SEPTEMBER 4, 2017

Related image

በአንድ ወቅት ይህ አለ …

አንተ የአሁኑ ዘመን ሰው ነህ፤ ግን የቀድሞዎቹን አጼዎች ታወድሳለህ፤ ታውቃቸዋለ?  ” ስትል ጠየቀችው። ሰኮንድ ያልፈጀበት ቴዲ ” ኢየሱስን ለመውደድ በኢየሱስ ዘመን መወለድ አያስፈልግም “

 

ቴዎድሮስ ካሳሁን ዜና የሆነው ገና የመጀመሪያውን አልበሙን ሲያቀርብ ነው። ከዛን ጊዜ ጀምሮ ኑሮው፣ ርምጃው፣ ውሎው፣ ምግባሩና ተግባሩ … ሁሉም ነገሩ ዜና ሆኖ እስካሁን ዘልቋል። የሚወዱት እንደ አሸን በየእለቱ የሚፈለፈሉትን ያህል የሚጠሉት ጥቂት የማይባሉ ክፍሎችም አሉ። ከሁሉም በላይ በድርጀት ደረጃ አገሪቱን በሚገዛው ኢህአዴግ፣ በተለይም በህወሃት አለመወደዱ የንጋት ሃቅ ነው። በድርጅት ስል ለይቶ ለመመልከት እንዲቻል እንጂ ከኢህአዴግ ውስጥ ከፓርቲው አመለካከት ውጪ በማፈንገጥ የሚወዱት ቁጥራቸው ይበዛል። በህወሃት ማዕቀፍ ውስጥ ያሉትን በውል መናገር ባይቻል የሚወዱት እንዳሉ ይታወቃል። እየተሉት ስራውን የሚወዱትን ጨምሮ።

መነሻዬ ስለ አቀንቃኙ ውዳሴ ለመጻፍ ሳይሆን እሱን ተከትሎ በሚወጡ ዘገባዎች ላይ የሚሰጡ ትንታኔዎችና ትርጉም የለሽ ዘገባዎች እንዳሳሰቡኝ ለመግለጽ በማሰብ ነው። በእጅጉ ካስደነገጡኝ አስተያየቶችና ትንታኔዎች መካከል አለምነህ ዋሴ ” በቲዲ አፍሮና በመንግስት መካከል ቀዘቃዛ ጦርነት እየተካሄደ ነው” ያለውና ፤ በዩቱብ ገጾች ተዘጋጅተው በማህበራዊ ገጾች ላይ ከተሰራጩት ውስጥ ” ብቸኛው ቲዲ አፍሮ ኢህአዴግን አምበረከከ” የሚሉትን በዋናነት ለማሳያነት ጠቅሻለሁ።

ቴዎድሮስ ፣ ካጠፋሁ ራሱ ያርመኛል አንድ የራሱ አመለካከት እና እምነት ያለው ሰው ነው። እሱ ” ፍቅር ያሸንፋል” በሚል ጥላቻን በፍቅር ለመስበር የተነሳ የመንፈስ ልዕልና ያለው ባለሙያ ነው። እሱ አገሩን ባመነበት መንገድ እያገለገለ እንደሆነ የሚያምን ሰው ነው። ቴዲ የመሰለውን ነገር ውብ አድርጎ መግለጽ የሚችል ምጡቅ ነው። በቆመለት ” ፍቅር ያሸንፋል” መርህ መሰረት ቴዲ ቀዝቃዛም ሆነ እንደ ወላፈን የሚያንገበግብ ጦርነት ከማንም ጋር አይገባም። ፍላጎቱም የለውም። አስቀድሜ እንዳልኩት ግን ያሰበውንና ያመነበትን ለመግለጽ መድረክ የማያጣ፣ ጥበብ የማያነሰው፣ ውብ አገላለጽ የማይቸግረው ሰው ነው። አሁን በቅርቡ ያውጣው አጭር ግን ውብ መልእክት የያዘ መግለጫው ከበቂ በላይ ማሳያ ነው።

እንደ ጋዜጠኛም ሆነ፣ እንደ አንድ አስተያየት ሰጪ፣ በጣም ጥንቃቄ በሚጠይቁ ጉዳዮች ላይ መዘላበድና ንግግር አማረልኝ ብሎ እዛም እዚህም መርገጥ አግባብ ሆኖ አልተሰማኝም። ቴዲን አስመልክቶ አንድ ነገር ሲነሳ፣ ጉዳዩን ለጥጦና የራስን ስሜት ሰግስጎ ማቅረብ ለምንወደው ቴዲ የሚጠቅመው አይሆንም። እሱ ራሱ ከነገረን እምነቱና ደጋግሞ ካዜመልን ዜማዎች ጋርም የሚስማሙ አይመስለኝም። እንደውም ቴዲ ያሰበውን እንዳያደርግ የሚያገደው ይመስለኛል። በዚህም አድናቂዎቹ ብቻ ሳንሆን አገርም በዝምታው እንዳትከስር እሰጋለሁ። ለሚገባቸው ሁሉ ስጋቴ ስጋታቸው እንደሚሆን አምናለሁ።

ይህንን ስል አስተያየትና “ትንተና” አያስፈለግም ወይም አይቻልም ለማለት ሳይሆን፣ ትንታኔዎችም ሆኑ አስተያየቶች አርቲስቱ በርቀት የሚያየውን ጉዳይ መሰረት አድርጎ በሚናገራቸው መርሆቹ ላይ እንዲሆኑ ቢደረግ ለማለት እወዳለሁ። ራሱ ቴዲ ጠላት ወይም በአለምነህ “ቋንቋ በቀዝቃዛ ጦርነት ውስጥ ነህ?” ተብሎ ቢጠየቅ ” የምን ጠላት፣ ጠላት የለኝም” ብሎ መልሱን እንደሚጀመር አልጠራጠርም።

በአንድ ወቅት አንድ እንስት ጋዜጠኛ ” አንተ የአሁኑ ዘመን ሰው ነህ፤ ግን የቀድሞዎቹን አጼዎች ታወድሳለህ፤ ታውቃቸዋለ?” ስትል ጠየቀችው። ሰኮንድ ያልፈጀበት ቴዲ ” ኢየሱስን ለመውደድ በኢየሱስ ዘመን መወለድ አያስፈልግም” ብሎ ለተወላገደው ጥያቄ ማቃኛ የሚሆን መልስ መመለሱን አስታውሳለሁ።

ቴዲን የወደድንና የተቆረቆርንለት መስሎን፣ ለመከረኛ የኢንተርኔት ገበያና የገበያው እሽቅድድም በወጉ ያለተዘጋጁ፣ ያልታሰበባቸው፣ ብውል ያለተጠኑ መረጃዎችን ማሰራጨት ከትርፉ ኪሳራው ይበዛልና ጥንቃቄ ቢደረግ? በዚህ ብቻ ሳይሆን በተለያዩ ጉዳዮች ላይ ” ሰበር” የሚል ታቤላ እየተለጠፈባቸው የሚወጡ ” ሁሴን ቦልት ዜናዎች” ችግር ሲፈጥሩ እንጂ ውጤት ሲያስመዘገቡ ባለመታየታቸው የሶሻል ሚዲያ ተከታታዮች በደመ ነፍስ ሼር / መጋራታቸውን / በልኩ ቢያደርጉት።

ሲጠቃለል ቴዲ የሕዝብም፣ የራሱም፣ የሚዲያውም፣ ጥበቃ ያሸዋል። ዛሬ አዲስ ዓመትን አስመልክቶ የፍቅርና የአንድነት በሚል ለተዘጋጀው መርሃ ግብር ዋናው መድሃኒት ቴዲ ሆኖ ሳለ መንግስትም ስር ስር እየተከተለ የሚወስደውን የሚያስንቅ ተግባር ቢያቆም የተሻለ ይሆናል። ዛሬ ስለ ፍቅርና ስለአንድነት ለመስበክ ሚሊዮን ብር ከማፍሰስ ቴዲን የፕሮጀክቱ መሪ በማድረግ ቢሰራ ስንቱ ቀዳዳ በተዘጋ ነበር። ይህንን ማድረግ ባይቻል እንኳ እንደ አንድ ዜጋ ከወዳጆቹና ከአድናቂዎች ጋር ራት እንዳይበላ መክልከል አገር ከሚመራ አካል አይጠበቅም። ይልቁኑም ቂመኛነትን መስበክና ለትውልድ ማስተማር ነው።

እኔ ፈራሁ – ቴዲ አፍሮን ሚዲያዎች እና ማህበራዊ ገጾች እየጠቀሙት ነው? በነጻነት ለሰጠሁት አስተያየት ቴዲን ጨምሮ ቅሬት ካለ ለመቀበልና ለመታረም ዝግጁ ነኝ

አስማርች ብልሁ

ዛጎል ዜና የተወስድ