October 3, 2017

ህወሀቶች ስለትግራይ ለመነጋገር ብቻ ሳይሆን ስለሀገሪቱ አጠቃላይ እጣፈንታ ሊወስኑ ዛሬ መቀሌ ስብሰባ መቀመጣቸው ታውቋል። በህወሀት ተጠፍጥፈው የተሰሩት፡ የምርኮና የአሽከር ስብስብ የሆኑት ብአዴንና ኦህዴድ በመንደር ታጥረው፡ በሙስና አጀንዳ ተወጥረው፡ በክልላዊ ጉዳዮች ያውም በጥቃቅን ነገሮች ተጠምደው በሚፋተጉበት ሰዓት ጌቶቻቸው መቀሌ ላይ ስለኢትዮጵያ ሊወስኑ መሆኑን በድፍረትም እየነገሩን ነው። ህወሀቶች ብአዴን መንደር እሳት ጭረዋል። ኦህዴድን በገመድ አስረዝመው በሰጡት ጊዜያዊ ደስታ አስፈንጥዘውታል። ደኢህዴን እስከመኖሩም ተዘንግቶ በህወሀቶች ”የሰጡትን የሚቀምስ” የሳሎን ውሻ ሆኖ እንዲቀመጥ ተፈርዶበታል። እነዚህ የህወሀት ስሪቶች ከተቀመጠላቸው አጀንዳ ውጪ ለመነጋገር ድፍረቱም፡ አቅሙም፡ ወኔውም የላቸውም። ህወሀቶች ከመቀሌ እስከ ሞያሌ፡ በአራቱም አቅጣጫ ስለሁሉም ኢትዮጵያዊ ሊነጋገሩ፡ ሊወያዩ፡ሊወስኑ ማንም የሚከለክላቸው አልነበረም። አሁንም የለም።

የህወሀት የፌስ ቡክ ሰራዊት ደግሞ ‘እኩል የመልማት መብታችን እንዲከበር’ የምትል የጅል ለቅሶ እያቀለጡት ነው። የዓለም ባንክ በሰሞኑ ሪፖርቱ የትግራይ ክልል ኢትዮጵያ ውስጥ መኖሩንም እስክንጠራጠር የሚያድርጉና ሌሎቹ ክልሎች ወደኋላ ቀርተው ትግራይን አንጋጠው የሚመለከቱበትን እውነተኛ መረጃዎችን ማጋለጡን እነዚህ የህወሀት የፌስቡክ ሰራዊቶች ሳያዩ ቀርተው አይደለም። ውሸትን ደጋግመን ከተናግረን እውነት ተደርጎ ይወሰዳል የምትለዋ የጎብልስ የሻገተች፡ መደርደሪያ ላይ የቀረች ባዶ ዲስኩር ደማቸው ውስጥ ተቀብራ ቀርታ እንጂ። ለማንኛውም የኢትዮጵያ ህዝብ አንድ ሆኖ ካልተነሳ ቢጭኑት አህያ፡ ቢለጉሙት ፈረስ መሆኑ የሚቀጥል ነው። እንግዲህ ከመቀሌ የሚወሰንልንን አንጋጠን እንጠብቃ!