እአአ 2014 በእስራኤል የሚኖሩ ስደተኞች በሀገሪቱ ውስጥ የጥገኝነት መብት እንዲሰጣቸው የተቃውሞ ሰልፍ ባደረጉበት ወቅት
JACK GUEZ
አጭር የምስል መግለጫ እአአ 2014 በእስራኤል የሚኖሩ ስደተኞች በሀገሪቱ ውስጥ የጥገኝነት መብት እንዲሰጣቸው የተቃውሞ ሰልፍ ባደረጉበት ወቅት

መቀመጫቸውን እስራኤል ያደረጉ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት ሩዋንዳ ከእስራኤል የሚባረሩ ስደተኞችን እንዳትቀበል ለፕሬዝዳንት ፖል ካጋሜ ግልጽ ደብዳቤ ጻፉ።

የእስራኤሉ ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ እና የሩዋንዳው ፕሬዝዳንት ፖል ካጋሜ በእስራኤል የሚገኙ ስደተኞችን ወደ ሩዋንዳ ለማዘዋወር የጀመሩትን ድርድር ከፍፃሜ ለማድረስ በነገው ዕለት ተገናኝተው ይመክራሉ።

እስራኤል ከ35 ሺ በላይ ስደተኞችን ወደ ሩዋንዳ ልታዘዋውር ነው

የእስራኤል ባለስልጣናት ሰሞኑን በሰጡት መግለጫ ከ35ሺ በላይ የሚሆኑ ተቀማጭነታቸውን እስራኤል ያደረጉ የኤርትራና የሱዳን ስደተኞችን ወደ ሩዋንዳ እንደሚዘዋወሩ ፍቃደኛ ካልሆኑ ደግሞ እሥራት እንደሚጠብቃቸው ገልጸው ነበር።

በሌላ በኩል የሩዋንዳ ውጭ ጉዳይ ሚኒስተር ሉዊስ ሙሺኪዋቦ ከኒው ታይምስ ጋር ባደረጉት ቆይታ ሩዋንዳ የምትቀበላቸው ስደተኞች በገዛ ፈቃዳቸው ወደ ሩዋንዳ መምጣት የሚፈልጉትን ብቻ ነው ብለዋል።

መቀመጫቸውን እስራኤል ያደረጉ ሰባት የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማት ይህን የእስራኤል አካሄድ ክፉኛ ኮንነዋል። ተቋማቱ ለሩዋንዳው ፕሬዝዳንት ፖል ካጋሜ ማብራሪያ እንዲሰጡዋቸው በጻፉት ግልጽ ደብዳቤ ጠይቀዋል።

“የተከበሩ የሩዋንዳ ሪፓበሊክ ፕሬዝዳንት ፖል ካጋሜ፤ ከእርሶና ከሩዋንዳ ህዝብ አስቸኳይ ትብብር እንሻለን። እስራእል እና ሩዋንዳ መልካም ግንኙነት ቢኖራቸውም፤ ግንኙነታቸው የአፍሪካ ስደተኞችን ሕይወት ለሸቀጥ ማቅረብን ሊጨምር አይገባም” ብለዋል የሰብዓዊ መብት ተሟጋች ተቋማቱ ለካጋሜ በጻፉት ደብዳቤ።

ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንያሚን ኔታንያሁ በጉዳዩ ላይ በሰጡት መግለጫ ”ሩዋንዳ አፍሪካውያን ስደተኞችን ከእስራኤል ለመቀበል ተስማምታለች። ስደተኞቹ ተገደው ይወጣሉ። ወደ ሩዋንዳ ለመሄድ ካልተስማሙ ደግሞ የሚጠብቃቸው እሥር ብቻ ነው” ብለዋል።

“እንዲህ ያለ የሰዎችን ነፃነት የሚጋፋ ስምምነት እንደማያጸድቁ ከፍተኛ እምነት አለን። አፍሪካውያን ስደተኞች በዚህ መልክ እንዲሸጡ እንደማይስማሙም ተስፋ አለን። ከፍቃዳቸው ውጪ የሚባረሩትን ስደተኞች እንደማትቀበሉ ለጠቅላይ ሚኒስትር ኔታንያሁ ያሳውቁልን” ይላል ደብዳቤው።

“ከእስራኤል ጠቅላይ ሚኒስትር ቤንጃሚን ኔታንያሁ ጋር ያለዎትን መልካም ግንኙነት ተጠቅመው እስራኤል የስደተኞት አገር መሆኗን እንዲያሳውቁልንና የኤርትራ እና የሱዳን ስደተኞችን ተቀብላ ማስተናገድ እንዳለባት ይንገሩልን” ሲሉ ሰብዓዊ መብት ተከራካሪ ድርጅቶች በደብዳቤያቸው ጠይቀዋል።

እአአ 2014 በእስራኤል የሚኖሩ ስደተኞች በሀገሪቱ ውስጥ የጥገኝነት መብት እንዲሰጣቸው የተቃውሞ ሰልፍ ባደረጉበት ወቅት
GALI TIBBON
አጭር የምስል መግለጫ እአአ 2014 በእስራኤል የሚኖሩ ስደተኞች በሀገሪቱ ውስጥ የጥገኝነት መብት እንዲሰጣቸው የተቃውሞ ሰልፍ ባደረጉበት ወቅት

የጋራ ደብዳቤ የፃፉት የሰብዓዊ መብት ድርጅቶች የሚከተሉት ናቸው፦

  • በእስራኤል የስደተኞች እና ጥገኝነት ጠያቂዎችን እርዳታ ሰጪ ተቋም (ኤ.ኤስ.ኤስ.ኤፍ)
  • በእስራኤል የሰብዓዊ መብት ተሟጓች የሕክምና ባለሙያዎች
  • መረጃ ለስደተኞች እና ተፈናቃዮች
  • በእስራኤል የአምነስቲ ኢንተርናሽናል ቢሮ
  • በእስራኤል የዜጎች ሰብዓዊ መብት ማህበር
  • ካቭ ላኦ ኦቭ – ሰራተኞች መረጃና መስመር
  • በእስራኤል የኤ.ች.አይ.ኤስ ቢሮ

የእስራኤል መዲና በሆነችው ቴልአቪቭ የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን ቢሮ የህዝብ መረጃና ኮሚዩኒኬሽን ኃላፊ ሻሮን ሐሬል ስደተኞችን ወደ ሶስተኛ ሃገር የማዛወሩ ጉዳይ ለኮሚሽኑ አሳሳቢ ሆኖዋል ሲሉ ለቢቢሲ ተናግረው ነበር።

ሻሮን ከቢቢሲ ጋር በነበራቸው ቆይታ “ከስደተኞቹ መካከል ብዙ ሴቶች እና ህጻናት መኖራቸው ችግሩን የተወሳሰበ ያደርገዋል። ከዚህ ቀደም በነበረን ልምድ ወደ ሶስተኛ ሀገር የሚዘዋወሩ ስደተኞች የሥራ ፍቃድ ማግኘት አይችሉም፤ የደህንንት ስሜት ስለማይሰማቸው ሜደትራንያን ባህርን አቋርጠው ለሌላ ስደት ይነሳሉ” ሲሉ ያስረዳሉ።