September 9, 2017 19:39

እዚህ ፎቶ ላይ የምታይዋቸው የሕወሃቱ መሪና የትግራይ ክልል ፕሬዘዳንት አቶ አባይ ወልዱ እና የብአዴኑ ምክትልና የአማራ ክልል ፕሬዘዳንት አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ናቸው። “በሁለቱ ክልሎች መካከል የነበረውን ችግር በዉይይት ፈተናል። ከዚህ በኋላ የድንበር ጥያቄ የለም” በሚል የተፈራረሙትን ወረቀት ወደ ላይ በማድረግ የተነሱት ፎቶ ነው።

አቶ ገዱ አንዳርጋቸው ይሄን ስምምነት ያደረጉት በኢሕአዴግ ፖሊት ቢሮ አስገዳጅነት እንደሆነ ይነገራል። በአጭሩ በሕወሃቶች እንጆቻቸውን ተጠምዝዘው ማለት ነው። በሌላ አባባል ይህ ስምምነት የሕዝብን ጥያቄ የመለሰ ወይንም በጥቂቱም እንኳን ለመመለስ የሞከረ agreement ሳይሆን surender ነው። የሕዝብ ጥቅም የሸጠ።

ዘላቂ መፍትሄ የሚመጣው ሁሉም አሸናፊ የሆኑበት መፍትሄ ሲኖር ነው። አንዱ ብቻ ተዋርዶ፣ አንዱ ብቻ ተሸንፎ፣ አንዱ ባዶዉን ቀርቶ ፣ ሌላውን አሸናፊ ያደረገ፣ ሌላውን ብቻዉን የጠቀመ ስምምነት የዉሸት ስምምነት ነው። ይህ እነዚህ ሁለት ባለስልጣናት የያዙት ሰነድ ሰላም የሚያመጣ የሰላም ሰነድ ሳይሆን፣ ለልጅ ልጆች የሚሆን ቁርሾ የሚፈጥር የጦርነት ሰነድ ነው። ሕወሃቶች የዘመኑ ነፍጠኞች ስለሆኑ ብቻ የጎንደርን ሕዝብ በአደባባይ ያዋረዱበት ሰነድ ነው።

ይሄ ስምምነት በአስቸኳይ ተከልሶ ጸገዴ ጠገዴ የሚሉትን አቁመው ወልቃይት፣ ሴቱቱ ሁመራ፣ ጠገዴና ጠለምት ቢቻል ወደ ታሪካዊው ቦታቸው ወደ በጌምድር ካልሆነ ደግሞ ከትግራይ ክልል ዉጭ አማርኛና ትግሪኛ የሥራ ቋንቋ ሆኖ፣ ትግሬዉም አማራውም ሁሉ እኩል የሚታዩበት አዲስ አስተዳደር/ክልል ውስጥ ሊካተቱ ይገባል። የጦርነቱ ሰነድ በሰላም ሰነድ ይተካ።

የወልቃይትን ጉዳይ ሲስተማቲክ በሆነ መንገድ ለማዳፈን፣ ቅማንት እያሉ ሰው ስለ ቅማንት እንጂ ስለ ወልቃት እንዳያስብ ለማድረግ ሕወሃቶች ቢሞክሩም ሕዝቡ በጣም የነቃና መረጃ በሚገባ ያለው እንደመሆኑ አይሳካላቸውም። በፊትም ህዝቡ ተቃዉሞዉን ረገብ ያደረገው የብአዴን አመራሮች ሕዝቡን በማነጋገርና በማወያየት የሕዝቡን ጥያቄ እንዲከበር እናደርጋለን የሚል ቃል ገብተው ስለነበረ ነው። አሁን ግን ብአዴኖች በሕወሃት በአደባባይ ሲሰደቡ፣ ሲዋረዱ እየታየ በመሆኑ የብአዴን አመራሮች ከፍተኛ አጣብቂኝ ውስጥ ነው የገቡበት ሁኔታ ነው ያለው። ብአዴኖች በአስቸኳይ በአደባባይ ከሕዝብ ጎን መቆም አለባቸው። ምንም ቢሆን ከሕዝብ ጎን መቆሙ ይሻላቸዋል፤ ከበሰበሰ፣ ዘረኛ ከሆነ የጥቂት ሕወሃቶች አገዛዝ ጋር ሆኖ አብሮ ከመበስበሰ።