September 22, 2017 17:03

ብአዴን የአማራ ጠላት ድርጅት ነው። አፈጣጠሩ አማራን ማጥፊያ ነው። አናቱ ሲፈጠር በጸረ አማራ ግለሰቦች ነው። አማራ የሆኑም ያልሆኑም። ከዛ ወዲያ የገባው ለአማራ ለመታገል አይደለም። ለራሱ ሲል እና በተለያየ ምክንያት የገባ ነው። ለአማራ ለመታገል አስቦ ወደብአዴን የሚገባም የገባም የለም። አማራን ለማዳን ቦታው ብአዴን አልነበረም፤ ሆኖም አያውቅም። አማራን ለማዳን ጸረ ብአዴን ድርጅት እና አፍቃሬ አማራ ድርጅት እንዲሁም አመራሮቹ አማራ ብቻ የሆኑ የአማራ ድርጅት ነበር የሚያስፈልገው። መዐሕድ ይሄን አድርጓል- በጊዜው። ህወሀት ብአዴንን እያጎለበተ የመጣው መዐሕድን ለማጥፋት ነው። ስለሆነም ብአዴን ውልደቱ አማራን ለማጥፋት፣ ጉልምስናው መዐሕድን ለማጥፋት እና እርጅናው ህወሀትን ለማገልገል ነው። ብአዴን ህልውናው የተንጠለጠለው ለህወሀት በሚያሳየው የተንደፋዳፊነት ታዛዥነት ማለትም ሳይጠሩት አቤት፣ ሳይልኩት ወዴት በሚልበት የሎልነት መጠን ነው። ብአዴን ህልውናው የተንጠለጠለው በሚያሳፍናቸው፣ በሚያስራቸው እና በሚጨቁናቸው የአማራ ተወላጆች ብዛት ነው። በከፍተኛ አመራር ደረጃ ምናልባት ከተገደለው ሙሉዓለም በቀር ለአማራ ተቆርቋሪነት ያሳየ አይተንም ሰምተንም አናውቅም። ይሄ ሁሉ በመሆኑ ግን ብአዴንን ለይተን አንወቅሰውም፣ ለይተን አንጠላውም፤ ነገር ግን አማርኛ ተናጋሪ ህወሀት በመሆኑ ከፈጣሪው ትግርኛ ተናጋሪ ህወሀት ጋር አብረን የምንታገለው ነው። በትግሬው ህወሀት እና በአማራው ህወሀት መካከል ልዩነት የለም። ስለዚህ እኛም ሳናዳላ እንታገለዋለን፤ ሁለቱንም። ከጠላት ጠላት ቢያዳሉ አይጠረቃም ትግሉ ብለን።
ለመሆኑ የአማራነት እንቅስቃሴ ወይም የአማራ ብሄረተኝነት አላማው ብአዴን መሆን ነው ወይስ ብአዴንን አማራ ማድረግ ነው? የእኛ አላማ ብአዴንን አማራ ማድረግ ነው። ልክ ሌላ ቦታ የተሰገሰጉትን ወገኖቻችንን ወደአማራነት ማምጣት ግባችን ሆኖ እደምንሰራበት ሁሉ። ብአዴንም ወደአማራነት መምጣት ያለበት ነው። ስናመጣው ግን ውስጡ ያሉትን አባላት ለአማራ እንዲታገሉ በማድረግ እንጅ ድርጅቱን አይደለም። እኛ ብአዴን ለመሆን ነው እንዴ የምንታገለው? ብአዴን ለመሆን የምንታገል ከሆነ ምን አደባበቀን? ከማን ሸሽተን ነው በውጭ አገር አመራር ፈጥረን የምንታገለው? ከብአዴን መስሎኝ ድብብቆሽ የምንጫወተው! ብአዴንን ለመሆን ከሆነ ለምን በትግሬው ህወሀት ምርጫ ቦርድ ተመዝግበን እዛው አንንቀሳቀስም? የብአዴን መስመር ያዋጣል ብለን ነው ምንታገለው? ማለቴ ለትግሬው ህወሀት ዘላለማዊ ኮርቻ ለመሆን ነው የአማራነትን እንቅስቃሴ የምናስፋፋው? አይደለም። ብአዴንን ወደኛ ማምጣት፤ እምቢ ካለ ማጥፋት ነው አላማችን።
በውስጥ የሚታገሉ ለአማራነት የቆሙ አሉ። አወ አሉ። ታዲያ እነሱን ለማስደሰት ብአዴንን እናመስግን እንዴ? አይሆንም። ሲጀመር ብአዴን ውስጥ ሆኖ ለአማራነቱ በሌላ መንገድ መቆሙ እኮ በብአዴን አለማመኑን ነው የሚያሳየው። ስለዚህ ብአዴንን እየታገለው ነው ያለው። ይሄንን የሚታገለውን ድርጅት እንኳን መዝለፍ ባናቱ ብንተክልለትስ ደስ ይለዋል እንጅ እንዴት ሊከፋው ይችላል? ለአማራነት ስንቆም ስድብና ምርቃትን በመጠባበቂያ ይዘን ነው እንዴ? አይደለም። ለአማራነት እንኳን ብአዴን ተብለህ መሰደብ መገደልም አለኮ። ስድስት መቶ አማራ ገደልኩ ብሎ የትግሬው ህወሀት ሲፎክር ባለፈው አላያችሁም? እነዛን እያነቀ የሰጠው ማው? ብአዴን አይደለም? ነው ወይስ ይሄ ሁሉ አማራ ሲያልቅ ብአዴን የመንዳባ መድሐኒያለምን ማንጎ ፍሬ እየለቀመ ነበር? ለመሆኑ ሲሰድቡት ከፋኝ ብሎ ትግል የሚያቆም አለ? ብአዴን ውስጥ ያሉት እኒህ ለአማራነት የቆሙ ወገኖች እምቦቃቅላ ጨቅላ ናቸው እንዴ ተቆጡኝ አልተቆጡኝ እያሉ ሆድ የሚብሳቸው? ተው እንጅ አንተዛዘብ። ተው እንጅ ጎበዝ።

ለመሆኑ ብአዴን እንደ ድርጅት አማራ ተበድሏል ብሎ ያምናልን? አያምንም። በአንድ በኩል የአማራ ትግል የህልውና ነው እንላለን። በሌላ ወገን አማራን እስከመበደሉ እንኳ እውቅና የማይሰጥ ጥገኛ ድርጅትን እንንከባከብ እንላለን! የህልውና ትግል የሚያደርግ እና ለምንታገልለት ህዝብ መከራ ጆሮው ድፍን የሆነ ድርጅት በምን ሂሳብ ነው አንድ መስመር ላይ ሊቆሙ የሚችሉት? ሊጠፋፉ ካልሆነ በቀር። ብአዴን እኛ እንደምንለው አማራ የመጥፋት አደጋ ተደቅኖበታል ብሎ ቢያምን እስካሁን እርምጃ ይወስድ ነበር። እኛ በምንለው ደረጃ በችግሩ ቢያምን ኖሮ እጁ ላይ መሳሪያ አልነበረም!? እጁ ላይ የራሱ የትግሬው ህወሀት “ህገ-መንግስት” የተባለ መሳሪያ አልነበረውም? ነበረው። ቢያንስ በዛ የፖለቲካ ሚዛኑን በአስተማማኝ ሁኔታ ማስተካከል ይችል ነበር! ይሄንም የምንለው በራሱ በብአዴን ቋንቋ ለመግባባት ያክል ነው። ሆኖም ብአዴን ይሄንን አያደርግም። ምክንያቱም በአማራ መበደልና አደገኛ ጥፋት ላይ መሆን ስለማያምን። ጎንደር ተኮም ተኮርምሞ ባህር ዳር ሊደርስ ጥቂት እደቀረው እንኳ አይገነዘብም። በአላማጣ/ኮረም እና አጠቃላይ ራያ ከባድ የሆነ የማንነት ቅየራ ሂደት ሲሰራ እነደቆየ አያውቅም፤ ወደትግሬ የተከለለው ምድር በኋላ የትግርኛ ተናጋሪ እንደሆነ ሀሰተኛ ምስ እንዲከስት ተብሎ። “ከክልሉ” ውጭ ያለው ወገን ወደአለመኖር ሲያመራ እጁን አጣጥፎ የተቀመጠ እና ምንም ስሜትበ የለለው ነው። ስንቱ ይዘርዘር እንድንግባባ…..??????
አወ። የማንነት ትግል ሁሉንም አማራ አሳታፊ ነው። ከፖለቲካዊ ርእዮተ አለም ይልቅ ማንነት ቅድሚያ ስለሚመጣ ሁሉንም በነቂስ ያሰልፋል። ነገር ግን ይሄ ሲባል ያልነቃውንም፣ በጠላት ጎራ የተሰለፈውንም አያመለክትም። ማለት ትግልን በተመለከተ።
ስለሆነም የእኛ ህልም ያልተሸራረፈ ነጻነት እና ህልውና እንጅ ብአዴን መሆን ወይም የጠላት የእጅ ስሪት የሆነን ድርጅት እሽሩሩ ማለት አይደለም።
አማራነት ወደፊት!
ምስጋናው አንዱዓለም