July 14, 2017

በአማራ ክልል በሰሜን ወሎ ዞን እና በአፋር ክልል የሚገኙ ሁለት ተጎራባች ቀበሌ ነዋሪዎች በየጊዜው በሚቀሰቀስ ግጭት ሲጋጩና ሲታረቁ ቢቆዩም አሁን ግን የ12 ሰዎች ሕይወትን ያጠፋ የከረረ ግጭት መፈጠሩን የሁለቱ አካባቢ ነዋሪዎች ይናገራሉ።

ዋሽንግተን ዲሲ —

ግጭቱ መሰረታዊ መፍትሔ የሚሰጥ አካል በመጥፋቱም የሚጠፋው የሰው ሕይወትና በስጋት ቀያቸውን ጥለው የሚሰዱ ሰዎች ቁጥር እየጨመረ መምጣቱን ይናገራሉ። የአካባቢው አስተዳደር አካላት እና የተመረጡ ሽማግሌዎች ችግሩን ለመፍታት ጥረት እያደረጉ መሆኑን ጭምር ይገልፃሉ።

በአማራ ክልል ሰሜን ወሎ ዞን ሀብሩ ወረዳ ሶዶማ ቀበሌ በአፋር ክልል ውስጥ ከሚገኘው ጭፍራ ወረዳ ጋር ተጎራባች እንደሆነች የአካባቢው ነዋሪዎች ይገልፃሉ። የሁለቱ ተጎራባች ነዋሪዎችም ለረጅም ጊዜ አብረው የኖሩና ተጋብተው የወለዱ ጎረቤታሞች ናቸው ይላሉ። ግን ደግሞ በየጊዜው በመካከላቸው ግጭት ይፈጠራል የሰው ሕይወት ይጠፋል ሽማግሌ ገብቶ ያስታርቃቸዋል እንደገና ደግሞ መልሰው እንደሚጣሉ ይናገራል።

ባለፈው ዕረቡ ሰኔ 28 የተከሰተው ግጭትም የዚህ አካል ነው ይላሉ። ከሁለቱም ወገን ያነጋገርናቸው ነዋሪዎች ለዚህ ዕለት ግጭት መነሻ የተለያየ ምክኒያትን ይሰጣሉ። “ቀድሞ ጥቃት የፈፀሙት እነሱ ናቸው” በማለት እርስ በእርስ ይካሰሳሉ። በሁለቱም ወገን የታየው ግን ከዕረቡ ሰኔ 28 እስከ አርብ ሐምሌ 1 ቀን ባደረጉት የሦስት ቀን ውጊያ የ12 ሰው ሕይወት መጥፋቱን ነው።
Audio Player