመረዳት ነው።

~ እነዚህን ድረገፆች አነባለሁ ብያለሁኝ ። ታድያ አንድ የሚገርመኝ አለ። እነዚሁ ድረገፆች ባለፈው አመት ብቻ የአማራ ክልልን ፕሬዚዴንት ገዱ አንዳርጋቸውን ርእስ አድርገው የሚሳደቡ፣ የሚያንቋሽሹ ከ 10 በላይ ፅሁፎች ፅፈዋል። ዘንድሮም እንደዚሁ እየፃፉ ነው። በእነዚህ ድረ ገፆች በሚፃፉ ፅሁፎች ገዱ አንዳርጋቸው ይከሰሳል፣ ይዘለፋል፣ ይተፋበታል፣ ይገረፋል በመጨረሻም ይሰቀላል ። የሚጠቀሙት ፀያፍ ቃላት “ኤሎሄ” የሚያስብል ነው ።

~ ህውሃት ይሄን የገዱን ጉዳይ በድረገፆች ብቻ አልበቃው ሲል በወኪሉ ዳንኤል ብርሃነ አማካኝነት ወደ ፌስቡክ አምጥቶታል ። ይሄው ውዝግብ አድጎ ብአዴን በቃልአቀባዩ ንጉሱ ጥላሁን አማካኝነት የተሽለጠለጠ መልስ ሰጥቷል። የአቶ ንጉሱ መልስ መሽቆጥቆጥ የሚበዛው ቢሆንም ህውሃቶች ግን “እንደት አሻንጉሊታችን ንጉሱ ደፍሮ መልስ ይሰጠናል ?” በሚመስል ስሜት “ቡራከረዩ” እያሉ ነው።

~ አሁን ላይ ጡዘት ላይ የደረሰው የፅሁፍ ጦርነት የተጀመረው ዳንኤል ብርሃነ የተባለ የወያኔ ወኪል ገዱ አንዳርጋቸውን “ዶማ” ብሎ በመሳደቡና “ሃይለማሪያም ደሳለኝን አንጓጠጠው” በማለት ከፃፈ በኋላ ነው። እነ ንጉሱ ጥላሁን እነ “አይጋ ፎረም” እና “ትግራይ ኦን ላይን ” ስለማይከታተሉ “ዶማ ” በሚለው ስድብ ደነገጡ እንጅ እነዛን ድረገፆች ቢከታተሉ ኖሮ “ዶማ ” የሚለው ስድብን እንደ ምርቃት ይቆጥሩት ነበር። “አልሰሜን ግባ በለው! ” የሚለው የአገሬ ሰው ለዚህ ነው ።

~ ህውሃቶች ይዘውት የመጡት አዲስ ክስ “ገዱ ሃይለማሪያም ደሳለኝን በንቀት አመለካከት ተመለከተው። ሃይለማሪያምም በገዱ ንቀት ተበሳጭቶ ስልጣኔን ተረከቡኝ አለ” የሚል ከትከትከት አድርጎ የሚያስቅ ክስ ነው። ሃይለማሪያም እኮ ንቀት ቁርስ ምሳ እራቱ ነው ።

የሱማሌ ክልል ፕሬዚደንት አብዲ ኢሌ ጅጅጋ ላይ በጉንጩ ሙሉ ያጠራቀመውን ምራቅ ሲተፋበት ያልተናደደ ጅላጅል በገዱ ግልምጫ “ስልጣኔን እለቃለሁ” በማለት ተናገረ የሚለው አስገራሚ ነው ።

~ አቶ ንጉሱ ጥላሁን የፃፋቸው ሶስት ቃላት ዳንኤልንና ህውሃቶችን እጅግ በጣም አወራጭቷቸዋል። “ተልእኮ” ፣ “እናንተ ያላችሁበት ጭቃ ውስጥ ገብተን እንድንጨማለቅ አታድርጉን” የሚልና “አንቺ” የሚሉት ናቸው።

~ አቶ ንጉሱ “ተልእኮ” ሲል ዳንኤል ብርሃነ የህውሃት የደህንነት ወኪል መሆኑንና የምናውቀውን እውነት እየገለፀልን ነው። በነገራችን ላይ ዳንኤል ብርሃነ የቀድሞው የኢደፓ አመራር አባል የነበረ ሰው ነው። ከልደቱ አያሌው ፣ሙሸ ሰሙ ቀጥሎ የፓርቲው ሃላፊነት ቦታ የነበረ መሆኑ ይሰመርበት። እነ ልደቱን ከደህንነት ጋር በማደራደር እና ቅንጅትን በማፍረስ የዳንኤል ብርሃነ ድርሻ ከፍተኛ ነበር ።

~ አቶ ንጉሱ እና ብአደኖች የዳንኤልን ሀሳብ እንደ ግለስብ ሀሳብ መውስድ አስቸግሯቸዋል። ዳንኤል የህውሃት ባላስልጣናትን ቃል በፈለገበት ሳዓትና ቦታ የሚቀበል ብሎም የተቀበለውን ቃል የሚያስተላለፍ ሰው ከመሆኑ አንፃር ዳንኤል የአባይ ወልዱ ወኪል ነህ ቢለው የሚያስኬድ ነው። ዳንኤል እኮ ሰለገዱ የጻፈው የኢህአዴግ ምክር ቤት ተነገረ በተባለ ሀሳብ ዙሪያ ነው፤ ለዳንኤል ማን ነገረው እሱ አባል አይደለም ያው የሚነግሩት በውይይቱ የተገኙ በዙሪያው ያሉ የህውሃት ባለስልጣናት ነው አስጨብጠው እንደላኩት ግልፅ ነው።

~ “ወደ ቆማችሁበት ጭቃ አታውርዱን” የአቶ ጥላሁን ወደ ቆማችሁበት ጭቃ አታውርዱን የሚለውም ባህርዳር ለመቀሌ ያስተላለፈችው ቃል ነው። አቶ ንጉሱ እየተቅለሰለሰም ቢሆን በባከነ ሰአት ህውሃት የጭቃ ስብስብ እንደሆነ ተንፍሷል።

~ የሁለቱ ፓርቲዎች ጡዘት አድስ ነገር ሳይሆን በአለፈው አመት ጀምሮ ብዙ የተባለለትና እስካሁንም ያልበረደ ነው። ብአዴን የህውሃት አሻንጉሊት ነው ነገር ግን በውስጡ አፈንጋጭ የለም ማለት አይቻልም። የህውሃትም ታርጌት ያደረገው ሰጥለጥ ብሎ የሚገዛው አሽከር ብአዴን አመራር ላይ ሳይሆን አፈንጋጩ ገዱ ላይ መሆኑ ምክንያቱ ምን እንደሆነ ይገባናል።

እንደ አለምነው መኮንን ያለ ሆዳም አሽከር፣ እንደ ካሳ ተክለብርሃን ያለ የህውሃት አሻንጉሊት፣ እንደ አዲሱ ለገሰ ያለ ዝቃጭ ባተጠራቀሙበት ድርጅት ውስጥ እንደ ገዱ ያለን የሰከነ እና በአንፃራዊነት ሃቀኛ ሰው ሳያደንቁ ማለፍ አይቻልም።

****************************************************************************************
የአማራ ክልል የኮምኒኬሽስን ሃላፊው አቶ ንጉሱ በፌስቡክ ለህወሃቱ ለዳንኤል ብርሀኔ የጻፈውን ጽሁፍ በሙሉ ከዚህ በታች አንብቡ  

ይህን ይጫኑት PDF⇓

https://ethiopanorama.comwp-content/uploads/2017/06/bern.pdf