November 5, 2017 10:40

እንስማው ሐረጉ

እንስማው ሐረጉ

የህዝብ ለህዝቡ ምክክር የውይይት መርሃ ግብር ጥሩ ጅምር ነው። በየትኛውም መስፈርት ይህ አይነቱ ቅዱስ ተግባር የህወሃት ሊሆን አይችልም። ህወሃት ህዝብ መከፋፈል እንጂ አንድ ማድረግ እራሱን አጥፍቶ ካልሆነ በስተቀር እንዴት ይቻለዋል? ከአሁን በኋላ የይምሰል ተሃድሶስ ምን ሊያመጣ? የባሰ ችግር እንጂ ህዝቡ ወደኋል አይመለስም። አቶ ለማ መገርሳ “ አንድ ህዝብ፤አንድ ሃገር፤ አንድ አላማ..” በማለት ሰሞኑን የጀመሩትን የአንድነት ጥሪያቸውን ገፍተውበታል። “ አንድ ህዝብ፤አንድ ሃገር፤“ የሚሉ የአንድነት ጥሪ ድምጾችን በኢህአዴግ ዘመን ያየሁት ወይም የሰማሁት በመኢአድ ልሳን ጋዜጣ “አንድነት” ላይ ወይም ታማኝ በየነ በአድዋ 100ኛ አመት ባደረገው ንግግር ላይ ነበር። አቶ ለማና አቶ ገዱ ንግግራቸውን ኢህአዴግአዊ ቅመም ሳያበዙበት ሲናገሩ ተስተውለዋል። ተሃድሶው የእውነት ፍንጭ እዬታየ ይመስላል።

አቶ ለማ ትናንትና እንዲህ አሉ “ኢትዮጵያዊነት ከደም አልፎ በልብ ውስጥ የተቀመጠ የተከበረ ማንነት ነው- ሞክሬው ባላውቅም‹‹ ሱስ ›› ነው፡” በመቀጠልም አቶ ለማ “ ‹‹እምንወዳችሁ እና የምናከብራችሁ መላ የአማራው ህዝብ ጋር ለመምከር እዚህ በመገኘቴ እጅጉን አመሰግናለሁ፡፡ ከኦሮምያ ለመጡት ልዑካን ከአባይ ጀምሮ ላደረጋችሁት ሁሉ ምስጋና ይግባችሁ››!!” በማለት የፍቅር ንግግር አሰምተዋል።

አንድ አባገዳ አባት ደግሞ እንዲህ ብለዋል “ በኦሮሚያ ክልል አንድ አማራ ወንድ እና ኦሮሞ ሴት ተጋቡ፡፡ወንድየው ኦሮምኛ አይችልም፡፡ ሴቷም አማርኛ አትችልም፡፡ግን በመንፈስ ተግባቡ እና ተጋቡ፡፡ተጋብተው የሁለቱንም ቋንቋ ተመማሩ፡፡እንኳንስ በቋንቋ በመንፈስ ይግባባሉ ፡፡ይሄ የሆነው ዛሬ አይደለም፡፡ከ 50 ዓመት በፊት ነው፡፡እና አማራ እና ኦሮሞ ህዝቦች እንዲህ ናቸው፡፡በመካከላችን ማንም አይገባም፡አማራ እና ኦሮሞ ሀይቅ ነው፡በሀይቁ ውስጥ ያሉ ነገሮች ሊረብሹን አይገባም፡ አንድ ነን። “ አዎ ትክክል ነው በሃይቁ ውስጠ ያሉት ህወሃቶች ሊረብሹን አይገባም። መቆም አበት።

እንዲዚህ ያለ ንግግር መስማት ከናፈቀን ድፍን 26 አመት ሞላን እኮ። እንግዳ ተቀባይ ፤ እሚበላው እንኳን ባይኖር ከጓዳ አፈላልጎ የሚጎረስ የማያጣውን ያገሬን ሰው በፊት የነበሩት የነዚህ የሁለቱ ወያኔ ሰራሽ ደርጅቶች መሪዎች “ነፍጥኛ ፤ ወራሪ“ እያሉ ነበር አፈር ድሜ እሚያበሉት። እስኪ አንባቢዎቼን ልጠይቅና ታምራት ላይኔ፤ አባዱላ ገመዳ፤ አዲሱ ለገሰ ፤ ተፈራ ዋልዋ፤ በረከት ስምኦን፤ (ያለምነውን ተውት) ወዘተ ስለአማራው ህዝብ ከተናገሩት ጥሩ ነገር ፈልጋችህ አሳዩኝ??

አገሪቱ እርስ በእርስ እንደ ሩዋንዳ ትተላለቅ ይሆን እዬተባለ ባለበት በዚህ ዘመን ይህን አይነት የፖሊሲ ለውጥ ከህወሃትም ይሁን ከአጋር ድርጅቶች በተናጠል ማዬት በጄ ብቻ ሳይሆን ተቃዋሚውም ሊደግፈው ይገባል። የኢትዮጵያ ህዝብ ለጭቆና እንግዳ አልነበረም፤ ዘላለሙን በራሱ ልጆች ሲጨቆን የኖረ ምስጊን ህዝብ ነው። የወያኔ የተለዬ የሚያደርገው አገሪቱን እንደ ጠላት ቆጥሮ አገር በቀል የዘር መድሉኦውና ህዝቡን በዘር መከፋፈላቸው፤ እርስ በውርስ ማጫረሳቸው ነው። አሁን የብአዴንና የኦህዴድ ወደ ህዝብ መምጣት ማስመሰልን ሳይሆን የምር መሆንን የሚጠይቅ ሰአት ነው። የተንሰራፋው ችግር በአንድ ሰሞን የህዝቦች ድራማ የሚቀረፍ አይደለም። ቁርጠኝትን ይጠይቃል። ከሟእለ ህጻናት እስከ ከፍተኛ ትምህርት ተቁማት ድረስ የትምህርት ፖሊሲ ለውጥ ይጠይቃል። አንድነትን፤ወንድማማችነትን በውይይት ሳይሆን በትግባር መዋልን ይጠይቃል። ባጠቃላይ ህወሃት ያፈራቸውን ተቋማት መቀዬር ግድ ነው። የትምህርት ፖሊሲው፤ የፌድራል አውቃቀር፤የስልጣን ሽግሽግ፤ የመከላከያ አዛዦች ሽግሽግ ወዘተ መቀየር አለበት። ይህ ማለት ህገ መንግስቱን ጨምሮ ባጠቃላይ ህወሃት ያፈራቸው ተቋማት ሁሉ ሙሉ በሙሉ ይቀየራሉ ማለት ነው።

አቶ ገዱም እንዲዚሁ የአንድነት ደምጽ አሰምተዋል። ቀድሞውንም የኢትዮጵያ ህዝብ አንድ ነው። የኢትዮጵያ ህዝብ ጠላት ካልለያዬው ሊለያይ የማይችል ህዝብ መሆኑን ባለፉት 27 አመታት የተሞከረበት ፈተና ቁልጭ አድርጎ ያስረዳል። ወያኔ በብአዴንና በአኦህዴድ አማራና ኦሮሞ ያልሆኑትን አመራር ላይ በማስቀመጥ ሁለቱን ህዝቦች እንደጠላት እርስ በእርስ በማጋጨት እያሸበረ ሲጋዛ ቆይቷል። ይህን ለማድረግ ደግሞ ዲቃላ አስመሳይ መሪዎች ነበሩት። አሁን የመጡት ዲቃላ አለመሆናቸውን እያዬን ይመስላል፤ እኛም በጄ ብለናል። እደጉ ተመንደጉ ማለት ነው። የብአዴኑ ደግሞ የባሰ ነበር። አንዳቸውም አማራ ሳይሆኑ አማርኛ የሚናገሩ እርትራዊያንና ትግሬ ዘር ያለባቸውን ሰብስበው የብአዴን መሪዎች ተብለው በህዝቡ ተጭነውበት ነገር ግን በስምም በምግባርም አማራን ፈጽሞ የማይወክሉ፤ይባስ ብለው እንዴውም እወክለዋለሁ የሚሉትን ምስጊን የአማራ ህዝብ እራሳቸው እንደ ጨቋኝ አስፈርጀው ቁም ስቅል ሲያበሉት ሩብ ምእተ አመት አለፋቸው። አሁን እነዚህ ሁለቱ ታላላቅ የኢትዮጵያ ወንድማማች ጎሳዎች ከራሳቸው የወጡ ልጆችን መሪዎች ያገኙ ይመስላል። መቼም እነዚህ መሪዎች እንደቀደሙት የህወሃት ፈረስ ለመሆን፤የውሸት ተሃድሶ ዘፈን እያቀነቀኑ አይመስለኝም። ንግግራቸውና አጀማማራቸው እንደ ጥንቶቹ አባቶቻችን እውነት ያለበት ይመስላል። አሁን ሜዳውም ፈረሱም የነሱ ነው። የባርነት ምግባር ተጠናውቷቸው መጋለብ እንደለመደ ፈረስ ህወሃት እንዲጋልባቸው አጎንብሰው ካልጠበቁት በቀር ከአሁን በኋላ ህወሃት ሊያሸንፋቸው አይችልም። መጋለብ ከፈለጉም የኢትዮጵያ ህዝብ የጀመረውን አብዮት መስዋእትነት ይበዛ እንደሆን እንጅ የማታ ማታ በድል ማጠናቀቁ የማአይቀር ሃቅ ነው።

መልካም ሳምንት

እንስማው