November 9, 2017 mail
ሳስተውለው ውዬ ቆሜ ስመረምር
ጥበቡ ገብቷቸው መሄጃውን አውቀው
መላ የጨበጡት ስሌት አስተካክለው
ከተጠቀሙበት ኃያል ብልሃቶች
አንዱ ማስመሰል ነው ለመኖር ከሰዎች
እንደውም አንዳንዱ ከማስመሰል አልፎ
በረቀቀ ጥበብ በተንኮል ቆልፎ
ለተዘጋጀበት ላሰበበት ዕቅድ
ማሰለፍ ይችላል በግድና በውድ
እንዲሁም ሌላውን አድርጎ መሰላል
ሁሉንም አሟልቶ እላይ በመንጠልጠል
ሲፈልግ አጣልቶ፤ ሲሻው በማስታረቅ
ሌላን እየጎዳ ጥቅሙን በማስጠበቅ
በተገኘው መላ ባዘጋጀው መንገድ
መረቡን ዘርግቶ ገንዘብ ለማሳደድ
ምንም ጊዜ – የትም እሱን አስበልጦ
አምሮ ተሽቀርቅሮ በአልባሳት አጊጦ
ድሮውንም ያለው የቱጃር ቤተሰብ
ገና በልጅነት ያየ ብዙ ገንዘብ
ሃይማኖት አክባሪ ጿሚ ጸሎተኛ
እጁ እማይታጠፍ ካየ ችግረኛ
መምሰሉ አስገርሞኝ በማውቀው ቀንቼ
ልመስል ተነሳሁ እጆጄን ዘርግቼ
ብዙም ሳልገፋበት ገና ከጅምሩ
አላምርብህ አለ በኔ ላይ ነገሩ
በማያስለቅሰው አስቤ ለማልቀስ
መስዬ ቁጭ አልኩኝ የተራበ ፈረስ
ደስተኛ ለመምሰል ሳቁንም ብስቀው
ፊቴ መስሎ ታየ መርፌ ‘ሚወጋ ሰው
ሳላዝን አዝኜ ብሆን እንደራራ
መስዬ ታየሁኝ ትያትር ‘ምሰራ
አንዱን ካንዱ ጋራ በወሬ አስማምቼ
የራሴን ቆጥቤ የሰው አድፋፍቼ
ከሌላ እንዳየሁት ለማድረግ ብነሳ
ሸክሙ የከበደ መጣብኝ ወቀሳ
ካንዱ ተበድሬ ለሌላ በመክፈል
ብዙ ገንዘብ ያለው ለመባል ለመምሰል
እንደ ጮካዎቹ መንገድ ብዘረጋ
ልወጣው የማልችል ገጠመኝ አደጋ
ደግሞም አሰኝቶን ተጋብዞ መጋበዝ
በእዳ ደፈቀኝ አመጣብኝ መዘዝ
በፖለቲካው መስክ ገብቼ ልመራ
ተመራጭ ሆንኩና ያዝኩኝ ትልቅ ስፍራ
እሱም አልቀናኝም ወራትም አልዘለኩ
አጎብዳጅ ተብዬ ተዋርጄ ወረድኩ
ሁሉም አልሆን ብሎኝ ብመለስ ቦታዬ
አንድ ነገር ወድቆ ቆየኝ ከገላዬ
ምንድነው የጠፋኝ እያልኩኝ ስዋትት
ለካስ ሌላ ሰው ነኝ ራሴን አጣሁት
ማስመሰል ሳልጀምር በፊት የምታውቁኝ
ወሮታ እከፍላለሁ “ያን እኔን አፋልጉኝ!”