ፍርድ ቤቱ በፌስቡክ በሚወጡ ዘገባዎችና ፅሁፎች ላይ  የፌደራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት ልደታ ምድብ 4ኛ ወንጀል ችሎት ጦማሪ ማህሌት ፋንታሁን “አክላቸው ወንድወሰን” በተባለ የፌስቡክ አድራሻ የዳኛ ስም ተጠቅሶ የተፃፈ የፍርድ ቤቱን ክብር የሚነካ ፅሁፍ አጋርተሻል በሚል ማስጠንቀቂያ ሰጥቷል።

አሚር በፌስቡክ የተፃፈ ፅሁፍ ስር አስተያየት እንደሚሰጥ፣ እንዲሁም እኔ (ጌታቸው ሺፈራው) የምፈልገውን የፍርድ ቤት ውሎ ብቻ ቆርጬ እንደምዘግብ ይህም ምን “ሸንቆጥ” ለማድረግ እንደተፈለገ ፍርድ ቤቱ እንደሚረዳው፣ ለሌላ ሰውም መረጃ እንደምልክ ፍርድ ቤቱ ገልፆአል። ፍርድ ቤቱ ለሌላ ሰው መረጃ ትልካለህ ሲል የጠቀሰው ማስረጃም ሆነ የሰው ስም የለም።

ናትናኤል (የአባቱ ስም ያልተጠቀሰ)፣ አንገቱ ላይ “ሻርፕ” ያደርጋል የተባለና በችሎት ያልነበረ ግለሰብም ስሙ በችሎት ተጠቅሷል።

ጦማሪ ማህሌት ፋንታሁን በችሎት ቀርባ አጋርተሽዋል ስለተባለው ፅሁፍ የተጠየቀችው በጠዋቱ የፍርድ ቤት ጊዜ ሲሆን ለከሰዓት ተቀጥሮ ከአሁን ቀደም የምትፅፋቸው ፅሁፎች አጋራችው የተባለውን አይነት ይዘት እንደሌለው በመጥቀስ በተግሳፅ እንደታለፈች ፍርድ ቤቱ ገልፆአል።

ፌስቡክ ላይ የተፃፉ ፅሑፎችን ዳኞች እንደሚያነቡ የገለፀው ፍርድ ቤቱ ይህን የምናደርገው የፍርድ ቤቱን ክብር ለማስጠበቅ ነው ብሏል። ፍርድ ቤቱ “እንዲህ የምናደርገው እናንተን ሃራስ ለማደረግ አይደለም” ቢልም ለሌላ ሰው መረጃ መላክና መሰል ጉዳዮች ላይ ተላከለት የተባለ ሰው ስም፣ ምን እንደተላከ እና እንዴት እንደተላከ ሳይጠቅስ ማስጠንቀቂያ መሰል ምክር ሰጥቶ አልፏል።

በሌላ በኩል የፌደራል ፖሊስ አክላቸው ወንድ ወሰን የሚል የፌስቡክ አድራሻን አጣርቶ ለፍርድ ቤት እንዲያቀርብ ትዕዛዝ ተላልፏል።

ከአሁን ቀደም በዚሁ ችሎት መሃል ዳኛው “የተቀረፀ በሚመስል መልኩ ቃል በቃል እየተዘገበ ነው” እንዲሁም የግራ ዳኛው የተዛቡ ዜናዎች በፌስቡክ እየተላለፉ ነው በሚል ማስጠንቀቂያ መሰጠቱ የሚታወስ ነው።