ተቃዋሚዎች ለምርጫ ሕጉ ድርድር ዝግጅት እያደረጉ ነው

ገዥው ፓርቲ ኢሕአዴግ በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ ተቋማዊ ቅርፅ ላይ ማሻሻያ ለማድረግና የምርጫ ኮሚሽን ሆኖ እንዲቋቋም ጥናት እያከናወነ መሆኑን ምንጮች ገለጹ፡፡

የሪፖርተር ምንጮች እንደገለጹት፣ ከሳምንት በፊት በጉዳዩ ላይ የሚመክር ከተለያዩ ተቋማት የተውጣጣ ቡድን በሐዋሳ ከተማ ሲመክር ነበር፡፡

ማሻሻያው በምርጫ ቦርድ ላይ የመዋቅር ለውጥ የሚያስከትል ብቻ ሳይሆን፣ በአገሪቱ ሕገ መንግሥት ላይም ማሻሻያ እንዲደረግ የሚያስገድድ እንደሚሆን ምንጮች ገልጸዋል፡፡

ኢሕአዴግ በአሁኑ ወቅት ገና በጉዳዩ ላይ እየመከረ መሆኑን የተናገሩት ምንጮች፣ የፓርቲው ከፍተኛ አመራሮች ይሁንታን ካገኘ በመስከረም ወር መጀመርያ ላይ በሚካሄደው የኢሕአዴግና የተቃዋሚዎች የድርድር መድረክ ላይ ይቀርባል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

በመጪው መስከረም ወር መጀመርያ ላይ ሁለተኛው ዙር የፖለቲካ ፓርቲዎች ድርድር የሚጀመር ሲሆን፣ የድርድር አጀንዳውም ምርጫ ቦርድን በሚያቋቁመው የተሻሻለው የምርጫ ሕግ አዋጅ ቁጥር 532 ላይ መሆኑን፣ የድርድሩ የሚዲያ ኮሚቴ ሰብሳቢ አቶ ገብሩ በርሔ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡

በተቃዋሚዎች በኩል አሥር ተቃዋሚ ፓርቲዎች በጋራ በመሆን በምርጫ አዋጁ ላይ ሊሻሻሉ ይገባል ያሏቸውን፣ እንዲሁም ሊካተቱ ይገባል ያሏቸውን ሐሳቦች በማጠናቀር ላይ መሆናቸውን አቶ ገብሩ ገልጸዋል፡፡

የምርጫም ቦርድ አባላት አመላመል ተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችን ያካተተ እንዲሆን፣ ቋሚ የቅሬታ ሰሚ ኮሚቴ እንዲዋቀርና የቦርዱ ጽሕፈት ቤት እስከ ክልል ወረዳዎች ድረስ እንዲዋቀር የሚሉት ከቡድኑ ሐሳቦች መካከል ይገኙበታል

Source       –        Ethiopian Reporter