9 October 2017
የኢትዮጵያ ስኳር ኮርፖሬሽን ወደ ኬንያ ኤክስፓርት እንዲደረግ የሸጠው 4400 ቶን ስኳር ላለፉት ሁለት ወራት በሞያሌ ድንበር ፀሐይና ወበቅ ሲፈራረቅበት ከቆየ በኃላ ወደ ወንጂ መመለስ ጀመረ።
የኢትዮጵያዊ ስኳር ኮርፖሬሽን ስኳሩን የሸጠው በ2.2 ሚሊዮን ዶላር ቢሆንም፣ ክፍያው ግን እስካሁን አልተከፈለውም ። የኮርፖሬሽኑ የሕዝብ ግንኙነት ኃላፊ አቶ ጋሻው አይችሉህም” ለደረሰብን ኪሳራና ጉዳት ኩባንያው ላይ ክስ እንመሠርታለን፤” ሲሉ ለሪፖርተር ማምሻውን ገልጸዋል። ስኳሩን ኬንያ ለማድረስ የተዋዋለውና 110 ተሽከርካሪዎችን ያሰማራው ብራይት ድንበር ተሻጋሪ የትራንስፖርት ማሕበር የመጀመሪያዎቹ 40 ተሽከርካሪዎች የጫኑትን ስኳር ይዘው ነገ መስከረም 30 ቀን 2010 ዓ.ም. ወንጂ ስኳር ፋብሪካ እንደሚደርሱ ይጠበቃል።
ዱባይ የሚገኘው አግሪ ኮሞዲቲ በኢትዮጵያ ወኪሉ አማካኝነት ስኳሩን ወደኬንያ ቢልከውም ድንበር መሻገር ሳይችል ቀርቶ በፀሐይ እየቀለጠ እንደነበር መዘገባችን ይታወሳል፡፡
የስኳር እጥረት በአገሪቱ እያለ ስኳር ኤክስፖርት ማድረጉ በበርካቶች ዘንድ ግርምትንና ቁጣን ፈጥሯል፡፡
Source – Ethiopian Reporter