July 31, 2017

 

Obang Metho
Executive Director of the SMNE

“እነሱ (ምዕራባውያን) ገፍተው የገደል አፋፍ ላይ ቢያስቀምጡህ እንኳ ክፉ ቃል አይጠቀሙም። በተግባር ግን ያሳያሉ። በጀት ሲቀንሱ ምልክት ነው። የጦር ካምፓቸውን ሲያነሱ ምልክት ነው። ፊት ሲነሱ ምልክት ነው። ከሶማሌ እንዳትወጣ እያሉ ሲለምኑና ዶላር ሲያፈሱ ኖረው የራስህ ጉዳይ ካሉህ ትልቅ ምልክት ነው። መከርንህ፣ ነገርንህ አሁን የራስህ ጉዳይ ነው፣ ለራስህ እወቅ፣ ሁሉም ነገር ባንተ እጅ ነው ሲሉህ ምልክት ነው። ከዚህም በላይ አሁን ኢትዮጵያ እየሄደች ያለችበት መንገድ ወዴት እንደሚያደርሳት ጠንቅቀው ያውቃሉ። ወያኔዎቹ በዘላቂነት ምስራቅ አፍሪቃ እና አካባቢው ላይ ያላቸውን ፍላጎት የማስጠበቅ አቅማቸው መዛሉን ያውቃሉ። ከውስጥ የተነሳው ችግርና አገዛዙ የገባበት የቀውስ ገደል መጨረሻ ከማንም በላይ ይታያቸዋል። ተወደደም ተጠላም አሁን ነገሮች እየከበዱ ነው። እነሱ እንዳሉት ምርጫው በባለስልጣኖቹ እጅ ላይ ነው።” ኦባንግ ሜቶ ሰሞኑን የህወሃት/ኢህአዴግን የሰብዓዊ መብቶች ይዞታና አጠቃላይ አስተዳደርን የሚወቅስ የህግ ረቂቅ በዩናይትድ ስቴትስ የሕግ መምሪያ የውጭ ጉዳዮች ኮሚቴ ፊት ቀርቦ በሙሉ ስምምነት ክጸደቀ በኋላ ከዛጎል ጋር ካደረጉት ቃለምልልስ የተቀነጨበ። ሙሉው ቃለምልልስ ከዚህ በታች ቀርቧል።

ዛጎል፡- ተደስተሃል?

ኦባንግ ፡- በምኑ? ለምን? ምን አዲስ ነገር አለና?

ዛጎል፡- ኢህአዴግን የሰብዓዊ መብቶች ይዞታና አጠቃላይ አስተዳድሩን የሚወቅስ የህግ ረቂቅ ዛሬ በመጽደቁ፤
ኦባንግ፡- ጥሩ እርምጃ ነው። ግን አስቀድሜ ስለማውቀው ብዙም አልገረመኝም። አሜሪካኖቹ እንዲህ ወዳለው ድምዳሜ እንደሚመጡ ይገባኝ ነበር። እዚህ መድረሱ ትልቅ ጉዳይ ቢሆንም ብዙ ርቀት መሄድ ያስፈልጋል። ገና ብዙ ይቀረናል።

ዛጎል፡- ከኢህአዴግ ወገን ያሉ ወሳኔው አያሳስብም እያሉ ነው። ትስማማለህ ማለት ነው?

ኦባንግ፡- ምን ማለትህ ነው?

ዛጎል፡- ገና ብዙ መንገድ ይቀረናል እያልክ መሰለኝ፤

ኦባንግ፡- አልተግባባንም። በየትኛውም መስፈርት ይህን የህግ ረቂቅ ቀላል አድርጎ የሚወስድ አካል ካለ ከመገረም ውጪ የምለው ነገር የለም። ግን ሥራው አልተጠናቀቀም እና ገና ብዙ ይቀራናል ለማለት ነው። ሥራው አላለቀም።

ዛጎል፡- አስቀድሜ አውቀው ነበር አለከኝ? እንዴት? አንተ ማን ነህ?

ኦባንግ፡- እኔ ኦባንግ ነኝ። (ይስቃል …) ሥራው ሲሰራ ነበርኩ ለማለት ነው። ረቂቁ ከመቅረቡ ቀናት በፊት ስለ ጉዳዩ በቂ እውቀት ነበረኝ። አብረንም …. ብቻ ይህ ጠቃሚ አይመስለኝም። ሌሎች ጉዳዮች ላይ እንነጋገር።

ዛጎል፡- ታዲያ አስቀድመህ ለምን አልገለጽከውም?

ኦባንግ፡- ማውራቱ ምን ይጠቅማል? ቀጣዩ ሥራ ላይ ትኩረት ማድረጉ ነው የሚጠቅመው።

ዛጎል፡- እና ቀጣዩ ጉዳይ ምንድን ነው?

ኦባንግ፡- በተቀናቃኝ ፓርቲዎች ዙሪያ ያለው ግብግብ ሊቆም ይገባል። የጋር ግብና ራዕይ አስፈላጊ ነው።

ዛጎል፡- አንግባባም፤ እንደየ እምነታችን እንጓዛለን ካሉስ?

ኦባንግ፡- አዩት እኮ!! እንደዚህ አይነቱ ሩጫ የትም አላደረሰም። በሄየድንበት ቦታ ሁሉ የምንጠየቀው አገራዊ ራዕይና ጥልቀት የላችሁም የሚለውን ወሳኝ ጥያቄ ነው።

ዛጎል፡- የጋራ ዓላማና ራዕይ ሊይዙ ያልቻሉበትን ምክንያት ታውቀዋለህ? ወይም ደርስህበታል?

ኦባንግ፡- ምርምር የሚያስፈለገው ጉዳይ አይመስለኝም። አገርን፣ ሕዝብን፣ መጪ ትውልድን የሚያስቡ አካላት የጋራ ራዕይ ለመቅረጽ አይቸገሩም። ይህንን ለማድረግ አገላጋይና ሸምጋይ አያስፈልግም። ስለ አገር፣ ስለ ሕዝብ፣ ስለ መጪ ትውልድ በቃል ሳይሆን በተግባር የማያስቡ ስለ ምን እንደሚያስቡ መናገሩ አሰስፈላጊ አይመስለኝም፤ ግልጽ ነው። ስለዚህ በመከፋፈል፤ በመበጣጠስ የትም አይደረስም። ስትበጣጠስ ታንሳለህ። ስትበጣጠስ ሳታስበው ሳይከፈልህ የምትታገለውን ድርጅት እያገዝክ ነው ማለት ነው። በግልጽ ቋንቋ ለኢህአዴግ እና ለወያኔ ትሠራለህ፣ ታገለግላለህ፣ ትገዛለህ፣ ትኖራለህ … ማለት ነው። በዛው ነጻ ሰው የመሆን እድል ሳይገጥምህ ታልፋለህ ማለት ነው።

ዛጎል፡- ኢህአዴግ መንግሥት ነው። ለምን ወያኔ ትላለህ? በመንግሥት ደረጃ እያነሳን ብንነጋገር፤

ኦባንግ፡- ችግር የለብኝም። ግን ስማቸው እኮ ነው። እነሱ እንዲጠሩበት የሚወዱትን ስም እኔ ምን አግብቶኝ እቀይረዋለሁ? ያውም አገር የሚገዙበት ስማቸው እኮ ነው፤ ተገንጣይ ቡድን አይደል የሚባለው፤ … ለማንኛውም እነሱ ሲቀየሩት ያኔ እኔም በአዲሱ ስማቸው እጠራቸዋለሁ። ብዙ ጊዜ በዚህ ጉዳይ የሚነሳ ክርክር ይገርመኛል። እኔ ኦባንግ ነኝ ። ሌላ ሰው ተነስቶ እንዴት ኦባንግ ትለዋልህ ቢልህ መልስህ ምንድን ነው? የሰውየውን ጤንነት አትጠራጠርም? አንድን አካል በስሙ መጥራት ግድ ነው። ክብርም ነው። አንተ መንግሥት ነው ትላለህ፤ እነሱ አሁን አገር እየገዙ ያሉት በውሸት ስም አይደል? ወይ የንግሥና ስም አይደል! በነገርህ ላይ ይህ የሰብዕና (ፐርሰናሊቲ) ችግር ያመጣል፤ ለምሳሌ መለስ ማነው? መለስ ነው? ወይስ ለገሠ? ስሙ ደግሞ የተቀየረው ሲጠቀምበት ቆይቶ ካደገ በኋላ ነው፤ በልጅነቱ እንኳን አይደለም፤ ስምና ማንነት የተያያዘ ነው፤ ብቻ ተወው ወደ ሌላ ርዕስ ይወስደናል፤

ዛጎል፡- ወደ ተነሳንበት እንመለስ፤ ስለዚህ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ችግራቸው የስልጣን ጥማት ነው እያልክ ነው?

ኦባንግ ፡- ሕዝብን ለመታደግ፣ አገርን ለመታደግ፣ የወደፊቱ ትውልድ ነጻና ተስፋ ያለው እንዲሆን ካሰብክ እንዴት የጋራ ራዕይና ግብ እንዲኖርህ አትስማማም? ተበጣጥሶ የመደራጀቱ ጣጣ ያው ለስልጣን ያለ ጉጉት እንጂ አገርና ህዝብን የሚጠቅም አይደለም።

ዛጎል፡- በብሔር መደራጀት ግድ ነው? አሁን በብሔራዊ ደረጃ ታግሎ ውጤት ማምጣት አይቻልም የሚሉ አሉ፤ እነዚህ ክፍሎች የትግሉ ደረጃ በብሔር ተቧድኖ ወደ መደራጀት አድጓል ባይ ናቸው፤

ኦባንግ፡- ውጤቱ መጨረሻ ላይ ምን ይሆናል? ይህንን ጥያቄ ይመልሱታል? ለምንስ እሳካሁን ውጤት ሳያመጡ ቀሩ? አሸንፈው በተራቸው ሌላውን ለመጫን ነው የሚመኙት? እኔ የምመራው ድርጅት “ሁላችንም ነጻ ካልወጣን ማንም ብቻውን ነጻ አይወጣም” የሚለው ያለምክንያት አይደለም፤ የተበደሉት ሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች ናቸው። የተገፉትና የሚሰቃዩት ሁሉም የህብረተሰብ ክፍሎች ናቸው። ታዲያ ሁሉም የሚበደሉ ከሆነ ሁሉም ለምን ነጻ እንዲወጡ አይደረግም። በኢትዮጵያ ማዕቀፍ ውስጥ ይህንን ማድረግ የሚቀል ሆኖ ሳለ ወደፊት የማይቀረፍ ችግር ለመትከል መምረጥ ለኔ አግባብ ሆኖ አይታየኝም። ህዝብንም ይጎዳል። የህዝብም ፍላጎት አይመስለኝም።

ዛጎል፡- የምታነሳው ሃሳብ በጣም ቀላልና ግልጽ ነው፤

ኦባንግ፡- ቀና ስትሆን ቀላልና ግልጽ ነገር ታስባለህ። በቀናነት መንገድ ውስጥ ውስብስብ ነገር የለም። እኔ ይህን የምናገረው ተመራማሪ ሆኜ አይደለም። ሁልጊዜ ነገሮችን በቀናነት የመመልከት እምነትና ፍላጎት ስላለኝ ብቻ ነው። የክፋት ፖለቲካ ለማራመድ የሚወስን ልብና እምነት ቢኖረኝ በአኙዋክ ወንድሞቼ ላይ ዕልቂት በተፈጸመ ማግስት አውሬ መሆን እችል ነበር። ግን የትም አያደርስም። ሁሉም ኢትዮጵያዊ ወግኖቼ ነጻ የሚወጡበትን መንገድ ማሰቡ ነው የቀለለኝ። ብዙ ማለት ይቻላል…

ዛጎል፡- ታዲያ ለማቀራረብ ሞክረሃል? ወይስ ታስባለህ? ወይስ …

ኦባንግ፡- ሞክሬ ነበር የሚሰማ አልተገኘም። ካሁን በኋላ አልሞክረውም። እኔ በፕሮፓጋንዳ አላምንም። ለመተማመን ቅድሚያ እርስ በርስ እንነጋገር ብዬ ጥሪ አስተላልፌ አይቸዋለሁ። እኔ የማምነው በመነጋገር ነው። ቅድሚያ አንዱ ከሌላው ጋር ሩቅ ሳይሄድ መነጋገር ሲጀምር ነገሩ ሁሉ ያለ ፕሮፓጋንዳ ይሆናል። አሁን ወያኔዎቹ ብቻቸውን ቲቪ፣ ራዲዮ፣ ጋዜጣ … ሁሉን ይዘው የፕሮፓጋንዳ ዘመቻ ያደርጋሉ። በተግባር የሚታየው ግን ብቻቸውን ተጠቃሚ ሲሆኑ፣ ራሳቸው ብቻ ሲበለጽጉ፣ ሌላውን ሲገድሉ፣ ሲያሳድዱና ሲያፈናቅሉ፣ ሲያስሩ፣ … ወዘተ ነው። ተመሳሳይ ነገር መድገም አልፈልግም። ሊሆንም አይገባም። ሰው ሁሉም ክቡር። ሁሉም ክቡር ከሆኑ በታማኝነትና በከበረ ስብዕና ሁሉም ነጻ እንዲወጡ ለማሰብ አንዱ ለሌላው ቀሰቃሽና ሰባኪ ሊሆን አይገባም። ተለይቶ ነጻ የሚወጣና ተለይቶ ቀንበር የሚጫንበት ሰው ሊኖር አይገባም። የሁሉንም ጥያቄ በኢትዮጵያ ማዕቀፍ ውስጥ መመለስ ይቻላል። ይህ ሲሆን ማየት ከስልጣንም፣ ከግል ዝናም፣ ከሁሉም ዓይነት ፍላጎት በላይ ነው። ይህ ሲሆንና ሕዝብ ሲከበር፣ ቀናነት ሲታከልበት የግል ጉዳዮች፣ ተከታይ ለማግኘት የሚደረግ ሩጫ፤ የጎሳና የዘር መቧደን ይቀራል። ለምን? ምክንያቱም ከትግሉም ሆነ ከድሉ ህዝብ የሚያገኘውን እፎይታ በማየት ከእርካታ የዘለለ የምትፈልገው ነገር የለምና፤

ዛጎል፡- አሜሪካና ኢህአዴግ አሁን በመልካም ግንኙነት ላይ ያሉ ይመስለሃል?

ኦባንግ፡- በአጭሩ አይመስለኝም።

ዛጎል፡- እንዴት? ሁሌም አሜሪካኖቹ አጋራችን ነው የሚሉት፤

ኦባንግ፡- እነሱ ገፍተው የገደል አፋፍ ላይ ቢያስቀምጡህ እንኳ ክፉ ቃል አይጠቀሙም። በተግባር ግን ያሳያሉ። በጀት ሲቀንሱ ምልክት ነው። የጦር ካምፓቸውን ሲያነሱ ምልክት ነው። ፊት ሲነሱ ምልክት ነው። ከሶማሌ እንዳትወጣ እያሉ ሲለምኑና ዶላር ሲያፈሱ ኖረው የራስህ ጉዳይ ካሉህ ትልቅ ምልክት ነው። መከርንህ፣ ነገርንህ አሁን የራስህ ጉዳይ ነው፣ ለራስህ እወቅ፣ ሁሉም ነገር ባንተ እጅ ነው ሲሉህ ምልክት ነው። ከዚህም በላይ አሁን ኢትዮጵያ እየሄደች ያለችበት መንገድ ወዴት እንደሚያደርሳት ጠንቅቀው ያውቃሉ። ወያኔዎቹ በዘላቂነት ምስራቅ አፍሪቃ እና አካባቢው ላይ ያላቸውን ፍላጎት የማስጠበቅ አቅማቸው መዛሉን ያውቃሉ። ከውስጥ የተነሳው ችግርና አገዛዙ የገባበት የቀውስ ገደል መጨረሻ ከማንም በላይ ይታያቸዋል። ተወደደም ተጠላም አሁን ነገሮች እየከበዱ ነው። እነሱ እንዳሉት ምርጫው በባለስልጣኖቹ እጅ ላይ ነው።

ዛጎል፡- አዲሱ ረቂቅ ህግ የሚጠይቀውን አንቀበልም ቢሉስ?

ኦባንግ፡- አይመስለኝም።

ዛጎል፡- እንደ ቀድሞው ረቂቅ HR 2003 ቢያስገለብጡትስ? ያንን የማድረግ አቅም እንዳላቸው የሚናገሩ አሉ፤

ኦባንግ፡- በዛሬው ሁኔታ፣ በቅርብ እንደማውቀውና በግል እንደማምነው አዲሱን ረቂቅ በሎቢ ማስቀየር የሚቻል አይመስለኝም። ተራ ቀልድ ነው የሚሆነው። የተስማሙት ሁለቱም ፓርቲዎች ናቸው። በኢትዮጵያ ያለው የሰብዓዊ መብት አያያዝና ስርዓቱ የገባበት ውድቀት ከልክ በላይ ሆኗል። በአራቱም ማዕዘናት የሚታየው ሁሉ አያምርም። ወያኔዎቹም ቢሆኑ በራሳቸው ሚዲያ ሆን ብለው ይሁን ሳያውቁ የሚያቀርቡት ዘገባና ዜና ይህንኑ የሚያረጋግጥ ነው። አንዳንድ የመፍትሄ ርምጃ በሚል የሚወሰዱት ሁሉ የመደናበር ምልክት ነው። እናም በዚህ መልኩ የሚቀጥል ነገር አይኖርም።

ዛጎል፡- እና ህጉ በሙሉው ምክርቤት (በኮንግረስ) ቀርቦ ተግባራዊ ይሆናል እያልክ ነው?

ኦባንግ፡- በመጀመሪያ የአድቮኬሲ ስራ የትም አያደርስም ለሚሉ ወገኖች ይህ ትልቅ ትምህርት መሆኑንን መግለጽ እወዳለሁ። ከሌሎች ችግሮች ጋር ተዳምሮ የአድቮኬሲ ስራ ፍሬ አፍርቶ በማየቴ ደስተኛ ነኝ። ጉዳዩ ብዙ የተደከመበት ነው። እንዲሁ ወደዚህ ሃሳብ አልተደረሰም። እናም አሁን ባለው ሁኔታ ህጉ በኮንግረንስ ጸድቆ ተግባራዊ ይሆናል። አስቀድሜ እንዳልኩት አድርጉ የሚባሉትን አናደርግም ካሉ ተፈጻሚ የሚሆን ዓለምዓቀፍ ህግ አለ። ህጉ ኢትዮጵያውያንን በማሰቃየትና በመግደል፣ እንዲሁም የሰብዓዊ መብቶቻቸውን በመርገጥ ተግባር የተሳተፉ ለመሆናቸው የተመዘገቡ የስርዓቱ ባለስልጣኖችና ተባባሪዎች የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር  ከገንዘብ ሚኒስቴር ጋር በመቆራኘት በዓለምአቀፍ ሕግና ደንቦች መሠረት ዕቀባ እንዲያደርግባቸው በረቂቅ ሕጉ ተቀምጧል። በዚህ መነሻ ለአሜሪካ የለውጥ ዕቅድ አሻፈረኝ የሚሉ ከሆነ የአገዛዙ ሹሞችና ቤተሰቦቻቸው ወደ አሜሪካ እንዳይገቡ ማዕቀብ ይጣልባቸዋል፥ ሃብታቸው እንዳይነቃነቅ ይታገዳል። ሌሎችም ተመሳሳይ ደንቦችና ህጎች ተግባራዊ ይሆኑባቸዋል። ይህ ግድ ነው። ነገሮች ወደ መራራነት እየተቀየሩ ነው ያልኩት በዚህ መነሻ ነው። ይህ እንደሚመጣ አስቀድመው ሊያውቁትና እንመራዋለን የሚሉትን ህዝብ ሊያከብሩት በተገባ ነበር። ይህንን ስል ግን በእኛ በኩል ስራው የሚቀጥል …

ዛጎል፡- ቤተሰቦቻቸው ለምን?

ኦባንግ፡- የወያኔ ባለስልጣናት አገሪቱ ላይ የሚፈጽሙትን ወንጀልና ግፍ ቤተሰቦቻቸው አያውቁም? ለምንስ አይቃወሙም? ለምን ሌላውም ሰው ልክ እንደ እነሱ ክብር እንደሚያስፈልገው በማመን አይከራከሩም? ለምን የሌላው ስቃይ ስቃያቸው አይሆንም? አንድ የባለስልጣን ልጅ በንጹሃን ላይ የሚደርሰውን ግፍ በመመልከት የተቃወመ አለ? ስለዚህ ክሬሙን ብቻ ሳይሆን መከራውንም ሆነ ችግሩን አብሮ መጋራት ግድ ነው። ይህንን ስል ግን ጊዜ አለ። ህዝብ መሃሪ ነው። ህዝብ ይቅር ይላል። ሁልጊዜም እንደምለው እርቅ የአገራችንን ችግር የሚፈታው ብቸኛ መንገድ ነው። ወደዚያ ማምራት ከተቻለ ነገሮች ይቀላሉ። እነሱም አሁን የተባለውን ሁሉ ማድረግ ነው። ሰላም መፍጠርና ሁሉም ዜጎች እኩል ሆነው በመረጡት እንዲተዳደሩ ማድረግ … ለዚህ ተግባራዊነት ደጋፊ፣ ተቃዋሚ፣ ቤተሰብ ሳይባለ ሁሉም ከሰራ ችግሩን መቀነስና ወደ ሚፈለገው ግብ መድረስ ይቻላል።

ዛጎል፡- የኢትዮጵያ ጉዳይ ከእነ ሄዝቦላ፣ ሰሜን ኮሪያና ቬኒዙዌላ ከመሳሰሉት አገሮች ጋር በአንድነት ለወሳኔ መቅረቡን እንዴት አየኸው?

ኦባንግ፡- ሰዎቹ አስቀድሜ እንዳልኩት እንዴት እንደሚሰሩ ያውቃሉ። ይህ በራሱ ልዩ ትርጉም አለው። ከማንም በላይ ለወያኔዎቹ ይገባቸዋል። እነሱን ማግኘት ብትችልና መከራከሪያቸውን ብንሰማ…

ዛጎል፡- ረዥም ጉዞ ከፊት ለፊት አለ ብለህ ነበር፤

ኦባንግ፡- አዎ! የአሁኑ ትልቅ ድል ነው። ግን ድሉን እውን አላደረግነውም። ድሉ እውን እንዲደረግ በውጪ ያለው ሃይል ግፊቱን መቀጠል አለበት። ይበልጥ መግፋት አለበት። ዛሬ የተደረሰበት ደረጃ የሚያኮራና ደረት የሚያስነፋ ተደርጎ መታየት የለበትም። ተግባራዊ ሲሆን ለማየት ተቃዋሚ ፓርቲዎች በአስቸኳይ የጋራ ራዕይ ሊያበጁና አስተማማኝ አማራጭ መሆናቸውን ሊያሳዩ ይገባል። በሁሉም ዘርፍ ይበልጥ እንድንሰራ የሚያበረታታ ወቅት ላይ በመሆናችን ይበልጥ ጠንክረን ልንሰራ ይገባል።

ዛጎል፡- የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ በተለይ የሚያደርገው ነገር ይኖራል?

ኦባንግ፡- ከሂውማን ራይትስ ዎች፣ ከአምነስቲና ሰብአዊ መብት ላይ ከሚሰሩ ተቋማት ጋር ብዙ ሰርተናል። ዝርዝር ውስጥ መግባትና ይህንን አደረግን የሚለውን ጉዳይ እዚህ ላይ አልፈዋለሁ። ሆኖም ግን ስራው እንደሚቀጥል አውቃለሁ። ድርጅታችን በመርህ ላይ ተመስርቶ የሚሰራ፣ ሲሞቅና ሲበርድ የሚቀያየር፣ እንደ ወቅቱ ከፍና ዝቅ የሚል ግብ አስቀምጦ የሚሰራ ባለመሆኑ በአስቀመጠው ግብ መሰረት ከአጋሮቹ ጋር ይሰራል። ጫና መፍጠር ከሚችሉ ብዙ ድርጅቶች ጋር ሰርተናል። እየሰራን ነው። አሁንም እንሰራለን። አዲስ ነገር የለም። አዲስ ነገር የሚፈጠረው ዓላማችን ሲሳካ ብቻ ነው።

ዛጎል፡- ኢህአዴግ ቻይናን በአማራጭ በመያዙ የአሜሪካንን ጫና ወይም ማዕቀብ ሊቋቋም እንደሚችል፣ እንደውም ለማስፈራሪያነት እንደሚጠቀም የሚናገሩ አሉ፤

ኦባንግ፡- ቻይና እንደ አሜሪካ በጀት እየበጀተች፣ ሰፊ ድጋፍ እየሰጠች፣ እየደጎመች የምትገፋ አይመስለኝም። እንዲህ ያለው መላምት ለጊዜው ቀልድ ነው ብሎ ከማለፍ የዘለለ ምላሽ የለኝም።

ዛጎል፡- አሁን በአገር ቤት ተቃዋሚ የሚባሉት የፖለቲካ ድርጅቶች እየተደራደሩ መሆኑ ሰምተሃል?

ኦባንግ፡- አዎ! እንዴት አልሰማም?

ዛጎል፡- እንዴት አየኸው? አንድ ትልቅ እርምጃ ነው የሚሉ አሉ፤

ኦባንግ፡- መነጋገር ጥሩ ነው። ካለመነጋገር የተሻለ ነው። ለመነጋገር ግን የምታናገረው ሌላ፣ የተለየ አቋም ያለው አካል ያስፈልጋል። እስከሚገባኝ አሁን አሁን የሚካሄደው ድርድር አይደለም። በሺህ የሚቆጠሩ ዜጎች፣ ፖለቲከኞች፣ የፓርቲ መሪዎች፣ ጋዜጠኞች፣ ወዘተ እስር ቤት ታሽገው ምን አይነት ንግግር ነው የሚደረገው። ስለማንስ ነው ለመነጋገር የሚቀመጡት? ማንን ነው የሚወክሉት? እነዚህ ጥያቄዎች ሲመለሱ በሚነጋገሩት አካላት መካከል ልዩነት አይታይም። ልዩነት ከጠፋ ድርድር የለም ማለት ነው። እያሰርክ፣ እየገረፍክ፣ ቶርቸር እያደረክ፣ ያሻህን እያደረክ እንደራደር ብሎ ነገር ያለ አይመስለኝም። ካለ ምን አልባትም ይህ በታሪክ የመጀመሪያ ነው። ቅድም ያልኩት ጉዳይ እዚህ ላይ ይነሳል።

ዛጎል፡- ምኑ?

ኦባንግ፡- የመንፈስ ልዕልና፣ የህሊና ጉዳይ፣ ከሁሉም በላይ ስልጣን የመመኘት አዝማሚያ። አሁን ኢትዮጵያ ባለችበት ሁኔታ ስለ ስልጣን ማሰብ፣ አቋራጭ መንገድ መመኘት፣ የጋራ አገራዊ አጀንዳ እንዳይኖረን የሚያደርጉ አደገኛ በሽታዎች ናቸው። በዚህ ችግር ውስጥ እስካለን ድረስ የወያኔ አገልጋይ እንጂ የህዝብ ወኪል ልንሆን አንችልም። ኢትዮጵያ ብሄራዊ ችግር እንጂ የጎሳ፣ የብሄርና የተበጣጠሱ ጎሳዎች ድርጅት ችግር የለባትም። ብሄራዊ ችግር የሚፈታውና መፍትሄ የሚያገኘው በብሄራዊ አጀንዳ ነው። ብሄራዊ አጀንዳ ደግሞ ወደ ጋር ግብ ያደርሳል። የጋራ ግባችን ራስን ጨምሮ ሁሉንም ነጻ ማውጣት ከሆነ የማንም አገልጋይና ተገዢ መሆን የለም። ለማንም እንደማይገዛና እንደማያጎበድድ የተረዳ ሰው የሚያደርገውን ሁሉ በነጻነት ያደርጋል። ያንን ዘመን ለማየት ራዕይ ሰንቆ መጓዝ በታሪክም በትውልድም ፊት ታላቅ ዕልናን ያቀዳጃል። የፍቅርና የቀናነት ምሳሌ ያደርጋል። አሁን የራበን ይህ ነው። አመሰግናለሁ!!