26 November 2017ታምሩ ጽጌ

አንድ ተከሳሽ ልብሱን በማውለቅ የደረሰበትን ጉዳት ለችሎት አሳይቷል

ዳኛው በወልቃይት ጉዳይ ሊዳኙ አይገባም ያሉ ተከሳሾች መቃወሚያቸውን አስገብተዋል

በጎንደር ከተማ፣ በተለያዩ በክልሉ ከተሞችና በባህር ዳር ተከስቶ በነበረው ግጭት ምክንያት በሽብር ተግባር ወንጀል ክስ ከተመሠረተባቸው 35 ተከሳሾች ውስጥ፣ አራቱ ችሎት በመድፈር ወንጀል ጥፋተኛ ተብለው ቅጣት ተጣለባቸው፡፡ ሁለት የዋልድባ መነኮሳት በተካተቱበት በእነ ተሻገር ወልደ ሚካኤል የክስ መዝገብ አቶ ተሻገር ወልደ ሚካኤል በሦስት ወራት፣ አቶ በለጡ አዱኛ፣ አቶ ተስፋ ሚካኤል አበበና አቶ እንዳለው ፍቃዴ እያንዳንዳቸው በስድስት ወራት እስራት እንዲቀጡ መዝገቡን እየመረመረው የሚገኘው የፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ አራተኛ ወንጀል ችሎት ሐሙስ ኅዳር 14 ቀን 2010 ዓ.ም. ፍርድ ሰጥቷል፡፡

ፍርድ ቤቱ የቅጣት ውሳኔ ሊሰጥ የቻለው በዕለቱ ቀጠሮ ተሰጥቶት በነበረው መዝገብ መቃወሚያ ላይ ብይን ከመስጠቱ በፊት ተከሳሾቹ፣ ሌሎች ተከሳሾች አንድ ዳኛ እንዲነሳላቸው ያቀረቡት ጥያቄ የእነሱም እንደሆነ በመግለጽ የፍርድ ቤቱን ሥራ በማወካቸው መሆኑን ፍርድ ቤቱ ገልጿል፡፡ ፍርድ ቤቱ በርካታ መዝገቦች እንዳሉና ጊዜ እንደሌለው በመግለጽ ቀጠሮ ከያዘበት መዝገብ ውጪ ሌላ አቤቱታ እንደማያስተናግድ በመግለጹ፣ ‹‹አቤቱታ አለን ስሙን፣ ዳኛው የተቀመጡት እኛን ለመበቀል ነው፤›› በማለት የችሎቱን ሥራ በማወካቸው ፍርድ ቤቱ ቅጣቱን ሊወስን መቻሉን አስታውቋል፡፡

አራቱ ተከሳሾች ተለይተው የፍርድ ቤት መድፈር ወንጀል ቅጣት የተጣለባቸው አንድ ተከሳሽ ተነስቶ ሲናገር ዳኛው፣ ‹‹ችሎት በመድፈር ትቀጣለህ›› ሲሉ ሌሎቹም ተከሳሾች ‹‹እኛንም ቅጡን›› በማለት ደጋግመው ተናገሩ፡፡ ነገር ግን ዳኛው በድጋሚ ቀድሞ የተናገረውን ተከሳሽ እንዲወጣ በማዘዛቸው፣ ተከሳሹ ሲወጣ ‹‹ምን ያወራጭሃል?›› የሚል ጥያቄ ሲያቀርቡለት፣ ሌሎቹ ተከሳሾች ኃይል የተሞላበት ተቃውሞ በማቅረባቸው ችሎቱ ሥራውን አቋረጠ፡፡  ዳኞች ከዓቃቤ ሕግና ከጠበቆች ጋር ከተመካከሩ በኋላ ችሎቱ በድጋሚ ሲሰየም፣ የፍርድ ቤቱ ታዳሚዎች ተከልክለው ተከሳሾቹ ብቻ ገብተዋል፡፡ ፍርድ ቤቱም በአራቱ ተከሳሾች ላይ ከላይ የተጠቀሰውን ቅጣት ጥሎ፣ ባቀረቡት የክስ መቃወሚያ ላይ ብይን ለመስጠት ለታኅሳስ 11 ቀን 2010 ዓ.ም. ቀጠሮ ሰጥቷል፡፡ በሌላ መዝገብ በሽብር ተግባር ወንጀል ክስ የተመሠረተበት አስቻለው ደሴ የተባለ ተከሳሽ የደረሰበትን በደል የሚገልጽ አቤቱታ በወረቀት ጽፎ ካስገባ በኋላ የቃል አቤቱታ ለማሰማት እጁን ሲያወጣ ችሎቱ ስላልተቀበለው በድምፅ እንዲሰማ ቢጠይቅም ተቀባይነት በማጣቱ ሱሪውን በማውለቅ ኃፍረተ ሥጋውን እያሳየ ‹‹ሕዝብ ይፍረደኝ›› በማለቱ ሲቃ በተመላ ድምፅ ያለቀሱ የፍርድ ቤት ታዳሚዎች ነበሩ፡፡

ከተከሰሱበት የወልቃይት የማንነት ጥያቄ ጋር በተገናኘ የችሎቱ ዳኛ አቶ ዘርዓይ ወልደ ሰንበት ሊዳኟቸው እንደማይችሉ በመግለጽ ተቃውሞአቸውን ኅዳር 11 ቀን 2010 ዓ.ም. ያቀረቡት እነ አቶ መብራቱ ጌታሁን፣ መቃወሚያቸውን በጽሑፍ ኅዳር 14 ቀን 2010 ዓ.ም. አስገብተዋል፡፡ በዳኛው መቀጠል አለመቀጠል ላይ ውሳኔ ለመስጠት ለታኅሳስ 9 ቀን 2010 ዓ.ም. ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

ሪፖርተር