November 2, 2017 22:56
ፀጋዬ አራርሳ
አስቀድሜ የተለመደውን ኢትዮጵያዊ ሠላምታ ላቅርብ ፤ የጽሑፉ ትኩረት የሆንከው ዶ/ር ፀጋዬ ረጋሣ አራርሣ ከኦሮሞ አባት እና ከአማራ እናት መወለድክን፣ ከትግራይ ሴት ጋር መጋባትህን መረጃዎች ያመለክታሉ ። የውልደት ውጤት የሆንከው ዶ/ር ፀጋዬ ምርጫ የለህም እና ይህንን ማንነት ይዘህ ትቀጥላለህ ። ከዚህ ውጪ ከሕይወህ ጋር የተያያዙ ጉዳዮችን ለምሳሌ ጋብቻ ፣ ዕምነት ፣ ፖለቲካ … ወዘተ በተመለከተ በፍላጎትህ እና በምርጫህ ትወስናለህ ።
ስለ አንተ ምንነት እና ማንነት ለመናገር ወይም ለመጻፍ አመታት ይፈጃል ፣ ያን ያህል ፈጅቶም አንተን አገኘሁህ ፣ አወኩህ ማለት ያስቸግራል ያም ሆኖ ስለማንነት ፣ ስለአማርኛ ቋንቋ እና ስለአማራ እና ትግሬ መጤነት ከተናገርካቸው ላይ በማተኮር ትንሽ ልበል ። የምለው ሁሉ ከራሴ ፍላጎት ወይም ስሜት ወጥቼ ከራስህ አባባል እና የተመዘገቡ መረጃዎችን መሠረት በማድረግ ነው ።
ኢትዮጵያዊ ማንነት የለም
ዶ/ር ፀጋዬ መጀመሪያ ኦሮሞ ነኝ ብለሃል ፤ መታወቅ ያለበት እንደማንኛውም ሰብዓዊ ፍጡር ፀጋዬም መጀመሪያ ሰው ነው ፣ ይህንም ያገኘው ከኦሮሞ አባቱ እና ከአማራ እናቱ ነው ። ይህ ዕውነታ በዶ/ር ፀጋዬ ፍላጎት የሚቀየር አይሆንም ፣ እሱ ግን ተፈጥሮውን ቀይሬዋለሁ እያለ ነው ። ከሁለት ብሔረሰብ አባላት መወለዱ የሚቆጨው ዶ/ር ፀጋዬ በራሱ ላይ የደረሰውን እና የማይመቸውን በልጆቹ ላይ እንዲደርስ ወዶ እና ፈቅዶ የትግራይ ሴት አገባ ። በነገራችን ላይ የዶ/ር ፀጋዬ ልጆች ልጆቹ እንጂ ዶ/ር ፀጋዬ ባለመሆናቸው በራሳቸው መንገድ ማንነታቸውን እንደሚያገኙ በእርግጠኝነት መናገር ይቻላል ።
የተፈጥሮ ማንነትን መቀበል ያቃተው የፈለገውን ማንነት የመረጠ ያልፈለገውን የተወዎ ፣ በራሱ ላይ እንዲደርስ የማይፈልገውን በልጆቹ ላይ እንዲደርስ የፈቀደው ፣ ለራሱ ክብር መቆም ያልቻለው ፣ በአጠቃላይ በማንነት ውThንብር ውስጥ የገባው ዶ/ር ፀጋዬ ወደ አደባባይ ወጥቶ በማንኛውም ጉዳይ ላይ ላስተምር ፣ ልናገር ፣ ጥብቅና ልቁም ፣ ላደራጅ ፣ ልምራ ፣ ነፃ ላውጣ ቢል የሚነሳበትን የተአማኒነት ፣ የአቋም ፣ የዓላማ ፅናት
፣ ወገንተኝነት ፣ ሚዛናዊነት ፣ የሙያ ሥነ ምግባር ፣ የሞራል ብቃት ፣ ሕዝባዊነት ፣ የመርህ … ወዘተ ጥያቄዎችን የተገነዘበ አይመስልም ።
ዶ/ር ፀጋዬ ኢትዮጵያዊ ማንነት የሚባል የለም ፣ መጀመሪያ ኦሮሞ ነኝ ፣ ኦሮሞነት የማንነት መገለጫዬ ነው ፣ ኢትዮጵያ ሀገሬ ናት ብሏል ። ከዚህ አነጋገር መረዳት የሚቻለው ዶ/ር ፀጋዬ ኢትዮጵያዊ ማንነት የለም ብሎ ተነስቶ አለ ብሎ እንደደመደመ ነው ። ዶ/ር ፀጋዬ ኢትዮጵያ ሀገሬ ናት ካለ ኢትዮጵያ ሀገሬ ናት የሚል ሁሉ ዶ/ር ፀጋዬን ጨምሮ ኢትዮጵያ የምትባል የጋራ ሀገር አላቸው ማለት ነው ፣ ሀገር የጋራ
ማንነት መነሻ እንደመሆኑ ኢትዮጵያ የኢትዮጵያውያን የመጀመሪያው የጋራ ማንነት መገለጫቸው ናት ።
አገራዊ ማንነት የተወሰነ ወርድ እና ስፋት ያለው ጉዳይ ሳይሆን ከዜግነት ከእኩል መብት እና ግዴታ ፣ ከዲሞክራሲ ፣ ከፍትህ ፣ ከእኩልነት ፣ ከነፃነት ፣ ከውክልና … ወዘተ ጋር ተያይዞ በሚዳብር የጋራነት የአገራዊ ማንነት ይዘት እየተሟላ ይሄዳል ። ኢትዮጵያዊ ማንነት መኖሩ ግልጽ ነው ፣ጥያቄው ያለው ኢትዮጵያዊ ማንነት የሁሉንም ፍላጎት ያስተናግዳል አያስተናግድም የሚለው ነው ። ይህም በመነጋገር መስተካከል የሚችል ጉዳይ ነው ።
አገራዊ ማንነት ከመንግሥት አወቃቀር ፣ አደረጃጀት እና አሠራር ጋር ብቻ የተያያዘ አይደለም ፣ በሕዝብ መካከል ሰፊ ማህበራዊ እና ኢኮኖሚያዊ የአግድሞሽ ግንኙነት አለ ፣ ይህ ግንኙነት የቋንቋ እና የባህል መወራረስን ፣ የእርስ በርስ ጋብቻን ፣ እንደ እድር
፣ እቁብ … የመሳሰሉ ማህበራት ምሥረታን ያስከትላል ፣ ከዚህም ጋር ተያይዞ በረጅም ጊዜ የጋር ማንነት እና ሥነልቦና ይፈጠራል ፣ ይዳብራል ።
አማራ እና ትግሬ መጤዎች ናቸው
አማራ እና ትግሬ መጤዎች ናቸው ፣ አይመቹኝም ፣ የአቢሲኒያ ኢምፓየር መሠረት እንደመሆናቸው ለደረሰው ሁሉ ተጠያቂ ናቸው ይላል ፣ የዶ/ር ፀጋዬ የመጀመሪያው ሥህተት አገዛዝ እና ሥርዓትን ከሕዝብ መለየት አለመቻል ሲሆን ፣ ሁለተኛው ስህተት የገዢዎች ፍላጎት መግዛት እና ማስገበር እንደመሆኑ አልገዛም አልገብርም ባለው ላይ ዱላው በቅድሚያ የሚያርፈው በአካባቢው ሰው ላይ መሆኑን ካለመረዳት አማራን እና ትግሬን የሥራዓቱ ተጠቃሚ እና ተጠያቂ እንደሆኑ አድርጎ ያቀርባል ።
ሥልጣን በተለያዩ አደረጃጀት በየአካባቢው ይፈጠራል ። የሥልጣን መገለጫ የጎበዝ አለቃ
፣ ንጉሥ ፣ ሱልጣን ፣ አባ ገዳ ፣አሚር… ወዘተ ሊሆን ይችላል ። ሁሉም የበላይ ለመሆን ስለሚፈልጉ ግጭት ይፈጠራል ፣ አቅም ያለው ሥልጣን ይጠቀልላል ። ይህ የሥልጣን መነጣጠቅ ጉዞ ከአክሱም ንጉሥ ኢዛና ጀምሮ ወደ ዮዲት ጉዲት ፣ ዛጉዌ ሥርወ መንግሥት መልሶም ወደ ሰለሞናዊ ሥርወ መንግሥት ፣አህመድ ግራኝ እያለ ወያኔ እጅ ገባ ። በሌላ በኩል በገዳ ሥርዓት ላይ የተመሠረተው የኦሮሞ የሥልጣን ፍላጎት እንቅስቃሴ ከደቡብ ኢትዮጵያ ወደ ሰሜን እና ምዕራብ ኢትዮጵያ ከ16ኛው መ.ክ. ዘ. ጀምሮ ይደረግ ነበር ። ይህ ጉዞ የተለየ ቅርጽ እና ይዘት ቢኖረውም የመጨረሻ ግቡ መግዛት ማስገበር ነው ። በተጨማሪም ከምሥራቅ ኢትዮጵያ ወደ መሀል ሀገር እና ሰሜን ኢትዮጵያ የተደረገው የአህመድ ግራኝ የልግዛ ላስገብር ጦርነት እንደ ሌሎቹ የሥልጣን ሽሚያዎች ተመሳሳይ ባህሪ ያለው ነው ። በሁሉም የሥልጣን ሽሚያ ጉዞ ብዙ ሕይወት ጠፍቷል ፣ ንብረት ወድሟል ፣ ሕዝብ ተፈናቅሏል ፣ አዲስ የሕዝብ አሰፋፈር ተፈጥሯል ፣ ዛሬ በኢትዮጵያ የሚታየው የሕዝብ አሠፋፈር የሁሉም የሥልጣን ሽሚያ ጉዞ እና በየአቅጣጫው የተደረገ ፍልሰት ውጤት ነው ።
ዶ/ር ፀጋዬ አፉን ሞልቶ አማራ እና ትግሬ መጤዎች ናቸው ይላል ። ሰው በሀገሩ እንዴት መጤ ይሆናል ? ዛሬ የሚታየው የኢትዮጵያ የሕዝብ አሰፋፈር ከሞላ ጎደል የዘመናት የሕዝብ የሀገር ውስጥ ፍልሰት ውጤት መሆኑ እየታወቀ እንዴት አንዱ መጤ
ሌላው ነባር ይሆናል ? በአንድ ሀገር ውስጥ በተለያዩ ምክንያቶች ሕዝብ ከቦታ ቦታ ይንቀሳቀሳል ፣ ይፈናቀላል ፣ ይሠፍራል ፣ ይኖራል ፣ ችግሩ ከአለፈ በኋላ በመረጠው ሕይወቱን ያስቀጥላል ፣ ይህ አባባል ከሰሜን ወደ ደቡብ ፣ ከደቡብ ወደ ሰሜን እና ከምሥራቅ ወደመሐል ሀገር እና ሰሜን ኢትዮጵያ የተደረገውን እንቅስቃሴ በእኩልነት ይመለከታል ። በዚህ ሁኔታ አማራን እና ትግሬን ነጥሎ መጤ ማለት ሚዛን ያልጠበቀ
፣ተጨባጭ ሁኔታውን ያላገናዘበ ፣ ከሙያ ሥነምግባር የወጣ ፣ጭፍን ስሜታዊነት እና ወገንተኝነት ነው ። የኦሮሞ መስፋፋት ኦሮሞን ከደቡብ ምሥራቅ ኢትዮጵያ እስከ ሰሜን መዕራብ ኢትዮጵያ ጫፍ አድርሶታል፤ለምሳሌ በደቡብ ጎንደር የጋራ ጀልዱ ፣ በጎጃም የኢልማ እና ዴንሳ ፣በወሎ የራያ ፣ በሰሜን ሸዋ የከሚሴ ኦሮሞዎች በሀገራቸው ኢትዮጵያ እንደማንኛውም ነዋሪ በእኩልነት ስለሚኖሩ አንድም ቀን መጤ ተብለው አያውቁም ።
አማርኛ ቋንቋ በዕቅድ ፣ በሕግ ድጋፍ ነው የሥራ ቋንቋ የሆነው
ዶ/ር ፀጋዬ ፣ አማርኛ የመንግሥት የሥራ ቋንቋ የሆነው በአጋጣሚ ሳይሆን በዕቅድ ፣ በአዋጅ ፣ በሕግ እና በተቋም ተደግፎ እንደሆነ ይናገራል ። አሁንም እውነቱን ከመረዳት ፍላጎቱን እና ስሜቱን አስቀደመ ፣ አማርኛ የሥራ ቋንቋ መሆኑ ፣ የአፍ መፍቻ ቋንቋቸው አማርኛ ባልሆኑ ላይ መጫኑ እውነት ነው ። የሆነው ግን ዶ/ር ፀጋዬ ባለው መንገድ አይደለም ።
በ13ኛው መ.ክ. ዘ. በዛግዌ ሥረወ መንግሥት ጊዜ በኤርትራ በሚገኘው ሎጎሳርዳ ወረዳ የአካባቢ ሕግ በትግርኛ ተጽፎ ቢገኝም አማርኛ በ12ኛው መ.ክ. ዘ. መጨረሻ ጀምሮ የመንግሥት የሥራ ቋንቋ መሆኑ መረጃዎች ያመለክታሉ ።
የመጀመሪያው ገዢ በራሱ ምክንያት አማርኛን የመንግሥት የሥራ ቋንቋ ሊያደርገው ችሏል ። ከዚያ በኋላ ሌላ ቋንቋ ተናጋሪ ገዢዎች ተፈራርቀዋል ። እነዚህ ፈላጭ ቆራጭ ገዢዎች ላገዛዛቸው የማይመቻቸውን ሁሉ ያለ ርህራሄ ያስወግዳሉ ። ሁሉበእጃቸው በደጃቸው የሆነላቸው ዓፄዎች በአማርኛ ቋንቋ ላይ ተመሳሳይ እርምጃ ለመውሰድ አቅም አልነበራቸውም ማለት አይቻልም ፣ ማለት የሚቻለው የራሳቸውን ቋንቋ ጨምሮ አማርኛን ተክቶ የመንግሥት የሥራ ቋንቋ ለመሆን የሚችል አማራጭ በማጣታቸው ሳይወዱ በግድ አማርኛ እንዲቀጥል አድርገዋል ። አማራጭ ቋንቋ ቢኖራቸው ኖሮ ዛሬ ፕሬዚዳንት ዶናልድ ትራምፕ በቀድሞ ፕሬዚደንት ኦባማ ጊዜያት የተላለፉ እና የማይፈልጓቸውን ውሣኔዎች እየቀየሩ እንዳሉት ሁሉ አማርኛን አህመድ ግራኝ በአረብኛ / ሱማሊኛ ፣አፄ ዮሀንስ እና መለስ ዜናዊ በትግሪኛ ፣ ትልቁ ራስ አሊ ፣ ተፈሪ መኮንን ጋዲሳ እና መንግሥቱ ኃይለማሪያም ወልዴ አያኖ በአፋን ኦሮሞ ሥልጣን እንደያዙ እንደሚቀይሩ እርግጠኛ ሆኖ መናገር ይቻላል ። ምርጫ ባለመኖሩ ግን ሁሉም የአገዛዛቸው እና የሥርዓታቸው የደም ሥር የሆነው አማርኛ ቋንቋ እንዲቀጥል ፣ እንዲያድግ በመላ ሀገሪቱ ተደራሽ እንዲሆን ገዢዎች አስፈላጊውን ሁሉ አድርገዋል ።
ዶ/ር ፀጋዬ ፣ ሐሳብን በነፃነት የመግለጽ መብት ለሁሉም ይሰራል ፣ ጥያቄ የሚነሳው ይህን መብት ስንጠቀም ከስሜት ውጪ ሆነናል ፣ ምን ያህል ሚዛናዊነትን ጠብቀናል ፣ የሞያ ሥነምግባርን አስከብረናል ፣ መረጃን መሠረት አድርገናል ፣ ሰብዓዊ ሆነናል ፣
ከወገንተኝነት ርቀናል ፣ ከድብቅ ፍላጎት ወጥተናል ፣ የሕዝብን ፍላጎት አክብረናል …
ወዘተ የሚሉት ናቸው ፣ ሁላችን ለራሳችን መልስ እንስጥ ።
ዶ/ር ፀጋዬ ማንነትህን በውስጥህ ይዘህ ፍለጋ ወጣህ ፣ አላገኘኸውም ። ለራስህ ክብር ሳትቆም ለሌላው አትቆምም ፣ በራስህ ላይ እንዲደርስ የማትፈልገውን በሌላው ላይ አድርገሃል ፣ ተፈጥሮህን እቀይራለሁ ብለህ ግማሽ አካልህን ጥለህ በግማሽህ መኖርን መርጠሃል ። በአጠቃላይ ማንነትህን በማጣትህ በዘውገኝነት ተደብቀሃል ። የኦሮሞ ብሔርተኝነት አቀንቃኝ መሆን አለመሆን ምርጫው ያንተ ፣ ዳኝነት የኦሮሞ ብሔረሰብ እንጂ እኔን ጨምሮ የማንም አይደለም ። ጃዋር በአማራ ድምጽ ራዲዮ ቃለ መጠይቅ የኢትዮጵያ አንድነት ግዴታ ነው ፣ ኦሮሞ የሠራውን ቤት አያፈርስም ፣ ዶ/ር መስፍን አብዲ ኦሮሞ በደሙ እና በእንባው የገነባትን አገር ኢትዮጵያ ስትፈርስ ዝም በሎ አይመለከትም ፣ ብቻውንም ሆነ ከሌሎቹ ጋር ይታደጋታል ፣ ዶ/ር ዲማ ነገኦ አማራ እና ኦሮሞ አሸዋ እና ሲሚንቶ ናቸው ፣ የኦሮሞ ወጣቶች ጣና ኬኛ ፣ ዶ/ር አብራሃም ዓለሙ ኦሮሞን አታሳንሱ አታዋርዱ ፣ ባሪያ ሆኖ አያውቅም ፣ ኦሮሞ ያልተሳተፈበት መንግሥታዊ ሥርዓት የለም ፣ ዶ/ር ጳውሎስ ሚልኪያስ በኢትዮጵያ ላይ የኦሮሞ አሻራ ያላረፈበት የለም … ሌሎችንም ማንሳት ይቻላል ፣ የሚሉትን ዶ/ር ፀጋዬ የራስህን ማንነት እና አቋም መለስ ብለህ ለማየት መልካም አጋጣሚ ተፈጥሮልሃል ብዬ አምናለሁ ።
የነሱን አባባል በሚዛኑ አንድ ጎን የአንተን በሌላው ጎን አስቀመጠህ አመዛዝነው ። ዶ/ ር ፀጋዬ ፣ የኢትዮጵያን ሁኔታ ለመረዳት የአንተን የዶክትሬት መመረቂያ ጽሑፍ እንድናነብ ጋብዘሃል ፣ ግብዣህ ጥሩ ነው ግን አንተ የጽሑፉ ጥሩ መስታወት በመሆንህ ገለፃህ ፣ ትረካህ እና ትዋኔህ ጽሑፍህን ቁልጭ አድርጎ ያሳያል ብዬ አምናለሁ ፣ እኔ በሃይጅን ፈተና መቶ ከመቶ አግኝቶ እጁን ሳይታጠብ እንደበላው ተማሪ ነኝ ካላልክ በቀር!
ከሠላምታ ጋር