August 13, 2017

ጋዜጠኛ ግርማዬነህ ማሞ

በኢትዮጵያ ነፃ ፕሬስ ታሪክ ስመ ጥሩ በሆኑት በርካታ ጋዜጦችና መጽሔቶች ላይ በአዘጋጅነትና በከፍተኛ ዘጋቢነት የሠራው ግርማዬነህ፤ በአቶ ክፍሌ ሙላት ይመራ የነበረው የኢትዮጵያ ነፃ ፕሬስ ጋዜጠኞች ማኅበር አባል ሲሆን በሕዝብ ዘንድ ተነባቢና ተወዳጅ መሆን በቻሉት የኢትኦጵና የዓባይ ጋዜጣና መጽሔት ዝግጅት ክፍል ከፍተኛ የዘጋቢነትና የአዘጋጅነት ድርሻውን ሲወጣ የቆየ መንፈሰ-ብርቱ ጋዜጠኛ ነበር፡፡

ጋዜጠኛ ግርማዬነህ ማሞ ከኢትኦጵና ከዓባይ በተጨማሪ፤ በጦማር፣ በኢትዮ ታይም፣ በታዛቢ ጋዜጦች፤ እንዲሁም በትውልድ ጋዜጣና መጽሔት ላይ በዘጋቢነትና በቃለ-መጠይቅ አቅራቢነት ሠርቷል፡፡ በጉራማይሌ መጽሔትም ላይ በአዘጋጅነትና በዘጋቢነት የሠራው ግርማዬነህ፤ በመጨረሻም በሐምራዊ እና በዕንቁ መጽሔቶች ላይ ከፍተኛ አዘጋጅ በመሆን መጽሔቶቹ በአንባቢያን ዘንድ ተፈላጊና ተወዳጅ እንዲሆኑ ሙያዊ አስተዋጽኦ አበርክቷል፡፡

በአንጋፋው የኢትዮጵያ መምህራን ማኅበር ከዶክተር ታዬ ወልደሰማያት ጋር በመሆን የመምህራን ማኅበሩን ልሳን ሲያዘጋጅ የነበረው ግርማዬነህ ከፕሮፌሰር መስፍን ወልደማርያም እና ከሟቹ ዶክተር መኮንን ቢሻው ጋር በመሆን በኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብቶች ጉባዔ (ኢሰመጉ) የሰብዓዊ መብት ጥሰቶችን በመከላከልና በማጋለጥ ረገድ የበኩሉን ዜግነታዊ ድርሻ ተወጥቷል፡፡ የጦማር ጋዜጣ አዘጋጅ በነበረበት ጊዜ ከአንድ ዓመት በላይ ታሥሮ የነበረው ጋዜጠኛ ግርማዬነህ ባለትዳርና የአንዲት ሴት ልጅ አባት ነው፡፡

ጋዜጠኛው ዛሬ በተዘነዓ ሆስፒታል ሕክምናውን በመከታተል ላይ የሚገኝ ሲሆን ምንም ዓይነት ገቢ የሌለው በመሆኑ የኢትዮጵያውያን ወገኖቹን ዕርዳታ ይፈልጋል፡፡

ጋዜጠኛ ግርማዬነህ ማሞ ከ1983 ግንቦት ወር በፊት የኢትዮጵያ ሠራዊት ባልደረባ ነበር፡፡

ለመርዳት ለምትሹ የጎ ፈንድ ሚ ሊንክ ይኸው…