በኦሮምያና በሶማሌ ክልሎች የተፈጠረው የድንበር ግጭት በሺዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎችን ህይወት አመሰቃቅሏል።

ቢያንስ 40 ሰዎች ህይወታቸውን ሲያጡ ከ50 ሺህ በላይ የሚሆኑት ደግሞ ከቤት ንብረታቸው ተፈናቅለዋል።

አሁን ደግሞ ይህ ግጭት የመማር ማስተማር ሂደቱም ላይ ተፅዕኖ እያሳረፈ ነው።

በተለይም በሶማሌ ክልል በሚገኘው ጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ውጥረቱ እየበረታ ነው።

ከመመህራንና ከተማሪዎች ባገኘነው መረጃ መሰረት ከመስከረም መባቻ ጀምሮ የኦሮሞ ተወላጅ የሆኑ የዩኒቨርሲቲው መመህራን ለደህነንታቸው በመስጋት ወደ አካባቢያቸው ተመልሰዋል።

ተማሪዎችም በቅርቡ በሚጀምረው አዲሱ የትምህርት ዘመን ወደ ግቢው መመለስ አስግቶናልእያሉ ነው።

yunivarsiitii JigjigaaFACEBOOK/JIGJIGA UNIVERSITY

ጥለን ወጥተናል መመህራን

ስሙ እንዲጠቀስ ያልፈለገ አንድ መምህር ለቢቢሲ እንደተናገረው የሶማሌ ክልል ልዩ ፖሊስ አባላት በጅግጅጋ ዩኒቨርሲቲ ኦሮሞ መምህራን ላይ ብዙ ጥቃት እያደረሱ ነው ይላል።

መስከረም 5/2010 .ም ግቢው ውስጥ ከሚገኘው መኖሪያችን እንድንወጣ ከተደረገ በኋላ፤ ልጆቻችንም ባሉበት ከባድ ዝናብ እየዘነበ ጭቃ ላይ አስቀመጡን። ተንቀሳቃሽ ስልካችንንም ነጠቀውን ወደ እስር ቤት ሊወስዱን በዝግጅት ላይ እያሉ የዩኒቨርሲቲው አስተዳደር አባላት መጥተው አትርፈውናል።

ይህ ድርጊት ሲፈጸም ደግሞ የፌደራል ፖሊስና የመከላከያ ሠራዊት አባላት ቆመው ይመለከቱ እንደነበረ ነው መምህሩ ለቢቢሲ የገለፀው።

ከዚህ በኋላ ሁሉም ኦሮሞ መምህራን ባገኙት ማንኛውም የመመለሻ መንገድ ወደየመጡበት ለመመለስ ተገደዋል።

ችግራቸውንም እንዲያስረዱ ተወካዮችን በመምረጥ ወደ ኦሮሚያ ትምህርት ቢሮና የፌደራል ትምህርት ሚኒስቴር ልከዋል።

ካሁን በኋላም ወደ ዩኒቨርሲቲው መመለስ እንደማይችሉና ኦሮሚያ ውስጥ ወደሚገኙ ዩነቨርሲቲዎች እንዲዘዋወሩ ጠይቀዋል።

ፌደራሊዝም ?

የላኳቸው ተወካዮች በትምህርት ሚኒስቴር በነበራቸው ቆይታ ይህች ሃገር በፌደራሊዝም ስርዓት የምትተዳደር በመሆኗ ማንኛውም ችግር ቢያጋጥም አንድን መምህር ከአንድ ቦታ ወስዶ ወደሌላኛው ማዘዋወር አይቻልም፤ እንደዚህ ከሆነማ ሥርዓቱ ፈረሰ ማለት ነውየሚል ምላሽ እንደተሰጣቸው ነግረውናል።

በሌላ በኩል ደግሞ እነኚህ መመህራን መጠለያቸውን በዩኒቨርሲቲው ባደረጉበት ወቅት ዩኒቨርሲቲው ከተማሪዎች ጋር ምግብ እንዲመገቡ፤ ወደየአካባቢያቸው ሲመለሱ ደግሞ ወደአየር ማረፊያ የሚያደርሳቸውን የትራንስፖርት አገልግሎት እንዲያገኙ ማድረጉን ተናግረዋል።

yunivarsiitii JigjigaaFACEBOOK/JIGJIGA UNIVERSITY

ተማሪዎች

የኦሮሞ ተማሪዎች የሚያነሱት ችግርም ከመምህራኑ የተለየ አይደለም ።

በዩኒቨርሲቲው የሦስተኛ ዓመት ተማሪ የሆነው ኦሊቃ (ለደህነነቱ ሲባል ስሙ ተቀይሯል) እንደሚለው ከግቢ ስንወጣ መታወቂያችንን በተደጋጋሚ ይጠይቁናል። የዩኒቨርሲቲውን ስናሳያቸው የቀበሌውን አምጡ ይሉናል፤ በምንሰጣቸው መታወቂያ ላይ የኦዳን ምልክት ሲያዩ ያንገላቱናል።

በዚህም ሳያበቃ ይላል ተማሪውየተለያዩ ሰበቦችን በመፍጠር መግቢያ መውጫ ያሳጡናል፤ ለምሳሌ ስልክህ ላይ የኦነግ ባንዲራ አለየሚለው ዋነኛው ነው።

በዚሁ ምክንያት ሁለት ወርና ከዚያ በላይ በእስር ያሳለፉ ተማሪዎች እንደነበሩ ነግሮናል።

እናም ይህ የትምህርት ዘመን ሳይጀመር ችግራቸው እንዲፈታ አቤቱታ እያሰሙ ነው።

ኦሊቃ እንደሚለውና በጅግጅጋ ዪኒቨርሲቲ የኦሮሞ ተማሪዎችበሚል የፌስቡክ ገጽ ላይ እንደሰፈረው የተማሪዎቹ ቁጥር እስከ 4000 የሚደርስ ነው።

አቤቱታቸውም ካሁን በኋላ ወደዚያ ተመልሰን መማር ሰለማንችል በኦሮሚያ ወደሚገኙ ዩኒቨርሲቲዎች አዘዋውሩን የሚል ነው።

የመንግሥት ምላሽ ?

እነዚህ መምህራንና ተማሪዎች የፌደራል መንግሥት ስለጉዳዩ በየጊዜው የሚያወጣው መግለጫ መሬት ላይ ያለውን ነባራዊ ሁኔታ የሚያሳይ አይደለም ይላሉ።

በፌደራል ትምህርት ሚኒስቴር የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር ወይዘሮ ሐረጓ ማሞአንሄድም ስላሉ ብቻ ሌላ ቦታ አይመደቡም

በፌደራል ትምህርት ሚኒስቴር የኮምዩኒኬሽን ጉዳዮች ዳይሬክተር ወይዘሮ ሐረጓ ማሞ ለቢቢሲ ዩኒቨርሲቲው የሚገኝበት የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ተረጋግቷል፤ መምህራኑ አንሄድም ስላሉ ብቻ ሌላ ቦታ አይመደቡምብለዋል።

ወይዘሮ ሐረጓ በክልል ደረጃ መተዳደር ማለት ደሴት ሰርቶ መኖር ማለት አይደለም፤ ስለዚህ ህዝቡ በፌዴራሊዝም መርህ ዙሪያ ጠለቅ ያለ ግንዛቤና እውቀት እንዲኖረው አበክረን እየሰራን ነውሲሉ ተናግረዋል።

ችግሩን በፈጠሩት ኣካላት ላይ እርምጃ ለመውሰድ እየተጣራ እንደሆነና በአሁኑ ሰዓት ከመንግሥት ቁጥጥር ውጪ የሆነ ችግር እንደሌለ ኃላፊዋ ይገልጻሉ።

የማረጋጋቱ ሥራ የዩኒቨርሲቲውን መምህራንና ለተማሪዎች ብቻ ሳይሆን ለሌሎች የመንግሥት ሰራተኞችንም እንደሚመለከት የገለፁት ወይዘሮ ሐረጓ የትምህርት ሚኒስቴር ባለሞያዎች ወደ አካባቢው በመሄድ ላይ ናቸው ብለዋል።