Wednesday, 23 August 2017 12:34

የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ የአማራና ቅማንት ሕዝቦች ተቀላቅለው በሚኖሩባቸው 12 ቀበሌዎች ሕዝበ ውሳኔ ለማካሄድ ቅድመ ዝግጅት ጀመረ። በዚህ መሠረት ቦርዱ የሕዝበ ውሳኔው መስከረም 7 ቀን 2010 ዓ.ም እንዲካሄድ በማቀድ የአፈጻጸም የጊዜ ሰሌዳ ማውጣቱን ይፋ አድርጓል፡፡

ቦርዱ የአማራና ቅማንት ሕዝቦች ተቀላቅለው የሚኖሩባቸው 12 ቀበሌዎች ሕዝበ ውሳኔ እንዲያካሂድ በፌዴሬሽን ምክር ቤት በቀረበለት ጥያቄ መሠረት በማድረግ ቅድመ ዝግጅቶች መጀመሩን በቅርቡ በአምባሳደርነት የተሾሙት የቦርዱ ሰብሳቢ ፕሮፌሰር መርጋ በቃና መግጳቸውን ከቦርዱ የህዝብ ግንኙነት ክፍል ያገኘነው መረጃ ይጠቁማል።

ባሳለፍነው ወር የቦርዱ ፅ/ቤቱ የቴክኒክ ጉዳዮችን ለመመርመር አንድ ቡድን ወደ ቦታው በመላክ የቅድመ ዝግጅት ዳሰሳ ጥናት ማካሄዱንና ስንት ምርጫ ጣቢያዎች ማቋቋም እንዳለበትና ስንት የምርጫ አስፈፃሚዎችና የሕዝብ ታዛቢዎች ማሰማራት እንዳለበት  መለየቱን ቦርዱ አሳውቋል።

የአሁኑ ስብሰባም በሕዝበ ውሳኔ አፈፃፀም የጊዜ ሰሌዳ/ ረቂቅ ላይ ለመመካከርና የአማራና ቅማንት ሕዝቦች ተቀላቅለው በሚኖርባቸው 12 ቀበሌዎች በሚካሄደው ሕዝበ ውሳኔ የአፈፃፀም ማብራሪያ ላይ  ከክልሉ መስተዳድር አካላት እና በክልሉ የተዋቀሩ የሁለቱ ሕዝቦች የጥምር ኮሚቴ አባላት ጋር ጥልቅ ውይይት ተካሂዷል።

የአማራ ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ምክርቤት አፈ ጉባዔ አቶ ይርሳው ታምሬ በአካባቢው የነበሩትን ጥያቄዎች አብዛኛዎቹ ከሕዝብ ጋር በመወያየት፣ በመግባባት እና በመተማመን የተፈቱ መሆናቸውን በማስታወስ ሕዝበ ውሳኔ የሚካሄድባቸው 12 ቀበሌዎች ግን በሕዝብ ውሳኔ መፍትሄ እንዲያገኙ በሁለቱ ወገኖች ለፌዴሬሽን ምክር ቤት ጥያቄ መቅረቡን አስታውሰው፤ ምርጫ ቦርዱ በነዚህ አካባቢዎች ለሚያካሂደው ሕዝበ ውሳኔ አስፈላጊውን ትብብርና ድጋፍ እንደሚደረግና ሕዝበ ውሳኔው ሠላማዊና ዴሞክራሲያዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ እምነት እንዳላቸው ተናግሯል። በመቀጠልም የሁለቱ ህዝቦች በሠላም አብሮ የመኖር ታሪካቸውን የሚያጠነክርና የሚያጎለብት ሕዝበ ውሳኔ እንደሚሆን ያላቸውን እምነት ገልጿል።

በሁለቱ ህዝቦች ለዘመናት የዘለቀውን ተቻችሎና ተግባብቶ አብሮ የመኖር ግንኙነትና ዝምድና የሚጠናከርበት፣ ችግሮች ተወግደው ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ልማታቸው የሚጎለብትበት፣ የሕዝቦቹ ዘላቂ ሠላምና ብልፅግና የሚረጋገጥበት ሕዝበ ውሳኔ እንዲሆን የበኩላቸውን እንደሚወጡ የመድረኩ ተሳታፊዎች አረጋግጧል።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ በኢ.ፌ.ዲ.ሪ. ሕገ መንግሥት አንቀጽ 102 እና በተሻሻለው የኢትዮጵያ የምርጫ ሕግ አዋጅ ቁጥር 532/1999 ዓ.ም. መሠረት የተቋቋመ ተቋም እንደሆነና፤ ቦርዱ ግዙፍ ሕዝባዊና ሕገ-መንግሥታዊ ኃላፊነት ተሸክሞ ወደ ሥራ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ በየአምስት ዓመቱ በተከታታይ የሚካሄዱ ምርጫዎችን የጠቅላላ ምርጫ አምስት ጊዜ፣ የአካባቢ ምርጫ አምስት ጊዜ እንዲሁም በተለያዩ ደረጃ የምርጫ ዓይነቶች ማለትም የማሟያ ምርጫ፣ ድጋሜ ምርጫ እና ሕዝበ-ውሳኔዎችን ነፃ፣ ፍትሃዊ፣ ዴሞክራሲያዊ እንዲሁም በሕዝብ ዘንድ ተዓማኒ ሆነው እንዲጠናቀቁ በማድረግ በርካታ ልምድ ያካበተ ተቋም ነው።

ሕዝበ ውሳኔ ማለት በኢ.ፌ.ዲ.ሪ ሕገ መንግስት ሲወሰን የህዝብ ፍላጎትን ለመለካት እና የሕዝብን ውሳኔ ለማወቅ ድምፅ የሚሰጥበት ሥርዓት ነው። በዚሁ መሠረት ቦርዱ ከተቋቋመበት ጊዜ ጀምሮ በርካታ የሕዝበ ውሳኔ ምርጫዎችን በብቃት በማካሄድ የህዝቦችን የሉዓላዊ ስልጣን ባለቤትነትን አረጋግጧል። ለአብነት ለመጥቀስ የቤጊ ሕዝበ ውሳኔ፣ በኦሮሚያና በኢትዮጵያ ሶማሌ አዋሳኝ ቀበሌዎች፣ እንዲሁም በኦሮሚያ እና በደቡብ ብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች ክልሎች አዋሳኝ በሆኑት ቀበሌዎች ላይ የተካሄዱ ሕዝበ ውሳኔዎች ሠላማዊና ዴሞክራሲያዊ በሆነ መንገድ መጠናቀቃቸውን ይታወሳል፡፡

የኢትዮጵያ ብሔራዊ የምርጫ ቦርድ የአማራና የቅማንት ሕዝቦች ተቀላቅለው በሚኖርባቸው 12 ቀበሌዎች ለሚካሄደው ሕዝበ ውሳኔ አፈፃፀም ያጸደቀው የጊዜ ሰሌዳ እነሆ።

የኢትዮጵያ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ

የአማራና የቅማንት ሕዝቦች ተቀላቅለው በሚኖሩባቸው 12 ቀበሌዎች ለሚካሄደው ሕዝበ ውሳኔ አፈፃፀም የጊዜ ሰሌዳ

ነሐሴ 2009 ዓ.ም

ተ.ቁ

ክንውን

ቀን

1

በህዝበ ውሳኔው የጊዜ ሰሌዳ እና የህዝብ ውሳኔ ማስፈጸሚያ ማብራሪያ ላይ ውይይት የሚደረግበት፤ ነሐሴ 10 ቀን 2009 ዓ.ም

2

ለህዝበ ውሳኔው አስፈፃሚዎች ስልጠና የሚሰጥበት፤ ነሐሴ 24 እና 25 ቀን 2009 ዓ.ም

3

ለህዝበ ውሳኔው የህዝብ ታዛቢዎች ምርጫ የሚካሄድበት፤ ነሐሴ 28 ቀን 2009 ዓ.ም

4

ስለህዝበ ውሳኔው የድምፅ አሰጣጥ ሂደት ለህዝቡ ገለፃ የሚሰጥበት፤ ነሐሴ 28 ቀን 2009 ዓ.ም

5

ለህዝበ ውሳኔው ድምፅ ሰጪዎች ምዝገባ የሚከናወንበት፤ ነሐሴ 29 ቀን 2009 ዓ.ም እስከ መስከረም 3 ቀን 2010 ዓ.ም

6

የህዝበ ውሳኔው የመራጮች መዝገብ ለህዝብ ክፍት ሆኖ የሚቆይበት፤ ከመስከረም 4 እና 5 ቀን 2010 ዓ.ም

7

የህዝበ ውሳኔው ቅሬታ በየደረጃው የሚቀርብበት እና ውሳኔ የሚሰጥበት፤ ነሐሴ 29 ቀን 2009 ዓ.ም እስከ መስከረም 12 ቀን 2010 ዓ.ም

8

የህዝበ ውሳኔው የድምፅ መስጫ ዕለት፤

መስከረም 7 ቀን 2010 ዓ.ም ከጠዋቱ 12፡00 ሰዓት እስከ ምሽቱ 12፡00 ሰዓት

9

ድምፅ አሰጣጡ እንደተጠናቀቀ የህዝበ ውሳኔ ድምጽ ቆጠራ የሚጀመርበት፤ መስከረም 7 ቀን 2010 ዓ.ም ከምሽቱ 12፡00 ሰዓት ጀምሮ

10

የህዝበ ውሳኔው የድምፅ ቆጠራ በድምፅ መስጫ ጣቢያው በይፋ የሚገለፅበት፤ መስከረም 8 ቀን 2010 ዓ.ም

11

የህዝበ ውሳኔው የድምጽ ቆጠራ ውጤት ተጠናቅሮ ለፌደሬሽን ምክር ቤት የሚላክበት፡፡ መስከረም 15 ቀን 2010 ዓ.ም

 

 

የቅማንት ማህበረሰብ ራሱን በራሱ እንዲያስተዳድር ስለመወሰኑ፣

የአማራ ክልል ምክር ቤት መጋቢት 3 ቀን 2007 ዓ.ም ባካሄደው ጉባዔ የቅማንት ማህበረሰብ ራሱን በራሱ እንዲያስተዳድር ውሳኔ ማሳለፉ አይዘነጋም፡፡ ይህንን ውሳኔ ተከትሎም በሰሜን ጎንደር ዞን የቅማንት ማህበረሰብ የራስ ገዝ አስተዳደር 42 ቀበሌዎችን እንዲያቅፍ ተደርጎአል፡፡ በቀጣይም ከሕዝቡ ጋር በተደረጉ ውይይቶች 12 ቀበሌዎች ወደራስገዙ እንዲካተቱ መደረጉ የሚታወስ ነው፡፡ በአሁኑ ሰዓት ደግሞ የአማራና የቅማንት ሕዝቦች ተቀላቅለው በሚኖሩባቸው 12 ቀበሌዎች ሕዝበ ውሳኔ እንዲካሄድ ተወስኖአል፡፡

የቅማንት ማህበረሰብ በሰሜን ጎንደር ዞን በተወሰኑ ወረዳዎች የሚገኝ እና ራሱን በራሱ ለማስተዳደር ጥያቄ ሲያነሳ የቆየ ሕዝብ ነው፡፡

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮምሽን

የቅማንት ግጭትን አስመልክቶ ምን አለ

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮምሽን ሰኔ 3 ቀን 2008 ዓ.ም ለሕዝብ ተወካዮች ም/ቤት ባቀረበው ሪፖርት የቅማንት ብሄረሰብ የማንነት ጥያቄ ተከትሎ ስለደረሰው ግጭት እንዲህ ብሏል፡፡

በሰሜን ጎንደር ዞን የቅማንት ብሄረሰብ የማንነት ጥያቄ ማቅረቡ ሕገመንግስታዊ እንደነበር የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮምሽን ሪፖርት ይጠቅሳል። ይህ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠት በክልሉ መንግስት እንዲሁም በፌዴራሉ የፌዴሬሽን ም/ቤት በኩል የተወሰዱት እርምጃዎች ግን ደካማ መሆን ለግጭቱ መፈጠር አይነተኛ ምክንያት መሆኑን አመላክቷል። እንዲሁም አጥኚ ቡድን ተቋቁሞ ጥያቄው የጥቂት ቋንቋውን ተናጋሪ ግለሰቦች አድርጎ ለማሳየት መሞከሩ ትክክል እንዳልነበር፣ ሕገመንግስቱ ቋንቋን መሠረት ቢያደርግም ቋንቋውን አንድም ሰው ተናገረው ወይም ከዚያ በላይ ሕገመንግሥቱ ያስቀመጠው ነገር እንደሌለ ተመላክቷል።

ግጭቱ ከተፈጠረ በኃላ ከሰሜን ጎንደር ዞን የተሠማራው ልዩ ኃይል በተለይ በአይከልና በማወራ ቀበሌዎች በወሰደው እርምጃ በሰላማዊ ሰዎች ላይ የሞትና የመቁሰል አደጋ እንዲከሰት ማድረጉ ተመጣጣኝና ህጋዊ ምክንያት የሌለው ነበር ብሎታል።

በኮምሽኑ ሪፖርት መሠረት ከቅማንት የማንነት ጥያቄ ጋር ተያይዞ በተከሰተ ግጭት በአጠቃላይ 97 ሰዎች ሲሞቱ 86 ሰዎች ላይ ደግሞ ቀላልና ከባድ የመቁሰል አደጋ ደርሷል።

ኮምሽኑ በሪፖርቱ ላይ ባቀረበው ምክረሃሳብ የህዝቡ ጥያቄ አግባብ ባለው ሕግ መሠረት እንዲፈታ፣ ችግሩን በማባባስ ረገድ ሚና የነበራቸው አካላት ጉዳያቸው ተጣርቶ ለፍርድ እንዲቀርቡ ጠይቋል። ሕገመንግሥቱ ለሁሉም ብሄር ብሄረሰቦች እኩል ቦታ የሚሰጥ ቢሆንም ከዚህ በፊት የተለያዩ በደሎች ለደረሰባቸው ብሄረሰቦች ልዩ ጥበቃና ድጋፍ ሊደረግላቸው እንደሚገባ በሚያዘው መሠረት የአማራ ክልል ልዩ ድጋፋ ባለማድረጉ የቅማንት ማህበረሰብን ይቅርታ ሊጠይቅ ይገባል ማለቱ አይዘነጋም።

ስንደቅ