• ከ700 በላይ ደግሞ ትጥቅ መፍታታቸው ተገልጿል

በአማራ ክልል የሰሜን ጎንደር ዞን በ2009 ዓ.ም. ጫካ ገብተው ከነበሩ የታጠቁ ኃይሎች ጋር በተደረገ የተኩስ ልውውጥ 597 ሰዎች መገደላቸው ተገለጸ፡፡

የዞኑ አስተዳደርና ፀጥታ መምርያ ኃላፊ አቶ ዳኘው በለጠ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ ኤርትራ በመሄድ ከግንቦት ሰባትና አርበኞች ግንባር ጋር ተቀላቅለው በመሠልጠን በዞኑ ሕዝብ ላይ ከፍተኛ እንግልት ሲያደርሱና ግፍ ሲፈጽሙ የነበሩ በአጠቃላይ 708 ታጣቂዎች ናቸው፡፡ ከእነዚህ መካከልም 111 በሕይወት መያዛቸውን ተናግረዋል፡፡

በአሁኑ ወቅት የዞኑ ፀጥታ በአንፃራዊነት ጥሩ በሚባል ደረጃ ላይ እንደሚገኝ የገለጹት የመምርያው ኃላፊ፣ የሻዕቢያ መንግሥት እነዚህን ኃይሎች በገንዘብና በሎጂስቲክስ እገዛ ያደርግላቸው እንደነበር ተናግረዋል፡፡ ‹‹እነዚህ የታጠቁ ኃይሎች በሕዝቡ ውስጥ ሰፊ የሆነ ግፍ ሲፈጽሙ የነበሩና ሕፃናትንና ከብቶችን በመዝረፍ ሰቆቃ ሲያደርሱ የነበሩ ናቸው፤›› ብለዋል፡፡

አሁንም ቢሆን ከኤርትራ ሠልጥነው የመጡና በየቦታው እየተንቀሳቀሱ በሕዝቡና በመንግሥት ንብረት ላይ ጉዳት ለማድረስ ያለሙ ሰባት ግለሰቦች እንዳሉ ጠቁመዋል፡፡ በቀላል ወንጀል የታሰሩና ሰው ገድለው የሸሹ 23 ያህል ሽፍቶች በዞኑ ውስጥ ባሉ ጫካዎችና በሱዳን ድንበር አካባቢ እንዳሉም አስረድተዋል፡፡ የዞኑ የፀጥታ ኃይልና አስተዳደር በ2010 ዓ.ም. መስከረም ወር እነዚህን ኃይሎች ለማጥፋት አቅዶ እየሠራ እንደሆነም አቶ ዳኘው ተናግረዋል፡፡ እስካሁን በተደረገው ዘመቻም ከ500 በላይ የጦር መሣሪያዎች መማረክ ተችሏል ብለዋል፡፡

በሰሜን ዞን የፌዴሬሽን ምክር ቤት የቅማንት ሕዝብ አንስቶት የነበረውን የማንነት ጥያቄ ለመመለስ ሲባል በ12 ቀበሌዎች ሕዝበ ውሳኔ እንዲካሄድ መወሰኑ ይታወሳል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ በጭልጋ ወረዳ ያሉ አራት ቀበሌዎች በሕዝበ ውሳኔው ላይ ቅሬታ ማንሳታቸውን አቶ ዳኘው ገልጸዋል፡፡ እንደ አቶ ዳኘው ገለጻ፣ ጭልጋ ወረዳ ሕዝበ ውሳኔው ከሚካሄድባቸው 12 ቀበሌዎች መካከል ስድስቱ የሚገኙበት ሲሆን፣ ከእነዚህ መካከል አራቱ ማለትም ገለድባ፣ አንከራደዛ፣ ሹምየና አውርደርዳ ቀበሌዎች ውስጥ ከነዋሪዎች ቅሬታ ቀርቧል፡፡

በእነዚህ ቀበሌዎች የሚኖረው ሕዝብ ዋነኛ ጥያቄም፣ ‹‹ቅማንቶች ከ20 በመቶ በታች ሆነውና በቁጥር ደረጃ እኛ አማራዎች በልጠን ሳለ ሕዝበ ውሳኔው ለምን አስፈለገ የሚል ነው፤›› ብለዋል፡፡

መንግሥት ለቅሬታው በሰጠው ምላሽ እንደተባለው የአማራዎች ቁጥር የሚበልጥ ከሆነ በድምፅ መስጠት ሒደት የሚረጋገጥ እንደሚሆን፣ መጭበርበር እንዳይኖር ተብሎም ታዛቢዎች የሚመጡት ከሌላ ክልል እንደሆነም እንደተገለጸ ጠቅሰዋል፡፡ እንደ አቶ ዳኘው ማብራርያ፣ ሕዝበ ውሳኔ ከሚካሄድባቸው 12 ቀበሌዎች መካከል ሁለቱ ጎንደር ከተማ ውስጥ ሲገኙ፣ አራቱ ደግሞ መተማ ውስጥ የሚገኙ ቀበሌዎች ናቸው፡፡

የቅማንትና የአማራ ሕዝብ የማንነት ጥያቄ ከተነሳባቸው መካከል በ12 ቀበሌዎች ላይ ሕዝበ ውሳኔውን መስከረም 7 ቀን 2009 ዓ.ም. ለማድረግ ብሔራዊ ምርጫ ቦርድ መወሰኑ ይታወሳል፡፡

ምንጭ   –    ኢትዮጵያን ሪፖርተር