በሱዳን መንግስት የሚመራው የሀገሪቱ ጦር የኢትዮጵያን ድንበር ጥሶ መግባቱን መረጃዎች አመለከቱ፡፡ ከባድ መሳሪያዎችን እንደታጠቀ የተነገረለት የሱዳን ጦር፣ ወደ ኢትዮጵያ ድንበር መግባቱን ተከትሎ፣ መከላከያ ሰራዊት ወደ ስፍራው መጠጋቱን ከመረጃዎች ገለጻ ለመረዳት ተችሏል፡፡ ይህን ተከትሎም ኮረደም፣ ገላዋን እና ኮርመር በተባሉት የኢትዮጵያ ቀበሌዎች ከፍተኛ ውጥረት የነገሰ ሲሆን፣ በስፍራው የሚገኙ አርሶ አደሮችም ሀሳብ ላይ መውደቃቸው ታውቋል፡፡ የሱዳን ጦር የተጠቀሱትን ቀበሌዎች መቆጣጠሩንም የመረጃ ምንጮች ጠቁመዋል፡፡

ከባድ መሳሪያዎችን እንደታጠቀ የተነገረለት የሱዳን ጦር ለምን ዓላማ የኢትዮጵያን ድንበር ጥሶ እንደገባ እስካሁን የታወቀ ነገር የለም፡፡ ይህ ዜና እስከተጠናከረበት ሰዓት ድረስ የሱዳን ጦር እና ጦሩ ወደ ኢትዮጵያ ድንበር መግባቱን ተከትሎ ወደ ስፍራው የተጠጋው የኢትዮጵያ መከላከያ ጦር፣ ቃታቸውን አቀባብለው መፋጠጣቸውን መረጃዎች አመላክተዋል፡፡ በአካባቢው የሚገኘው እና መሳሪያ የታጠቀው አርሶ አደርም፣ ራሱን ለመከላከል ትጥቁን ማሰናዳቱን የጠቆሙት መረጃዎች፣ ነገሩ በቀጣይ ወዴት እንደሚያመራ እንደማይታወቅም መረጃዎቹ ያክላሉ፡፡

ከዚህ ቀደም የሱዳን ጦር አባላትም ሆኑ በድንበር ላይ የሚኖሩ ሱዳናውያን የኢትዮጵያ ድንበር ድረስ ዘልቀው በመግባት፣ በኢትዮጵያ አርሶ አደር ላይ ጥቃት ሲፈጽሙ መቆየታቸው አይዘነጋም፡፡ ከጥቃት በተጨማሪም በኢትዮጵያ አርሶ አደሮች የተዘሩ ሰብሎችን አውድመው ይሔዱ ነበር፡፡ በተለይ ከኢትዮጵያ አማራ ክልል ጋር በሚዋሰነው የሱዳን ክፍል፣ ተደጋጋሚ ጥቃት ሲፈጸም ቆይቷል፡፡ በሱዳኖች በኩል ሲፈጸም የነበረው ጥቃት ያማረረው የኢትዮጵያ ገበሬ፣ አቤቱታውን ለመንግስት አቅርቦ ነበር፡፡ በወቅቱ በስልጣን ላይ የነበሩት አቶ መለስ ዜናዊ፣ ለሱዳኖች በማገዝ የኢትዮጵያን ገበሬ አስጠንቅቀው ነበር፡፡ በእሳቸው እግር የተተኩት አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝም በተመሳሳይ ሁኔታ፣ በድንበር አካባቢ ከሱዳኖች ጋር እየተፈጠረ ላለው ግጭት ተጠያቂዎቹ በአካባቢው ያሉት የኢትዮጵያ አርሶ አደሮች መሆናቸውን በመግለጽ፣ ወገናዊነታቸውን ለሱዳን ገልጸው ነበር፡፡ የቀድሞዉም ሆነ የአሁኑ ጠቅላይ ሚኒስትሮች ይህን የተናገሩት መቶ ፐርሰንት በተቆጣጠሩት ፓርላማቸው ሲሆን፣ በወቅቱም ጉዳዩ ብዙዎችን አስቆጥቶ ነበር፡፡ ሁለቱ ሰዎች የኢትዮጵያ ጠቅላይ ሚኒስትር ሆነው ሳለ፣ ለባዳ መወገናቸው ብዙዎችን አሳዝኖ ነበር፡፡

BBN news December 4, 2017