JULY 11, 2017

AN ETHIOPIAN SOLDIER MANS AN OBSERVATION POST ON THE ERITREAN BORDER ON 19 NOVEMBER 2005

ዛጎል ዜናአስረኛ ወሩን የያዘው የአስቸኳይ  ጊዜ አዋጅ መነሳት  ከማንም በላይ በመከላከያ ሰራዊት አባላት በናፍቆት የሚጠበቅ ቀን መሆኑንን ነው የዜናው ምንጮች የሚናገሩት። ለዚህም ምክንያት አላቸው። ምክንያታቸውም መልቀቂያ አስገብቶ፣ ወይም “በቃኝ” በማለት ለመሰናበት። የስድስት ወር እድሜውን አገባዶ ተጨማሪ አራት ወር የተጨመረለት የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ የሚጠናቀቀው በያዝነው ሃምሌ መጨረሻ ግድም ቢሆንም ይነሳ ወይም ይቀጥል አልታወቀም።

የመከላከያ ሰራዊት ባለ ኮከብ አባል ነው። ስሙ ለደህነንቱ ሲባል እንዲጠቀሰ አይፈልግም። ይኽው መኮንን ለጎልጉል እንዳለው ከአስቸኳይ አዋጁ ጋር በተያያዘ በመከላከያ ሰራዊት ውስጥ መጨናነቅ ተከስቷል። ስራ መልቀቂያ ማስገባት አይቻልም። ልዩ የሀዘንና ከባድ ችግር ካልሆነ የእረፍት ፈቃድ አይጠየቅም። እሱ እንደሚለው ኑሯቸው ኑሮ አይደለም።

ያለማጋነን” ይላል ይኸው መኮንን ” በአሁኑ ሰዓት ቢፈቀድ ከ50 በመቶ በላይ የሰራዊቱ አባላት መሰናበትን ይመርጣሉ። ይህ በከፍተኛ አመራሩ ዘንድ በደንብ የሚታወቅ ሃቅ ነው። በሰራዊቱ ውስጥ የሞራል መላሸቅ እየነገሰ ነው” ችግሩ ይህ ብቻ አይደለም። መልቀቂያ ማስገባት በራሱ ልዩ ምርመራ ያስከትላል።

ለምን፣ እንዴ፣ ከማን ጋር ግንኙነት አለህ? እንዴት በዚህ ወቅት የመልቀቂያ ጥያቄ አነሳህ? ” ወዘተ የሚሉ ጥያቄዎች በማንሳት የሚደረገው ምርመራ አስፈሪ እንደሆነ የሚጠቁመው መኮንን  ” የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ መነሳት በቅድሚያ የሚያጓጓው ሰራዊቱን ነው” ብሏል። ከአዋጁ መነሳት ጋር በተያያዘ የመልቀቂያ ጥያቄ የማቅረብ እገዳው አብሮ ስለሚነሳ!

የዲቪ እድል፣ በውጭ አገር ነዋሪ ከሆነች ጋር ትዳር የሚያደርግ፣ አስቀድሞ የተጀመረ የትምህርት እድል ካለ ሰራዊቱ መሰናበት እንደሚቻል መኮነኑ አመልክቷል። የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሰለመነሳቱ ለተጠየቀው ” አሁን ሁሉም ነገር ተረጋግቷል ግን ታፍኖ የተያዘ ነው” የሚል መልስ ሰጥቷል። በሁሉም አቅጣጫ ችግሮችን የመፍታትና መፍትሄ አስቀምጦ ዘላቂ ሰላም የማስፈን ስራ እንደማይሰራ በተለያዩ አክላት የሚገለጽ ጉዳይ ነው። ራሱ ኢህአዴግ ” ጥልቅ” ሲል በጠራው ተሃድሶ ይህንኑ ጉዳይ በተደጋጋሚ ሲናገረው መሰንበቱም አይዘነጋም።

አገሪቱ ወደ ቀድሞ አስተማማኝ ሰላሟ መመለሷን ኢህአዴግ በተደጋጋሚ እየገለጸ ቢሆንም በሰሜኑ የአገሪቱ ክፍል በተለይ በጎንደር ግጭት እንዳለ እየተገለጸ ነው። አንዳንዴም ከግጭት ያለፈ ውጊያ እንደሚድውረግም ይገለጻል። የአካባቢው የሆስፒታል ምንጮች ቁስለኛ ስለመኖሩም ይናገራሉ። ኢህአዴግም ቢሆን ይህንን ሲያስተባብል አይሰማም። የመከላከያ ሚኒስትሩ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሲራዘም ችግር ስለመኖሩ በይፋ መናገራቸው ግን አይዘነጋም።

በሌላ በኩል ሰራዊቱ ቢሰላችና ሞራሉ ቢጎዳ እንደማይገርም የሚገልጹ አሉ። በኤርትራ ድንበር በረሃ ላይ ለሁለት አስርት ዓመታት የሰፈረው ሰራዊት በሁለት ምክንያት ያሳዝናል። በተለያዩ ወቅቶች በተሰጡ አስተያየቶች ሰራዊቱ በሚዘገንን መሰዋዕት ያሸነፈውን ጦርነት መሪዎች እንዲነጠቅ አድርገውታል። ደጀን የሆነው ህዝብ በዚህ የመሪዎች ተግባር አዝኗል። ከዛም በሁዋላ ያለ አንዳች መፍትሄ ሰራዊቱ የቀበሮ ጉድጓድ ውስጥ እየኖረ ነው። ይህ ከፍተኛ ቁጥር ያለው ሰራዊት ቢሰላችና ” በቃኝ” ቢል የሚገርም አይሆንም። በዚህ ላይ አሁን አገሪቱ በሕዝባዊ ቁጣ ነዳ በነበረችበት ወቅት እርምጃ የወሰዱትም ሆኑ እርምጃ ሲወሰድ የሚሰሙት የመከላከያ ሰራዊት አባላት ስሜት የላቸውም ማለት አይቻልም የሚሉም ጥቂት አይደሉም።

ይህ በእንዲህ እንዳለ ፋና ብሮድ ካስት 95 የቤኒሻንግል ነጻ አውጪ ንቅናቄ አባላት በስምምነት ጠመንጃ ማውረዳቸውን ዘግቧል።የቡድኑ አባላት የቆዩበትን የአመጽ ድርጊት በመተው ሰላማዊ እንቅስቃሴ ለማድረግ ነው ወደ ሀገራቸው መግባታቸውን ነው ፋና ያመለከተው።

95ቱ አባላት መካከል 15ቱ በካርቱም ይኖሩ የነበሩ የድርጅቱ አመራር አካላት እንደሆኑ የጠቆመው ፋና መነሻቸው ኤርትራ እንደሆነ በዘገባው አመልክቷል።

ZAGGOLENEWS. የዛጎል ዜና