(Yenus Muhammed)

ከሴት ተፈናቃዮች ውስጥ የአስገድዶ መድፈር ጥቃት የደረሰባት እንዳለችም ተገልጿል።

የማንቡክ ከተማ ነዋሪዎችና አመራሮች ችግሩን ለመግታት እየተንቀሳቀሱ ይገኛሉ።

አዲስ ዓመቱን በደስታ ለማክበር ጉምብስ ቀና በምንልበት በዚህ ወቅት አሳዛኝ ወሬ ከወደ ቤንሻንጉል ጉሙዝ ክልል መተከል ዞን ማንቡክ ከተማ ተሰምቷል።

***በጉብላክ፣ ድባፂና ባውላ በተሰኙ ቀበሌዎች ዙሪያ ይኖሩ የነበሩ 30 ያክል አማረኛ ተናጋሪ አባዎራውች ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለው በአሁኑ ስዓት በዳንጉር ወረዳ ማንቡክ ከተማ ቀበሌ 2 ላይ አርፈው ይገኛሉ። በአንዲት ሴት ላይም የአስገድዶ መድፈር ጥቃት መድረሱ ታውቋል። የአካባቢው ሰዎች ለተፈናቃዮቺ የተለያዩ ድጋፎችን በማድረግ ላይ ሲሆኑ…የቀበሌና የከተማው አመራሮች የተቻላቸውን ሁሉ በማድረግ ለመታደግ ጥረት እያደረጉ እንደሆነ የዐይን እማኞች ገልፀውልኛል።

በደረሰኝ መረጃ መሠረት የተፈናቃዮቹ ቁጥር ከተጠቀሰው በላይ ሊጨምር እንደሚችል የተገለፀ ሲሆን ተጨማሪ 30 አባወራዎችን ከጥፋት ለመታደግና ወደ ማንቡክ ከተማ ለማምጣት የጭነት ተሽከርካሪዎች ወደ ሥፍራው ተልከዋል።

ከዚህ በፊትም በዚሁ ክልል ተመሳሳይ ችግር ተከስቶ የነበረ ቢሆንም በመንግስት በኩል ችግሩ ሙሉ በሙሉ እንደተቀረፈ ተገልፆ ነበር። ይሁንና በዛሬው እለት በአጠቃላይ ወደ 60 የሚጠጉ አባወራዎች ከቤትንብረታቸው በግፍ መፈናቀላቸው የነበረው ችግር እንዳልተቀረፈ አመላካች ከመሆኑም በላይ የሀገሪቱን አለመረጋጋት ሊያባብስ ይችላል።

የአካባቢው አመራሮች፣ የፌደራል ባለስልጣናትና ሌሎች የሚመለከታችሁ ሁሉ አስፈላጊውን ዘመቻ በማድረግ የዜጎችን በሀገራቸው የመሥራትና የመኖር መብት ልታረጋግጡ ይገባል።

አሁን በማንቡክ ከተማ እየተደረገላቸው ያለው አቀባበል ይበል የሚያሰኝ ሲሆን ችግሩን ከስር መሠረቱ ለመቅረፍ ትልቅ የሆነ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ መሠራት እንዳለበት እና ተፈናቃይችንም በቶሎ ወደ ቦታቸው መልሶ በማሥፈር ማቋቋሞ እንደሚገባ ግን ሊሰመርበት ይገባል።