Sunday, 20 August 2017 00:00
Written by አለማየሁ አንበሴ
መንግስት አስፈላጊው እርዳታ እየተደረገ ነው ብሏል
በኢትዮጵያ በ7 መቶ ሺህ ዜጎች ላይ የረሃብ አደጋ ማንዣበቡን ኦክስፋም ያስታወቀ ሲሆን በተለይ በሱማሌ ክልል የተፈጠረው የድርቅ ችግር፣ በርካታ ማህበራዊ ቀውሶችን እያስከተለ መሆኑ ተጠቁሟል።
-
በቅርቡ የኢትዮጵያ መንግስትና አለማቀፍ ተቋማት በጋራ ባወጡት መግለጫቸው፤ የድርቅ ተረጅዎች ቁጥር 8.5 ሚሊዮን መድረሱን ማስታወቃቸው የሚታወስ ሲሆን ኦክስፋም በበኩሉ፤ ከነዚህ ውስጥ 7 መቶ ሺህ ያህል ዜጎች በከፍተኛ የረሃብ አደጋ ስጋት ውስጥ መሆናቸውን ከትናንት በስቲያ አስታውቋል፡፡
የምግብ እጥረቱና ረሃቡ በተለይ በሶማሌ ክልል ፀንቷል ያለው ኦክስፋም፣ ዜጎችም ከቀዬአቸው እየተፈናቀሉ መሆኑን ጠቅሶ፤ በዚህም ህፃናት ለጉልበት ብዝበዛና ያለ እድሜ ጋብቻ ችግሮች እየተጋለጡ ነው ብሏል፡፡
በሶማሌ ክልል የሚገኙት ዶሎ፣ ቆራሄ፣ አፎዴርና ጀራር ዞኖች በድርቁ በእጅጉ የተጎዱ መሆኑን የጠቆመው ኦክስፋም፤ በአካባቢዎቹ የአጣዳፊ በሽታ ወረርሽኝ ማንዣበቡንም ገልጿል፡፡መንግስት በበኩሉ፤ ለድርቅ ተረጂዎች አስፈላጊው እርዳታ እየተደረገ መሆኑን አስታውቋል፡፡ - አዲስ አድማሰ