November 3, 2017 14:26

ርዕስ-ስዉሩና ያልተነገረዉ የአይሁዳዉያን እና የኢትዮጵያዉያን ታሪክ

ደራሲ-ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ ጅግሳ

አሳታሚ-Nebadan plc

የገጽ ብዛት-234(ከአባሪዎችና ምስሎች ጋር)

ዳሰሳ አቅራቢ-ሚኪያስ ጥ.

ሰዉዬዉ በትምህርቱና በስነ-ጽሁፉ አለም ከከረሙ፣ዘመን አልፏቸዋል፡፡ኢትዮጵያ እያሉ ካሳተሟት፣‹‹ወለላ›› ከተሰኘች የኣጫጭር ልቦለዶች መድበል አንስቶ እስከዛሬ እስከጻፏቸዉ ታሪክ-ቀመስና ልቦለዳዊ ስራዎቻቸዉ ድረስ በዓለምአቀፍ ደረጃ እዉቅናን አትርፈዋል፡፡በአሁኑ ሰዓት በuniversity of Lincoln በመምህርነት እየሰሩ ይገኛሉ-ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ፡፡

የፕ/ሩ ስም ከቅርብ ጊዜያት ወዲህ በጉልህ ይነሳል፤‹‹የኦሮሞና የአማራ ዕዉነተኛ የዘር ምንጭ›› መጽሃፋቸዉ፣የበርካታ ዉይይቶች ማዕከል ሆኖ ሰንብቷል፡፡ጉዳዩን ወረድ ብለን የምናነሳዉ ይሆናል፡፡በቅርቡ ያሳተሙት ‹‹ስዉሩና ያልተነገረዉ የአይሁዳዉያን እና የኢትዮጵያዉያን ታሪክ›› ከቀደመዉ መጽሃፋቸዉ በጭብጥ ይለያል፡፡በአብዛኛዉ የሚተርከዉ ኢትዮጵያዉያን ከአይሁዶች ጋር ስላላቸዉ ስር የሰደደ ትስስሮሽ ነዉ፡፡

ደራሲዉ የመጽሃፉ መታሰቢያነት የሰጡት ‹‹ብርቅዬና ጥንታዊ ታሪካችንን መዝግበዉ ላቆዩ ባለዉለታዎቻችን›› ነዉ፡፡ከስሞቹ መካከል የመሪራስ አማን በላይ ስም ተጠቅሷል፡፡ፕ/ሩ ለዚህ መጽሃፍ እንደግብዓትነት የተጠቀሙት የመሪራስ ኣማን በላይን ስራዎችን፣መጽሃፍ ቅዱስንና ሌሎች የታሪክ መጽሃፍትን ነዉ።ሁለቱ መጽሃፍት፣‹‹ዣንሸዋ››ና ‹‹ያሻር›› በጥንት ዘመን ከመጽሃፍ ቅዱስ በፊት የነበሩ ናቸዉ፡፡(ገጽ 29) እነዚህ መጽሃፍት ያለፈዉን ዘመን ታሪክና የኢትዮ-አይሁድ ትስስሮሽን ለማሳየት፣ፕ/ሩ በእጅጉ ተጠቅመዉባቸዋል፡፡መጽሃፍቱ ‹‹ሱባ›› በሚባል፣በቅድመ-መጽሃፍ ቅዱስ ጊዜ በነበረ ቋንቋ የተጻፉ ናቸዉ፡፡የሱባ ቋንቋ ነባር መሆኑን ለማሳየት በዚህ መጽሃፋቸዉ የምስል ማስረጃ አካትተዉ ቀርበዋል፡፡(ገጽ 32ና 33 ላይ) ፊደላቱ ለላቲን ፊደል መነሻ በመሆን አገልግለዋል፡፡(ገጽ 31)

ግራ ሲያጋባን ለኖረዉ፣ኢትዮጵያ የሚለዉ ስም ‹‹ከየት መጣ?›› ለሚለዉ ጥያቄ፣ፕ/ር ፍቅሬ ‹‹ኢትዮጵያ ማለት ቢጫ ወርቅ (ለእግዚአብሄር) ማለት ነዉ፡፡››(ገጽ 222)የሚል ምላሽ ሰጥተዋል።ለ’ኔ፣ትክክለኛዉ ቃለ-ብያኔ የፕ/ር ፍቅሬ ቃለ-ብያኔ ነዉ።

ስለዮዲት ጉዲት(አስቴር) ‹‹ሊታመን የማይችል›› አዲስ ታሪክ፣ፕ/ር ፍቅሬ ይዘዉ ከተፍ ብለዋል፡፡ዮዲት ጉዲትን ሲገልጿት፣‹‹እንደባለዉለታ›› አድርገዉ ነዉ፡፡ለዓመታት ‹‹የተጋትነዉ›› የዮዲት አዉዳሚነት ትርክትን የሚገለብጥ መረጃ ያገኘን ይመስለኛል፡፡ይህቺ ሴት ለግዕዝ ቋንቋ ‹‹ባለዉለታ ናት›› ይሏታል፡፡ እንዴት ‹‹ባለዉለታ›› እንደሆነች በዝርዝር እንመልከት፡፡

አንድ ጊዜ ዮዲት የእንቁዮጳግዮን ወታደር ለመሆን ትበቃለች፡፡በወታደርነት ለመስራት የተነሳችበት ሰበብ፣አይሁዳዉያን ወገኖቿ ‹‹ህዝበናኝ›› በተባለ የአክሱም ንጉስ የደረሰባቸዉ ግፍ ነበር፡፡(ገጽ 139ና 140) በሌላ በኩል፣‹‹መራሪ(መሪ)›› የሚባል የአዜብ(አዘቦ) ንጉስ፣እንቁዮጳግዮን የተባለች ልጅ ነበረችዉ፡፡ትንቢት ተናጋሪዎች ‹‹ንጉስ ያልሆነ ባል ታገባና የቆየዉን ያ’ንተን ስርዓት የሚለዉጥ ልጅ ትወልዳለች፡፡›› ብለዉ ለመራሪ ስለነገሩት፣ልጁ ከማንም ወንድ ጋር እንዳትገናኝ ይከለክላታል፡፡(ገጽ 140፣141) ንጉስዬዉ ወደ አክሱም በሄደ ሰሞን፣ሰለሞን የሚባል ከሌዊ ወገን የሆነ አናጢ ያገኝና ወደእልፍኙ ያመጣዋል፡፡እንቁዮጳግዮን ወዲዉኑ በፍቅር ትከንፋለች፡፡ንጉሱ ይህንን ሲያዉቁ፣ሰለሞንን የግንድ ቀፎ ዉስጥ ከምግብ ጋር ከትቶ በአትባራ(በኋላ በንጉሱ ትካዜ ምክንያት ተከዜ) በተባለዉ ወንዝ ዉስጥ ጨመረዉ፡፡(ገጽ141)ወደ አክሱም ልኮት ‹‹ይሆናል›› ብላ ወደ አክሱም ተራ ሴት መስላ ሄዳ ስትፈልግ፣አንድ እሱን የሚመስል ሰዉ አየች፡፡ሰለሞን መስሏት ተጠመጠመችበት፡፡

እሱም ‹‹ንጉሴ ነኝ፤ወንደሙ ነኝ፡፡ሰለሞን ሳይሰናበተን እንደወጣ ከቀረ ዓመታት አልፈዋል፣የት እንዳለ እንጃ!›› አላት፡፡ንጉሴን ይዛ ወደ ቤተ-መንግስት መጣች፡፡አንዴ አባቷ ፈርቷልና ‹‹ጀግንነቱን ለማረጋገጥ›› በሚል ሰበብ ጦር ሜዳ ልኮ ያስገድለዋል፡፡(ገጽ142)የዮዲት ወታደር መሆን የሚጀምረዉ እንቁዮጳግዮን ህዝበናኝን አንቃ ከገደለች በኋላ ነዉ፡፡

ዮዲት የነበራት ጥንካሬና ተዋጊነት፣በሌሎች ዘንድ አስፈሪ እንደትሆን አድርጓታል፡፡እንቁዮጳግዮንና ዮዲት በዝምድናም ተሳስረዋል፤የእንቁዮጳዮግዮን ልጅ መራ ተክለሃይማኖትን ዮዲት አግብታለችና፡፡(ገጽ 146-147)
የግዕዝን ቋንቋ ከአረባዊ ድምሰሳ የታደገችዉ፣የአረብ ‹‹ብክለት›› ያጋጠማቸዉን ቤተ-ክርስቲያናትን በማቃጠል፣አረብ ጳጳሳትን አስሮ ‹‹በመግደል››ና ከአጋዝዕያን ጋር የተነካኩና የግዕዝ ቋንቋን መለያ ያደረጉ ቤተ-ክርስቲያናት እንዲቋቋሙ በማድረግ ሲሆን፣ድርጊቷ በእስክንድሪያና በሮማ ጳጳሳት አስወግዟታል፡፡

እስከዛሬ የምንሰማዉ ስም ‹‹ማጥፋት›› ከንቱ አንደነበርና አንደሆነ፣ፕ/ር ፍቅሬ በጥናትና ምርምር አስደግፈዉ አቅርበዉልናል፡፡አዕምሯችን ላይ ሰር የሰደደን ታሪክ፣በአንድ አዳር ነቅሎ መጣል ከባድ ነዉ፡፡አዲሱን ታሪክ ያኛዉን ለመሞገት ብንጠቀምበት ጥሩ ይመስለኛል፡፡‹‹እሳቶ፣ዮዲት ጉዲት›› እያልን የምንጠራት ሴት፣ምን ያህል ለግዕዝ ቋንቋ ‹‹ባለዉለታ›› አንደሆነች እንረዳለን-ከመጽሃፉ፡፡

ሌላዉ፣ለኔ አዲስ የሆነብኝ፣የንግስተ-ሳባ(ኢትያኤል) ታሪክ ነዉ፡፡ብዙ ጸሃፊያን፣‹‹የንግስተ-ሳባ ታሪክ ተረት-ተረት ነዉ፡፡›› በማለት ይናገራሉ-ይጽፋሉ፡፡ፕ/ር ፍቅሬ ይህንን ታሪክ ከመጽሃፍ ቅዱስና ከላይ ከተጠቀሱት(‹‹ያሻር››ና ‹‹ዣንሸዋ››) አጣቅሰዉ፣ዕዉነተኝነቱን አረጋግጠዉልናል፡፡ንግስተ-ሳባ ወደሰለሞን ስትሄድ፣ሁለት ሴቶችን አስከትላ ነዉ፤እንዷ የግል ዘመዷ የሆነችዉ ሳሆይ የተባለች የአገዉ፣የራያና ቆቦ ንግስት ስትሆን፣ሌላኛዋ ደግሞ ቢልቂስ፣አዜብ ከምትባል ኢትዮጵያዊትና በወቅቱ የየመን(በዛን ጊዜ የመን ናግራን ትባል ነበር) ንጉስ ከነበረ ሰዉ በየመን የተወለደች ልዕልት ነበረች፡፡(ገጽ 109)

ከሶስቱ፣ሁለቱ ሴቶች ከሰለሞን ጸንሰዋል፡፡ንግስት ሳሆይ ‹‹ዜጋዬ››፣ንግስተ-ሳባ(ኢትያኤል)‹‹ምኒልክ››ን ወልደዋል፡፡በአፈ-ታሪክ ደረጃ የሚወራዉን በዕዉነተኛ ሰነዶች አማካይነት አረጋገጥን ማለት ነዉ፡፡

የኢትያኤል(ሳባ) እናት ‹‹እስያኤል›› በተባለ ዲበ-ሰብ ንጉስ ተገድላለች፤ምክንያቱም ከሌላ የንጉስ አገልጋይ ጋር ፍትወተ-ስጋ ስትፈጽም ተገኝታ፡፡ኢትያኤል(ንግስተ-ሳባ) የነገሰችዉ ‹‹እስያኤል››ን በመግደል ነበር፡፡

እንደአጋጣሚ ሆኖ ማንነቷን ደብቃ ንጉሱን ስታገለግል ቆይታ፣ጊዜና ቦታ ሲመቻችላት ትገድለዋለች፡፡በኋላም፣ንስሃ ለመግባት ጸሎት ስታደርስ፣እግዚአብሄር ተገልጦ፣በደለኛ እንዳልሆነች ይነግራታል፡፡ንግስተ-ሳባም ከጸጸት ትድናለች ማለት ነዉ፡፡(ገጽ 103፣104)

በስሙ አህጉር ስለተሰየመለት-ስለንጉስ ‹‹እስያኤል›› እናንሳ!እስያኤል ዲበ-ሰብ የሆነ ንጉስ ነበር፤150 ከሚደርሱ አንበሳዎች ጋር የተፋለመና በቅሎን ለመጀመሪያ ጊዜ በgenetic engineering ያስገኘም ንጉስ ነበር፡፡እርጅናን የሚከለከልበት መንገድ (mechanism)የነበረዉ ንጉስ እንደእርሱ ያለ አይመስለኝም፡፡ለ480 ዓመታት ኖሮ፣ከዚህ በኋላ መክረም ስለሰለቸዉ፣እግዚአብሄርን እንዲገድለዉ ተማጸነ፡፡ኢትያኤልን ጌታ አሳሰበና አስገደለዉ፡፡(ገጽ 98፣99ና 102)

ወደመጀመሪያ አካባቢ ስለኢትዮጵያ አሰያየም ስናወራ፣አብረን ያላነሳነዉ ነገር አለ፤ስለኢትዮጵና መልከጸዲቅ!
ኢትዮጵ የመልከጸዲቅ ልጅ ሲሆን፣የሁላችንም ‹‹የዘር ግንድ›› ነዉ፡፡መጀመሪያ ላይ ስሙ ‹‹ኢትኤል›› ነበር፡፡በእግዚአብሄር ትእዛዝ ወደኢትዮጵያ አምርቶ፣ኢትዮጵያ ላይ ነግሶ፣10 ወንድ ልጆችን ወልዶ፣እነርሱ ተባዝተዉ፣በ4000 ዓመታት ዉስጥ አሁን በስሙ ለሚጠሩት ወደ100 ሚሊየን ለሚጠጉት ኢትዮጵያዉያን አባት ሆነ ማለት ነዉ፡፡(ገጽ 41)

ስሙ ከ‹‹ኢትኤል›› ወደ ‹‹ኢትዮጵ›› የተቀየረዉ በእግዚአብሄር ትዕዛዝ ነበር፡፡እግዚአብሄር ‹‹ጣና ሃይቅ ስትደርስ ‹ዮጵ› በሚባል ቢጫ ወርቅ ትከብራለህ፡፡‹ኤል› የሚለዉን ቃል ከስምህ አዉጥተህ፣‹ኢት› የሚለዉን ከፊለ-ስምህን አስቀርተህ መጠሪያህን ‹ኢትዮጵ› ታደርጋለህ፡፡›› አለዉ፡፡(ገጽ 41ና 42) ከደረሰ በኋላ ነዉ-ያረፈባት ሃገር ‹‹ኢትዮጵያ›› የተባለችዉ፡፡

በግርድፉ ለማየት እንደሞከርነዉ፣መጽሃፉ ስለኢትዮ-አይሁድ ትስስርና ከዚህ በፊት በስህተት ስናነሳዉ የነበረዉን ታሪክ ለማጥራትና ለማስተካከል የሞከረ ነዉ፡፡ጥቂት የአርትዖትና የዓ/ነገር አሰካክ ግድፈት ቢታይም፣ግድፈቱ ግን የመጽሃፉን ድንቅ የትረካ ፍሰት አላደናቀፈም፡፡

የቀዳማዊ ምኒልክ ከታቦተ-ጽዮኑ ጋር 40,000 አይሁዳዉያንን ማምጣቱን፣ከዚህ በፊት ሰምተን አናዉቅም፡፡
በአጠቃላይ ፕ/ር ፍቅሬ ቶሎሳ ለኢትዮጵያዊነት ከባለፈዉ መጽሃፋቸዉ በበለጠ ሁኔታ፣በዚህ መጽሃፍ ተቆረቋሪነታቸዉን አሳይተዋል፤በርካታ የሰነድ ማስረጃዎችን ተጠቅመዋል።የእስራኤል ምክር ቤት አፈ-ጉባዔ ዮኤል ኤደልስቲን መጽሃፉን አንብበዉ፣‹‹…ስላለፈዉ ዘመን የእስራኤል ህዝብ ታሪክ በኢትዮጵያዊ ዕይታ ላከናወኑት ጥናታዊ ስራ አድናቆቴን ልግለጽልዎ እወዳለሁ፡፡›› በማለት፣አድናቆታቸዉን ለግሰዋል፡፡(ገጽ 6)ይህ ‹‹ብዙ›› የተባለለት መጽሃፍ፣በአብዛኛዉ ኢትዮጵያዊ ዘንድ የሚጨምረዉ አንዳች ነገር እንደሚኖር አምናለሁ፤ከኢትዮጵያዊያን ባሻገር፣እስራኤላዉያን በእብራይስጥ ተተርጉሞ ቢያነቡት(በቅርቡ መጽሃፉ ተተርጉሟል)፣የበለጠ አዕምሯቸዉን እንደሚያሰፉበትም አምናለሁ፡፡