የዘንድሮው በዓል በአፋር
Alex Solomon

በአፋር ክልል መዲና ሰመራ “በሕገ-መንግስታችን የደመቀ ሕብረ ብሔራዊነታችን ለህዳሴያችን” በሚል ርዕስ ለአስራ ሁለተኛ ጊዜ በመከበር ላይ የሚገኘው ‘የብሔሮች፣ ብሔረሰቦችና ሕዝቦች’ ቀን በዓል ከወትሮውም በበለጠ ለበርካታ ጥያቄዎች መጫር ምክንያት ሆኗል።

ጥያቄዎቹ በክብረ በዓሉ ፋይዳ ላይ ሳይወሰኑ ዕለቱ ይዘክራቸዋል ተብለው እስከሚታመኑት ሕግ-መንግሥት እንዲሁም ብሔርን መሰረት ያደረገ ፌዴራላዊ ሥርዓት ላይም የሚያጠነጥኑ እንደሆኑ ይስተዋላል።

ባለፉት ወራት በተለያዩ የአገሪቷ አካባቢዎች የተቀሰቀሱ ብሔር ተኮር ግጭቶች እና ማንነት ላይ ባነጣጠሩ ጥቃቶች ምክንያት ከፍተኛ ቁጥር ያላቸው ዜጎች ለህልፈት ተዳርገዋል።

ከዚህም በተጨማሪ በመቶ ሺዎች የሚቆጠሩት ደግሞ ከመኖሪያ ቀያቸው መፈናቀላቸው እና ንብረቶቻቸው መውደሙ፤ የዘንድሮውን ክብረ በዓል በተለየ ሁኔታ ትርጉም አልባ ያደርገዋል ሲሉ የሚከራከሩ ወገኖች አሉ።

“የፕሮፓጋንዳ ፍጆታ”

በኢንዲኮት ኮሌጅ የዓለም አቀፍ ሕግ እና የሰብዓዊ መብቶች መምህር የሆኑት ዶክተር ሰማኸኝ ጋሹ የአመለካከት፣ የፍላጎት እና የፖለቲካ አቋም ልዩነቶች በገነኑባቸው አገራት የብሔር ብሔረሰብ ቀንን የመሳሰሉ በዓላት የሰላም እና የእርቅ ዓላማን ለማራመድ ብሎም አገራዊ አንድነትን ለማጠናከር ሊያገለግሉ እንደሚችሉ ያወሱና፤ በእኛ አገር እየሆነ ያለው ግን ከዚህ የተለየ ነው ሲሉ ይናገራሉ።

“ኢትዮጵያ ውስጥ የብሔር ብሔረሰቦችን ቀን እንዲሁ ለፕሮፓጋንዳ ፍጆታ እና የሥርዓቱን ተቀባይነት የማጠናከር ዓላማን የሰነቀ ነው” ሲሉ ዶክተር ሰማኸኝ ለቢቢሲ ተናግረዋል።

በዓሉ የሚወክለው ሥርዓት መሠረታዊ ችግሮች የሚስተዋሉበት ከመሆኑም ባሻገር፤ የዲሞክራሲ እና የሰብዓዊ መብት መርሆች ሊከበሩ ባለመቻላቸው የአገሪቱ ፖለቲካዊ ምህዳር ከድጥ ወደማጥ በመቆርቆዝ እንደሚገኝ ዶክተር ሰማኸኝ ጨምረው ይገልፃሉ።

የሰመራ ከተማ በዓሉን ለማክበር ከየሥፍራው የመጡ እንግዶቿን ስታስተናገድ በሥራ ተጠምዳ ሰነባብታለች።

ለዚህም ዝግጅት በመቶ ሚሊዮን ብር የሚቆጠር ገንዘብ እንደዋለ ይገመታል።

ከሁለት ዓመት በፊት በጋምቤላ ከተማ ላይ የተስተናገደው ክብረ በዓል ከ340 ሚሊዮን ብር በላይ እንደወጣበት መዘገቡ ይታወሳል።

በአንድ በኩል በአሁኑ ሰዓት ከመኖሪያ ቀያቸውን የተፈናቀሉ በመቶ ሺህዎች የሚቆጠሩ ዜጎች ለማቋቋም ከፍተኛ ገንዘብ ያስፈልጋል።

ለጥቂት ቀናት የሚካሄዱ የአደባባይ ትርዒቶች እና ዓውደ ጥናቶች በተለያዩ ብሔሮች መካከል መከባበርን ለማምጣት፣ የፖለቲካ እኩል ተሳታፊነትን እንዲሁም የምጣኔ ኃብት እኩል ተጠቃሚነት ለማስገኘትም የሚያበረክቱት እዚህ ግባ የሚባል ፋይዳ እንደሌለ በማውሳት በበዓሉ ከመገኘት እንዲቆጠቡ በተለይ የኦሮሚያ መብት ተሟጋቾች ሲወተወቱ ቆይተዋል።

የዘንድሮው በዓል በአፋር
Alex Solomon

“ብዝኃነት አደጋ ላይ ወድቋል”

በአዲስ አበባ ዩኒቨርሲቲ የፌዴራሊዝም መምህር የሆኑት አቶ ናሁሰናይ በላይ አገሪቷ ያለችበት ፖለቲካዊ ነባራዊ እውነታ ዕለቱ የሚወክለውን ሥርዓት ከመቼው ጊዜ በበለጠ ማክበር የሚያስፈልግበት ደረጃ ላይ መደረሱን የሚጠቁም ነው ይላሉ።

“በዕለቱ የምናከብረው ሕገ-መንግሥት ላይ ያለ መርኅ ነው። ይህ መርኅ የፖለቲካ ከባቢው መጥፎ ሲሆን ወይንም አንዳች ዓይነት ኹከት በተፈጠረ ቁጥር የምናከብረው ወይም ደግሞ የምንተወው መሆን የለበትም” በማለት አቶ ናሁሰናይ ለቢቢሲ ገልፀዋል።

“የብሔር ብሔረሰቦች ቀን ስንል ብዝኃነትን መቀበል ማለት ነው። በብዝኃነት ውስጥ የሚፈጠር አንድነትን መዘከር ማለት ነው። ስለዚህ ከዚህ ሰዓት በላይ መቼ እናክብር? በአሁኑ ወቀቅት ተግዳሮቶችና መፈራቀቅ የበዙበት ጊዜ ነው። ብዝኃነት ፈተና ላይ የወደቀበት ሰዓት ነው” ሲሉ ጨምረው ተናግረዋል።

እንደዚያም ሆኖ ግን በየስፍራው የተነሱ የመብት ጥያቄዎች፣ ተቃውሞዎች፣ ግጭቶች እና ጥቃቶች በየዓመቱ ህዳር 29 ከሚዘከረው ሕገ-መንግሥትና ካለው የፌዴራሊዝም ሥርዓት ጋር አይገናኙም በማለት አቶ ናሁሰናይ ይከራከራሉ።

“ዜጎች ያነሷቸው የተለያዩ የዲሞክራሲ እና የምጣኔ ኃብት ተጠቃሚነት ጥያቄዎች ናቸው። መብት ይሰጠኝ የሚል ጥያቄ የዲሞክራሲ ጥያቄ ነው። ፌዴራሊዝም የሰጠኝ መብት ስለበዛ ይቀነስልኝ ብሎ የመጣ አካል ግን የለም። በራሴ ሰዎች መተዳደር አስጠልቶኛልና በራሴ ቋንቋ መናገር አልፈልግም ያለ ሕዝብ መኖሩን አላውቅም። እነዚህን ጥያቄዎች ሲነሱ ነው ፌዴራሊዝሙ ጥያቄ ውስጥ ወደቀ የምንለው። ያሉትን ጥያቄዎች በሙሉ ወደ ሥርዓቱ መውሰድ ስህተት ነው” ይላሉ።

“ሕገ መንግቱ አካታች አይደለም”

መፍትሄ ካልተሰጠ ሊደርስ በሚችለው አደጋ መጠን ላይ መግባባት፤ እየመጣ ያለውን ማዕበል ለማስቀረት የመጀመሪያው እርምጃ ነው የሚሉት አቶ ናሁሰናይ የችግሮቹን መሠረታዊ መንስዔ የአገሪቱ የፖለቲካ አመራር አካላት ፌዴራሊዝምን እና ብዝኃነትን ለመቀበል አቅምና ትከሻ ካለመደንደን ጋር ያያይዙታል።

ፖለቲካው ሕገ-መንግሥቱን እንዲመስል ማስቻል ዓይነተኛው መዋቅራዊ መፍትሄ እንደሆነ አቶ ናሁሰናይ ይገልፃሉ። “እገሌን በእገሌ የመተካት ጉዳይ አይደለም። የሕዝብ ሉዓላዊነት የሚረጋገጥባቸው የምርጫ እና የውክልና ሥርዓቶች በሕገ-መንግሥቱ መሠረት ይሁኑ። የዜጎች ኢትዮጵያዊነት ትርጉም የሚኖረው በሕገ መንግሥቱ መሠረት መብቶቻቸው ሲጠብቁላቸው ብቻ ነው።”

እንግሊዝ አገር በሚገኘው በኪል ዩኒቨርስቲ ሕግን የሚያስተምሩት ዶክተር አወል አሎ ከአሃዳዊ ሥርዓት በበለጠ ፌዴራላዊ ሥርዓት በብሔርም ሆነ በስነ ምድራዊ አካባቢ ቢዋቀር በጥቅሉ ግጭት እንደማያጣው ይናገራሉ።

“ማንነትን ማዕከል ያደረገ ፌዴራላዊ ሥርዓት ሲዋቀር ደግሞ በተለይም ፖለቲካዊ በደል፣ ምጣኔ ሃብታዊ መገለል እና ባሕላዊ ጭቆና መገለጫዋ በሆነች አገር ውስጥ ሲሆን ግጭቶች የመከሰት ዕድላቸው ከፍ ይላል” በማለት ዶክተር አወል ለቢቢሲ ያስረዳሉ ።

የዘንድሮው በዓል በአፋር
Alex Solomon

ዶክተር አወል እንደሚሉት ሆኖም አሁን ያለው በሕገ-መንግሥት ፀንቶ የተቀመጠ ብሔርን መሰረት ያደረገው ፌዴራላዊ ሥርዓት አገሪቷ ውስጥ ለሚታዩ ነውጦች መነሻ ሆኗል ለማለት የሚያበቃ ማስረጃ የለም።

“ምክንያቱም ሕገ-መንግሥቱ በአግባቡ ሥራ ላይ አልዋለም” ይላሉ።

እንደዚያም ቢሆን ግን ሕገ መንግሥታዊ የፌዴራል ሥርዓት ግጭቶችን ጨርሶ ለማስቀረቱ ምንም መተማመኛ እንደሌለ ዶክተር አወል ያምናሉ።

የሕገ-መንግሥቱ በትክክል አለመተግበር ዋነኛው የጥያቄዎች ምንጭ መሆኑ ሲደመጥ የመጀመሪያው ባይሆንም ችግሩ እርሱ ብቻ ያለመሆኑን የሚከራከሩም ጥቂት አይደሉም።

ዶክተር ሰማኸኝ ከእነዚህ ወገን ናቸው፤ እርሳቸው እንደሚሉት ሕገ-መንግሥቱ በራሱ መርኁ ከፋፋይና ልዩነትን አግናኝ ነው።

ከዚህም በተጨማሪ ሕገ-መንግሥቱ የተረቀቀበት ሂደት ተቀባይነት አጠያያቂ ነው።

በተለይም በሽግግሩ መንግሥት እና ሕገ-መንግሥትን በመፃፉ ሒደት ውስጥ የተፈለጉ ፓርቲዎች ብቻ ተነቅሰው መሳተፋቸው ሂደቱ አካታች እንዳልነበር የሚያሳይ እንደሆነ ዶክተር ሰማኸኝ ይናገራሉ።

“በርካታ ኅብረ-ብሔራዊ ፓርቲዎች እና የአማራ ልኂቃን ሕገ-መንግሥቱን ከማርቀቅ ሂደቱ ተገልለዋል። ይህም በሁለቱ ወገኖች ዘንድ በሕገ-መንግሥቱ ላይም ሆነ ሕገ-መንግሥቱን በሚዘክሩ ክብረ በዓላት ላይ ጥርጣሬ እንዲኖር በር ከፋች ነው” የሚሉት ዶክተር ሰማኸኝ “ችግሮቹ የመዋቅርም የአፈፃፀምም ናቸው” ይላሉ።

Source    –   BBC/AMHARIC