20 Sep, 2017

ዘመኑ ተናኘ

የአማራና የቅማንት ማኅበረሰብ ተቀላቅሎ የሚኖርባቸውን ቀበሌዎች ለመለየት በጭልጋ ወረዳ የምትገኘውና ኳቤር ሎምየ ተብላ በምትጠራው ቀበሌ እሑድ መስከረም 7 ቀን 2010 .. በተደረገው ሕዝበ ውሳኔ፣ በሁለቱ ወገኖች መካከል መጠነኛ ውዝግብ ተፈጥሮ ነበር፡፡ ከጎንደር  ከተማ 140 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ በምትገኘውና ኳቤር ሎምየ ተብላ በምትጠራው ቀበሌ በተካሄደው ምርጫ ሪፖርት እንዳረጋገጠው፣ በቅማንትና በአማራ ማኅበረሰቦች መካከል ለሰዓታት የዘለቀ ውዝግብ ተከስቶ ነበር፡፡ መራጮች በተለይም ነባሩ አስተዳደር እየተባለ የሚጠራው የአማራ ተወላጆች ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ የኳቤር ሎምየ ቀበሌ ነዋሪ ያልሆኑ ግለሰቦች ለመምረጥ ተገኝተዋል፡፡ አቶ ፈንታሁን አድነው የተባሉ ግለሰብ፣ ‹‹በደም ቅማንት የሚባለውን አምጥተው አስገቡብን፡፡ ከእንግድባ ቀበሌ አምጥተው ድምፅ እንዲሰጡ አደረጉ፡፡ እኛ ከሌላ ቀበሌ አማራ ብለን ማምጣት ግን አንችልም፤›› በማለት በቅሬታ ተናግረዋል፡፡ ሌላ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የአማራ ተወላጅ ደግሞ፣ ‹‹በዚህ ቀበሌ ነዋሪ ያልሆኑና በአካባቢው አምስት ዓመት ያልሞላቸው ግለሰቦች መጥተው እንዲመርጡ እየተደረገ ነው፤›› ብለዋል፡፡ ሪፖርተር ከሌላ ቀበሌ መጥተዋል የተባሉ ግለሰቦችን ተዟዙሮ ያነጋገረ ሲሆን፣ እነዚህ ግለሰቦች በቁጥር ከሃምሳ በላይ እንደሚሆኑና በዚህ ቀበሌ ከአምስት ዓመት በላይ የኖሩ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡

እነዚህ ሁለቱ ወገኖች በዚህ የተነሳ ባስነሱት ውዝግብ የምርጫ ሒደቱ ሳይጀመር ለሰዓታት ቆይቶ ነበር፡፡ የቅማንት ብሔር ተወላጅ እንደሆኑ የሚናገሩት አቶ አስማረ ዘለቀ በበኩላቸው፣ ‹‹እነዚህ ሰዎች የእንግድባ ቀበሌ ነዋሪዎች አይደሉም፡፡ የኳቤር ሎምየ ነዋሪ ናቸው፤›› ሲሉ መስክረዋል፡፡ በዚህ የምርጫ ጣቢያ የድምፅ አሰጣጥ ሒደቱ የተጀመረውም ከሁለት ሰዓት በኋላ እንደሆነ በብሔራዊ ምርጫ ቦርድ የምርጫ ኦፕሬሽንና ሎጂስቲክስ ዳይሬክተር አቶ ጌታቸው ረቢራ ተናግረዋል፡፡ የቀበሌው ሊቀመንበር ለምርጫ አስፈጻሚዎች በመጨረሻ በጻፉት ደብዳቤ የቀበሌ ነዋሪነታቸውን በማረጋገጣቸው ግለሰቦቹ ድምፅ ሰጥተዋል፡፡ ይህንን ውሳኔ ግን የአማራ ተወላጆች ተቃውመዋል፡፡ ምርጫ ቦርድ ምርጫው የሚካሄደው ከጠዋቱ 12 ሰዓት እስከ ምሽት 12 ሰዓት እንደሆነ ቢገልጽም፣ በዚህ ምርጫ ጣቢያ ለሰዓታት በቆየው የሁለቱ ወገኖች ውዝግብ ምክንያት የምርጫ ሒደቱ የተጀመረው ዘግይቶ ነው፡፡

በዚህ ውዝግብ የተሞላው የምርጫ ጣቢያ ሪፖርተር በአካል ተገኝቶ ለማረጋገጥ እንደቻለው፣ ድምፅ ለመስጠት የነበረው ሠልፍ ረዥም ከመሆኑም በላይ በግፊያና መጨናነቅ የተሞላ ነበር፡፡

በጎንደር ከተማ ዙሪያ ሕዝበ ውሳኔ ከሚካሄድባቸው ሁለት ቀበሌዎች መካከል አንዱ የብላጅግ ቀበሌ ሲሆን፣ በዚህ ቀበሌ በተካሄደው ምርጫ የቅማንት ተወላጆች ወደ ምርጫ ጣቢያው ሄደው እንዳይመርጡ የሚያከላክሉ አካላት እንደነበሩ አስተያየት ሰጪዎች ተናግረዋል፡፡ በዚህ ቀበሌ በሚካሄደው ምርጫ የቅማንት ብሔረሰብ ተወካይ አቶ ካሴ መለስ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ መራጮች ወደዚህ ምርጫ ጣቢያ መጥተው ድምፅ እንዳይሰጡ የሚያደርጉ ግለሰቦች ነበሩ፡፡ የእነዚህን ግለሰቦች ማንነት እንዲገልጹ ተጠይቀው፣ ‹‹እኔ አሁን እዚህ ሆኜ ሁኔታውን መከታተል አለብኝ፡፡ መጥተው ድምፅ እንዳይሰጡ የሚያደርጉ አካላት እንዳሉ ግን ሪፖርት ደርሶኛል፤›› ብለዋል፡፡

በዚህ ምርጫ መካሄድ ቅር የተሰኙ አካላት እንዳሉ ሪፖርተር አረጋግጧል፡፡ ‹‹ለዘመናት ተዋልደንና በደም ተሳስረን እንደዚህ ዓይነት ጉድ በመጨረሻ መጣብን፤›› ሲሉ አንድ ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ ግለሰብ አስተያየታቸውን ሰጥተዋል፡፡ ሌላ ግለሰብ ደግሞ፣ ‹‹እኔ ዘጠኝ ልጆች አሉኝ፡፡ እኔ ቅማንት ነኝ፡፡ ሚስቴ አማራ ናት፡፡ ሁላችንም አማራን ነው የመረጥነው፤›› ብለዋል፡፡ ስሙ እንዳይጠቀስ የፈለገ አንድ የአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የአራተኛ ዓመት የኢንጂነሪንግ ተማሪ ደግሞ የቅማንት ብሔር ተወላጅ መሆኑን ገልጾ፣ ባለፈው ጊዜ በአማራና በቅማንት ሕዝብ መካከል ተከስቶ በነበረው ግጭት ምክንያት የቤተሰቦቹ ንብረት የሆኑ 72 ከብቶች መቃጠላቸውን ተናግሯል፡፡ በመሆኑም ይህ ምርጫ መካሄድና ቅማንት ለብቻው መተዳደር እንዳለበት ያምናል፡፡ ምርጫ በመካሄዱም ደስተኛ መሆኑን ገልጿል፡፡ ምርጫ የተካሄደባቸው ስምንት ቀበሌዎችና 24 የምርጫ ጣቢያዎች ሲሆኑ፣ በእነዚህ የምርጫ ጣቢያዎችና ቀበሌዎች ወጣ ያለ ችግር እንዳልነበር የማዕከላዊ ጎንደር ዞን ዋና አስተዳደር አቶ አየልኝ ሙሉ ዓለም ለሪፖርተር ተናግረዋል፡፡ ምርጫ የተካሄደባቸው ቀበሌዎችና ጣቢያዎች ሩቅ ቢሆኑም በጥሩ ሁኔታ መጠናቀቁን ገልጸዋል፡፡

ሪፖርተር ተዟዙሮ ባያቸው አራት የምርጫ ጣቢያዎች ማረጋገጥ እንደተቻለውም በምርጫው ዕለት ወጣ ያለ የፀጥታ ችግር አልነበረም፡፡ ነገር ግን በቅድመ ምርጫ ወቅት ጳጉሜን 1 ቀን 2009 .. በአንከርደዛ ቀበሌ ግጭቶች እንደበሩና በዚህም አንድ የዞን መኪና በድንጋይ መሰበሩን ለማወቅ ተችሏል፡፡ በዚሁ ዕለት ማታ ደግሞ የላዛ ሹምጌ ቀበሌ አስተዳደር ጽሕፈት ቤት በእሳት መቃጠሉ ታውቋል፡፡ በሚቀጥለው ቀን ደግሞ በጭልጋ ወረዳ በገለድባ ከተማ ሌሊቱን ሙሉ የጥይት ተኩስ እንደነበር ምንጮች ተናግረዋል፡፡ በቅድመ ምርጫው ወቅት በሁለቱ ወገኖች መካከል የሚፈጠሩ ግጭቶች እንደነበሩም ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ምርጫው ከተካሄደበት እሑድ መስከረም 7 ቀን 2010 .. እስከ ማክሰኞ ድረስ ችግር እንዳልነበር ዋና አስተዳዳሪው አቶ አየልኝ አስታውቀዋል፡፡ መስከረም 7 ቀን 2010 .. በቀድሞው ሰሜን ጎንደር ከስምንት ቀበሌዎች መካከል የሦስቱን ቀበሌ የምርጫ ሁኔታ በአካል በመገኘት ለመከታተል ተችሏል፡፡ በጎንደር ከተማ ዙሪያ ከሚገኙ ሁለት የምርጫ ጣቢያዎች መካከል አንዱ ብላጅግ ቀበሌ ሲሆን፣ በዚህ ቀበሌ በተካሄደው ምርጫ እስከ ሦስት ሰዓት ድረስ አብዛኛው ሰው ድምፅ ሰጥቶ ወደቤቱ የተመለሰ መሆኑን የምርጫ ጣቢያ ኃላፊው ገልጸዋል፡፡ በዚህ የምርጫ ጣቢያ ምንም ዓይነት የፀጥታ ችግር እንዳልነበረም አስረድተዋል፡፡ ገና በጠዋቱ ሠልፍ እንደሌለና ለመምረጥ የመጣ ግለሰብ ቶሎ መርጦ እንደሚሄድም ለማረጋገጥ ተችሏል፡፡

ሪፖርተር የቃኘው ሌላው የምርጫ ጣቢያ ነጋዴ ባህር የምርጫ ጣቢያ ‹‹ሀ እና ለ››ን ሲሆን፣ በእነዚህ የምርጫ ጣቢያዎች የነበረው የምርጫ ሒደት በሰላማዊ መንገድ መጠናቀቁን የምርጫ ጣቢያ ሀ ኃላፊ አቶ ምናሴ ረጋሳ ተናግረዋል፡፡ ከአዳማ ከተማ እንደመጡ የተናገሩት አቶ ምናሴ፣ እስከ ቀኑ ሰባት ሰዓት ድረስ ከ70 በመቶ በላይ የሚሆነው ተመዝጋቢ ድምፅ መስጠቱን አረጋግጠዋል፡፡ ሌላውና ሦስተኛው ቀበሌ ኳቤር ሎምየ ሲሆን በዚህ ቀበሌ ረዣዥም ሠልፎች ታይተዋል፡፡

ምርጫ ቦርድ ሕዝበ ውሳኔ የሚካሄደው በ12 ቀበሌዎችና በ34 የምርጫ ጣቢያዎች እንደሆነ ሲገልጽ ቢቆይም፣ የአራት ቀበሌዎች ምርጫ በመጨረሻው ሰዓት እንዲሰረዝ ተደርጓል፡፡ ለጊዜው ምርጫ እንደማይካሄድ የተወሰነባቸው ቀበሌዎች ላዛሹምየ፣ አንከርደዛ፣ ናራ አወደርዳና ገለድባ የሚባሉ ናቸው፡፡ ሁለቱ ቀበሌዎች ማለትም አንከርደዛና ላዛ ቀበሌዎች በፊትም ከሕዝቡ ጋር የተሟላ መግባባት ተደርሶ እንዳልነበር አቶ አየልኝ ጠቁመዋል፡፡ የእነዚህ አራት ቀበሌዎች የወደፊት ዕጣ ፈንታ ምንድነው የሚሆነው? በማለት ከሪፖርተር የቀረበላቸው ጥያቄ ሲሆን በምላሻቸውም፣ ‹‹በእነዚህ ቀበሌዎች ከዚህ ምርጫ በኋላ ከሕዝቡ ጋር ሰፊ ውይይት ተደርጎ እንደገና እንዲካሄድ ነው የሚሆነው፤›› በማለት ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ ለዚህ ምርጫ በሚሊዮን የሚቆጠር ገንዘብ ወጪ እንደተደረገበት እየተነገረ ሲሆን፣ ይህን ምርጫ ለማስፈጸም የተመደቡ ባለሙያዎች ከሦስት ክልሎችና ከአንድ የከተማዋ አስተዳደር ብቻ እንደሆነ አቶ ጌታቸው ረቢራ ተናግረዋል፡፡

አቶ ጌታቸው እንደሚሉት እነዚህ የምርጫ አስፈጻሚዎች በቁጥር በዛ ያሉ ሲሆኑ፣ ከዚህ በፊት ተካሂደው በነበሩ ምርጫዎች ተሳትፎ የነበራቸውና ልምድ ያላቸው እንደሆኑ ገልጸዋል፡፡ የመጡበት ክልልም ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር፣ ከደቡብ ክልል፣ ከቤንሻንጉል ጉምዝ ክልልና ከኦሮሚያ ክልል መሆናቸውን አስረድተዋል፡፡ በዚህ ምርጫ ድምፅ ለመስጠት 23,283 ዜጎች ተመዝግበው 20,824 የሚሆኑ ድምፅ መስጠታቸውንም አቶ ጌታቸው ገልጸዋል፡፡ የምርጫው ውጤትም ያንኑ ዕለት ቆጠራ በማድረግ በየጣቢያዎች እንደተለጠፈ ገልጸው፣ አጠቃላይ ውጤቱ የሚገለጸው ግን ከመስከረም 15 ቀን 2010 .. በኋላ እንደሆነ አስታውቀዋል፡፡ በቀሪዎቹ አራት ቀበሌዎች ሕዝበ ውሳኔ እንደሚካሄድ የተገለጸ ሲሆን መቼ እንደሆነ ግን ለማወቅ አልተቻለም፡፡

የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን ምርጫ በተካሄደባቸው ስምንት ቀበሌዎችና 24 የምርጫ ጣቢያዎች ባለሙያዎችን በመመደብ መራጮች መብቶቻቸውን እንዲጠቀሙ ማድረጉ ተገልጿል፡፡ የኢትዮጵያ ሰብዓዊ መብት ኮሚሽን የኢንፎርሜሽንና ኮሙዩኒኬሽን ዳይሬክተር አቶ ደምሰው በንቲ ለሪፖርተር እንደተናገሩት፣ መራጮች በምርጫ ወቅት መብቶቻቸውን በትክክል እንዲጠቀሙና ተፅዕኖ እንዳይደርስባቸው ተደርጓል፡፡ እንደ ኳቤር ሎምየ የምርጫ ጣቢያ ዓይነት ግጭቶች ከነበሩና በዚህ ግጭት የመብት ጥሰቶች ከነበሩ እንዴት ነው ያያችሁት የሚል ጥያቄ ቀርቦላቸው በምላሻቸው፣ ‹‹በሁሉም የምርጫ ቀበሌዎች የተሰማሩ ባለሙያዎችን መረጃ አንድ ላይ ሰብስበንና አደራጅተን የመብት ጥሰቶች ከነበሩ ወደፊት የሚገለጽ ይሆናል፤›› ብለዋል፡፡ 

ዘመኑ ተናኘ‘s blog

Author

anon