Skip to content
የኦሮሚያ ክልል የሚያወጣቸው መረጃዎች ሚዛን የሚደፉ ይመስላሉ። አንድ ትልቅ እውነት ፤ ጨለንቆ አካባቢ ምንም ቦታ ከሶማሌ ክልል ጋር አይዋሰንም። በምዕራብ ሀረርጌ ዞን ሀዊ ጉዲና እና ዳሮ ለቡ የተባሉት አካባቢዎችም እንዲሁ ከስማሌ ክልል ጋር አይዋሰኑም። በአካባቢው አስተማሪ ሆነው ለሰባት ዓመታት የሰሩ ምስክር ለዛጎል እንደነገሩት በድፍን የቀደሞው ሃረርጌ ሶማሌዎችና ኦሮሞዎች መለየት በማያስችል ሁኔታ ግን የተቀላቀሉ ናቸው ። በጋዱሎ በሶማሌ ተወላጆች ላይ የጅምላ ግድያ መፈጸሙ ይፋ ከሆነ በሁዋላ እየተሰራጩ ያሉት ዜናዎች ከንጹሃን ሞት በላይ የሚያሳዝን ነው። መምህሩ እንዳሉት አብረው የኖሩና ሊለያዩ የማይችሉ ዜጎች ለምን ወደ ጸብ ገቡ? የሚለውን ጉዳይ መለየት ግድ ነው። ዛሬ ምን ተገኘና ተጣሉ? ማን ነው ከጀርባ? ለምን?
ሁለቱ ዜጎች የተዋለዱ፣ የተቀላቀሉ፣ ኦሮምኛው በሶማሊኛ የተለወሰ፣ እጅግ መለየት በማይቻል ደረጃ አንድ እምነት ያላቸው፣ የተጋመዱ ናቸው። መምህሩ እንደሚሉት እስካሁን እንደምታዘበው ኢህአዴግ የችግሩን መንሲኤ ቢያውቀውም ሊነካው አልወደደም። ፍርሃቻውም ከምን የመነጨ እንደሆነ አይገባኝም ባይ ናቸው። የኦሮሚያ ክልል ይህንን ብሏል። ከአቶ ሃይለማሪያም መግለጫ ጋር ሲመረመር ብዙ ሚስጥሮች አሉበት።
ታህሳስ 8/2010
ከታህሳስ 5/2010 ጀምሮ በምዕራብ ሀረርጌ ዞን ሀዊ ጉዲና እና ዳሮ ለቡ ወረዳዎች በተከሰቱ ግጭቶች የበርካታ ዜጎቻችን ህይወት አልፏል፥ አካል እና ንብረት ላይም ጉዳት ደርሷል።
በዞኑ ሀዊ ጉዲና እና የዳሮ ለቡ ወረዳዎች ከኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ጋር አይዋሰኑም። ሆኖም በርካታ የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ተወላጆች በነዚህ ወረዳዎች መንደሮችን መስርተዉ ክኦሮሞ ወንድሞቻቸዉ ጋር ለዘመናት በሰላም እና በፍቅር አብረዉ በመኖር ላይ ይገኛሉ። ታህሳስ 5/2010 ጀምሮ ግን በሃዊ ጉዲና ወረዳ የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ተወላጅ ወንድሞቻችን ከሚኖሩባቸዉ መንደሮች ሰላማዊዉን የሶማሌ ወንድሞቻችንን የማይወክሉ ታጣቂዎች ሰላማዊዉን ማህበረሰብ ተገን አድርገዉ ከአካባቢዉ እየተነሱ ኢብሳ እና ታኦ በሚባሉ ቀበሌዎች ላይ ጥቃት መፈፀም ይጀምራሉ። ከታህሳስ 5 እስከ ዛሬዉ ዕለት በሰነዘሩት ጥቃቶችም በተጠቀሱት ቀበሌዎች 29 የኦሮሞ ተወላጆች ሞተዋል። ከ360 በላይ መኖሪያ ቤቶችም ከነሙሉ ንብረታችዉ ወድመዋል።
በሃዊ ጉዲና ወረዳ በተፈፀመ ጥቃት ህይወታችዉን ካጡ ሰዎች መካከል አቶ አህመድ ጠሃ የተባለ በህብረተሰቡ ዘንድ ከፍተኛ ፍቅር እና ተቀባይነት ያለዉ ሰዉ ይገኝበታል። አቶ ዚያድ ጠሃ የተባለ የሟች አቶ አህመድ ጠሃ ወንድም ደግሞ በዳሮ ለቡ ወረዳ ጋዱሎ ቀበሌ ነዋሪ ነዉ። በሃዊ ጉዲና ወረዳ በተፈጠረዉ ግጭት የወንድሙን አቶ አህመድ ጠሃን ሞት የተረዳዉ አቶ ዚያድ በከፍተኛ የሀዘን ስሜት በመሆን ግብረአበሮቹን በማስተባባር ሃዊ ጉዲና ወረዳ ላይ ከተፈጠረዉ ግጭት ጋር ምንም ግንኙነት በሌላቸዉ በጋዱሎ ቀበሌ ነዋሪ በሆኑ ንፁሃን የኢትዮጵያ ሶማሌ ክልል ተወላጅ ወንድም እና እህቶቻችን ላይ ዘግናኝ እርምጃ ይወስዳል። እስካሁን በደረሰን ሪፖርትም በጋዱሎ ቀበሌ ነዋሪ የሆኑ የ32 የኢትዮጵያ ሶማሌ ተወላጆች ህይወት ማለፉን አረጋግጠናል።
የኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት በምዕራብ ሀረርጌ ዞን ሀዊ ጉዲና እና ዳሮ ለቡ ወረዳዎች በንፁሃን ዜጎች ላይ በደረሰዉ ጉዳት የተሰማዉን ጥልቅ ሀዘን እየገለፀ ህይወታችዉን ላጡ ዜጎች ቤተስቦች እና ወዳጆች መፅናናትን ይመኛል። የተፈፀመዉን ጥቃትንም አጥብቆ ያወግዛል። ጥፋተኞችንም በህግ ቁጥጥር ስር አዉሎ ለፍርድ ለማቅረብ በመስራት ላይ ይገኛል።
በሃዊ ጉዲና እና በዳሮ ለቡ የተፈጠሩ ዘግናኝ ጥፋቶች ማንኛዉንም ህዝብ አይወክሉም። ስለሆነም በኦሮሚያ ክልል የሚኖሩ ሁሉም ብሄር ብሄረስቦች እንደተለመደዉ አብሮነታችዉን አጠናክረዉ ሰላማዊ ኑሮአቸዉን እንዲቀጥሉ ጥሪዉን ያስተላልፋል። የኦሮሚያ ብሄራዊ ክልላዊ መንግስት ከሚመለከታቸዉ አካላት ጋር በመቀናጀት እንደዚህ አይነት ችግሮች ዳግም እንዳይከሰቱ ለማድረግ ጠንክሮ በመስራት ላይ ይገኛል።
Like this:
Like Loading...