September 26, 2017 14:23

ጌታቸው ሽፈራው

የማያወራ ፣ የማይኮራ ፣የማይፈራ ጀግና የወሎ ህዝብ የአማራዋ እንብርት መስቀልን እንድህ በውቦ ባንድራችን ደምቀዋል ዘርክ ይብዛ ወሎ በሁሉም ተመርቀሀል

ይህን ሰንደቅ አላማ የማውቀው ገና በህፃንነቴ ነው። በጊዜው የሀገር ምልክት መሆኑን አላውቅም ነበር። አዳኝ መሆኑን ነበር የማውቀው! ደግሞም አድኖናል!

ትህነግ(ህወሃት) ስትገባ ህዝቡ በደርግ እንዲማረር ተቋማትን እየተጠለለች ታስደበድብ ነበር። ቤተ ክርስትያንና ትምህርት ቤት ሳይቀር! አንድ ቀን ወርሃላ የምትባል ትንሽ ” ከተማ” የሚገኝ ትምህርት ቤት ውስጥ አለን ብለው አስወርተው ደርግም ይደበድበዋል። ከተደበደበ በሁዋላ አንዳንድ ሰዎች ትምህርት ቤቱን ለመዝረፍ ሲሞክሩ ተቆረወቋሪዎች ያድኑታል። አንዱ አባቴ ነበር።

የትምህርት ቤቱን ንብረቶች ወደእኛ ቤት አምጥቶ አንድ ቤት ውስጥ አስቀመጣቸው። ሰንደቅ አላማውን ግን “ሳንዱቅ” ውስጥ ከክት ልብሱ ጋር አስቀመጠው። እሁድ እሁድ ከ” ሳንዱቅ” እያወጣ ፣ እንደገና አጥፎ ያስቀምጠቃል። ለክፉ ቀን ያድነናል ብሎ መሰለኝ። በእርግጥም አድኖናል።

መስቀልን ለማክበር የሚያስፈልገው የ”ብረታ ብረት ………” ኮርፖሬሽን ምናምን ድጋፍ፣ የብረት ጥርቅም ሳይሆን እንደ ብረት የጠነከረ እምነት ነው! እንዲህ ድምቅ የሚያደርገው!

ደርግ ከደበደባቸው አካባቢዎች አንዱ በለሳ ነው። አይወራም እንጅ ልክ እንደ ሀውዜን እነ ሀሙሲት ተደብድበዋል። ከአንድ ቤት ሁለት ሶስት የቤተሰብ አባል በዋለበት ቀርቷል። የጦር አውሮፕላኖች የገጠር መንደሮችን ሳይቀር ስለሚደበድቡ ገበሬው ከብቶቹን ይዞ ከቤቱ ርቆ ገላጣ ቦታ ላይ ይውላል። ” ወያኔዎቹ” የማይጠለሉበት ቦታ ፍለጋ ነው። እኛ ግን የምንውለው ቤት ነበር። ሰንደቅ አላማውን ተማምነን!

አባቴ በጠዋት ተነስቶ ሰንደቁን ትልቁ ቤታችን አናት ላይ በረዥም እንጨት ይሰቅለዋል። አሁን የሚገርመኝ አባቴ ደርግ ሰንደቅ አላማው የተሰቀለበትን ቤት አይመታም ብሎ መተማመኑ ነው። እውነትም አውሮፕላኞቹ የእኛን ቤት ብቻ ሳይሆን ሰፈራችንም አልፈው ቦንባቸውን ሌላ ቦታ አራግፈው ይመለሳሉ።

አንዳንድ ቀን አባቴ ረስቶት አውሮፕላኖቹ መምጣታቸው ሲሰማ ሰንደቅ አላማውን ሮጦ ይሰቅላል። ሌሎቹም “ኧረ ስቀልልን” ይሉታል! ሰንደቁ ካለ ምንም እንደማይመጣብን፣ ያ የማናውቀው ነጎድጓዳማ ፍጥረት እንኳ እንደማያጠቃን እናውቅ ነበር። ህፃናቱ! ደርግ ከወደቀ በሁዋላ አባቴ የትምህርት ቤቱን ንብረት ሲያስረክብ ሰንደቅ አላማውምንም ከክት ልብሶቹ ነጥሎ ለመምህራኑ አስረከበ። ትምህርት ቤቱ ስራ ሲጀምር ያ በድብደባው ወቅት ያድነን የነበረው ሰንደቅ ነው ትምህርት ቤቱ ላይ የተውለበለበው።

ከዚህ ጊዜ ጀምሮ ይህን ሰንደቅ ሳየው የሆነ ነገር ይወረኛል። ደስታ ብቻ ብየ አልገልፀውም። ታዕምራዊ ነገር ያለው ያህል ይሰማኛል። በልጅነቴ አድኖኛልና። ከዛ ነጎድጓዳማ ፍጥረት። ለዛም ይመስለኛል ስለዚህ ሰንደቅ ከስራ ተባርሬበታለሁ! ጋዜጣ ተዘግቶበታል!

ይህን የደስ ደስ የሚፈጥርብኝ ሰንደቅ ይዛችሁ ስላከበራችሁ አስደስታችሁኛል!

መልካም በዓል ይሁንላችሁ!

የማያወራ ፣ የማይኮራ ፣የማይፈራ ጀግና የወሎ ህዝብ የአማራዋ እንብርት መስቀልን እንድህ በውቦ ባንድራችን ደምቀዋል ዘርክ ይብዛ ወሎ በሁሉም ተመርቀሀል

 

የማያወራ ፣ የማይኮራ ፣የማይፈራ ጀግና የወሎ ህዝብ የአማራዋ እንብርት መስቀልን እንድህ በውቦ ባንድራችን ደምቀዋል ዘርክ ይብዛ ወሎ በሁሉም ተመርቀሀል

የማ ይሽነፍ ትወልድ ቃሉን ጠባቂ :: እንቆረቆባሽ ወገኔ