June 19, 2017

 

ፍቅር ያዘኝ ብለህ አትበል ደንበር ገተር፤

እኛም አንድ ሰሞን እንዲህ አርጎን ነበር፡፡

ወያኔ አልጋ ላይ” (የፎቶው ምንጭ – ኢንተርኔት)

መውደቄ ነው ብለህ ልብህ አይበል ፈራ፤

አፄውና ደርጉም ሄደዋል በተራ፤

ደጅህ ደርሶልሃል ያኖርከው መከራ፤

መሰብሰቡ አይቀርም የዘሩት አዝመራ፡፡

በሠራኸው ሥራ ወያኔ ተጀነን! ለፈጸምከው ጀብዱ ምንጊዜም ኮራ በል፤

ኦሽትውዊዝን በሚያስንቅ፣ ሦርያን በሚያስንቅ፣ የመንን በሚያስንቅ

የዘመናት ልፋት ዘር የማጽዳት ግብርህ ዓለም አድንቆሃል፡፡

ትናንት ማታ አንዱ እንዲህ ሲል አወጋን፡፡ ባካፍላችሁ እንደምትዝናኑበት በማመን ይሄውና ከኔ እንዳይቀር አደረግሁ፡፡

በዚያን ሰሞን በአዲስ አበባ ከተማ የጦፈ የመንገድ ላይ ፍተሻ ነበረ አሉ፤ ይህ ነገር አልፎ አልፎ እንደሚከሰት አውቃለሁ፡፡ ወያኔዎች በተሸበሩና በደነበሩ ቁጥር በየመንዱና በየሰፈሩ ሰውንና መኪናን እያስቆሙ ይፈትሻሉ – ከዱሮም፡፡

አንድ አካባቢ በተደረገ የቅርብ ጊዜ ፍተሻ ሁለት ሽማግሌዎች እንዲፈተሹ ሦስት የወያኔ ፌዴራል ፖሊሶች ያስቆሟቸዋል አሉ፡፡ እዚያው በፍተሻው የነበረ ሰው ነው የሚነግረን፡፡ መገናኛ ሬዲዮ የያዘው ከሦስቱ ፈታሾች አንዱ የመሀል አገር ሰው ይመስላል፡፡ ሌሎቹ ደቡብ ናቸው – የወያኔ ልክፍት ተጋብቶብን ሰውንና ንብረትን ሳይቀር በዘውግና በአቅጣጫ ስም መጥራትን አሁን አሁን በሚገባ ተለማምደናል፡፡ የወያኔ የጦርና የፀጥታ ሰዎች በአብዛኛው ከደቡብና ከጋምቤላ መሆናቸው የታወቀ ነው፡፡ ከሕዝብ ጋር እንዳይመሳሰሉና የሕዝብን ባህልና ወግ፣ ቋንቋና እምነት እንዳይጋሩ በወያኔ የሚደረገው ጥረት ከፍተኛ ነው፡፡ ለማንኛውም  እነዚያ ሽማግሌዎች ተፈተሹ ሲባሉ አሻፈረን አሉ፡፡ “በገዛ ሀገራችን ለምንድን ነው የምንፈተሸው?ብለው አካኪ ዘራፍ ይላሉ፡፡ ሰዎቹ ለመፈተሽ ፈቃደኛ ካልሆኑ ውስጣቸውን ገልቦ አብጠርጥሮ እንደሚፈትሻቸው አንዱ ደቡቤ ፌዴራል በራሱ አማርኛ እያስፈራራ ይገስጻቸዋል፤ በወያኔ ቤት መደዴነት ትልቁ ጨዋነት ነውና ትልቅ ሰውን ማክበር እንደወንጀል ይቆጠራል – አቤት ሰውን በማዋረድና በመሳደብ እንዴት እንደሚደሰቱ ብታዩዋቸው! … ሰዎቹ በእምቢታቸው ጸኑ – ለጽናታቸውም አንዱ ቀጭን ሰበብ ውኃ ቢጤ ቀምሰው ለብ ያላቸው መሆኑ ነው ተብሏል፡፡ አጠገብ በነበሩ ሰዎች ተማጽኖ ፍተሻውን እንደነገሩ ዳበስ ተደርገው እንዲያልፉ ተደረገ፡፡ ሰዎቹ ካለፉና ራቅ ካሉ በኋላ አንደኛው ሽማግሌ ፌዴራሎቹን ይጣራና “ስማ አንት ወታደር፤ አታውቅም እንጂ ጡትና መንግሥት ዱሮውንም ቀስ ብሎ መውደቁ አይቀርም! አትጃጃሉ!” ያኔ የመሀል አገር ሰው የሚመስለው ሰልጠን ያለው ፌዴራል በጁ የያዘውን ሬዲዮ መቆጣጠር እስኪያቅተው ድረስ በሣቅ ሞተ፡፡ ሰው የሆዱን ሲነግሩት ከልቡ ይስቃል ይባላል አይደልሌሎቹ ግን ፊታቸው እንደሳት ግሞ የሚያደርጉትን አጡ፡፡  በሰዎቹ ላይ ግን እርምጃ አልወሰዱባቸውም፡፡ የወያኔ ቅልብ ጦር እኮ እንደሚታወቀው ግደል እስኪባልም አይጠብቅም – ግደል ሲሉት “ለምን?” ብሎ ከመጠየቅ ይልቅ “ስንት ልግደል?” ማለቱ እንደተጠበቀ ሆኖ እነዚህ ደነዝ ፌዴራሎች ትኩር ብለህ ካየሃቸው እንኳን ራሱ ሊገድሉህ ይችላሉ፡፡ ሰው ናፈቀን፤ እውነተኛ ሀገር ጠባቂ የሕዝብ ሠራዊት ናፈቀን፤ ሃቀኛ ዳኛ ናፈቀን፤ መምጣቱ መቼም ቢሆን የማይቀረው ቀን ራቀብን፡፡