ነገ መስከረም 7,2010ዓ.ም. ወያኔ የ8 ቀበሌን የጎንደር ሕዝብ ቅማንት/አማራ ብሎ ድምፅ በማሰጠት ሕዝቡ ከሚሰጠው ድምፅ ተቃራኒ የሆነ ውጤት በማወጅ የሕዝቡን አንድነትና ጥንካሬን ለመፈረካከስ እንዲሁም ወደፊት ላሰበው ግፈኛ ጥቅሙ አመች መደላድል ለመጣል መዘጋጀቱ ይታወቃል፡፡ አንዳንድ ነገሩ ያልገባቸው ወገኖች ሕዝቡ በነቂስ ወጥቶ ድምፅ እንዲሰጥ እየቀሰቀሱ ይገኛሉ፡፡ እነኝህ ወገኖች ምንም እንኳ ፖለቲካ (እምነተ አስተዳደር) ባይገባቸውም እንኳ አስመራጩ አካል ነጻ ቢሆንና ሕዝብ የሚሰጠው ድምፅ ያለ አንዳች ማጭበርበር በይፋ የሚገለጽ ቢሆን ኖሮ እንዲህ ብለው መቀስቀሳቸው ባላስከፋ ነበር፡፡ ነገር ግን ውጤቱ ምን ሊሆን እንደሚችል አስቀድሞ የታወቀን ምርጫ፣ ሕዝቡ ወያኔ ሊያደርግ ያሰበውን ማጭበርበር መከላከል እንደማይችል እየታወቀ “ምረጡ!” ብሎ መቀስቀስ ግን አንድም ድንቁርና ነው ካልሆነም ደግሞ ቅጥረኝነት መሆኑ የሚያጠራጥር አይመስለኝም፡፡ እነኝህ ወገኖች ሕዝባችንን “ድምፅ ስጡ!” ብለው ሲቀሰቅሱ ምን እያደረጉ እንደሆነ ሌላው ያልገባቸው ነገር ምንድን ነው መሰላቹህ የወያኔን አጥፊ ፀረ ኢትዮጵያ እና ፀረ ሕዝብ የጎሳ ፌዴራሊዝም (የራስ ገዝ) ሥርዓትን መደገፋቸው እንደሆነ ሊገባቸው አልቻለም፡፡ እኔግን እላለሁ ቅማንት አማራ ሳይባል ሁሉም የስምንቱ ቀበሌ የጎንደር ሕዝብ ሆይ! ነገ ድምፅ አለመስጠት ብቻ ሳይሆን እንደተቀሩት ምርጫው እንዳይኪያሔድ ያደረጉት አራት ቀበሌዎች አስመራጭ አካል መስሎ በአስመራጭ ስም የገባውን የወያኔ ጭፍራ በማባረር ምርጫ ተብየው እንዳይኪያሔድ አድርግ! ምርጫው ከተኪያሔደና ሁለት ሦስት ሰው ብቻ እንኳ ቢሆን ድምፅ መስጠት ከቻለ ግን ወያኔ ምርጫው እንደተኪያሔደ በማስመሰል ኮሮጆውን ጠቅጥቆ ሞልቶ ሊያውጅ የፈለገውን ውጤት ማወጁ አይቀርምና ይሄ እንዳይሆን ተጠንቀቅ!!!

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!!!

ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!!

ሠዓሊ አምሳሉ ገ/ኪዳን አርጋው

amsalugkidan@gmail.com