የፓርላማ አባላት ለጠቅላይ ሚኒስትሩ ያቀረቡትን ጥሪ እሳቸውና የኢሕአዴግ አመራሮች ድርጅታዊ ምላሽ እየሰጡበት ነው

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ

7 December 2017

ዮሐንስ አንበርብር

የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት አባላት ወቅታዊ የአገሪቱ የፖለቲካ ውጥረቶችን በተመለከተ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ምላሽ እስኪሰጧቸው ድረስ መደበኛ ስብሰባዎችን እንደማይሳተፋ በመግለጻቸው ምክንያት፣ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ከሌሎች የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ አባላት ጋር በመሆን የፓርላማ አባላቱን በድርጅታዊ መዋቅር እንዳነጋገሩ ተሰማ። በዚህም ምክንያት የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ ኮሚቴ በአገሪቱ የተከሰተውን ውጥረት ለመፍታት እያካሄደ የነበረው ዝግ ስብሰባ ለጊዜው መቋረጡን የሪፖርተር ምንጮች ገልጸዋል።

ጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም በፓርላማው ተገኝተው ማብራሪያ እንዲሰጧቸው የፓርላማ አባላት ያቀረቡት ጥያቄ ከሕዝብ ተወካይ የሚጠበቅና ተገቢነት ያለው ቢሆንም፣ በአገሪቱ የሚስተዋለው ውጥረት ምክንያቱም ሆነ መፍትሔው ከገዥው ፓርቲ ውስጣዊ ዴሞክራሲ ጋር የተያያዘ በመሆኑ የፓርላማ አባላቱን በድርጅታዊ መዋቅር ማነጋገርና ለጥያቄዎቻቸው ማብራሪያ መስጠት መመረጡን ለጉዳዩ ቅርብ የሆኑ የሪፖርተር ምንጭ ተናግረዋል።
ምንጩ የአራቱ የኢሕአዴግ አባል ድርጅቶችን የሚወክሉ አባላትና የአጋር ድርጅቶች አባላት የየራሳቸውን ጥያቄና አስተያየት አሰባስበው፣ በነፃነት የኢሕአዴግ ሥራ አስፈጻሚ አመራሮችን እንደ ሕዝብ ተወካይነታቸው እንዲሞግቱ እየተደረገ መሆኑን ገልጸዋል።

አገሪቱ ለምንድነው እዚህ ሁኔታ ውስጥ የገባችው? በወቅቱ የተወሰደው ዕርምጃ ምንድን ነበር? ትክክለኛስ ነበር ወይ? የሚሉ ጥያቄዎችን ያለምንም መሸፋፈን መነሳታቸውንና አመራሩም ዝርዝር ምላሽ እየሰጠ መሆኑን ለማወቅ ተችሏል። ይህ ስብሰባ ሰኞ ታኅሳስ 16 ቀን 2010 ዓ.ም. ጀምሮ ሙሉ ቀን እንደዋለና በማግሥቱም መቀጠሉን የሪፖርተር ምንጭ ገልጸዋል።

ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የፓርላማ አባላት ፖለቲካዊ ይዘት ባላቸው የሕግ ማውጣትና ሥራ አስፈጻሚውን የመንግሥት አካል የመቆጣጠር ተግባር ጠንከር ባለ መንገድ እየተወጡና ተፅዕኖ እየፈጠሩ መሆናቸውን፣ ሒደቶቹን በመከታተል የቀረቡ ዘገባዎች ያስረዳሉ።

ባለፈው ሳምንት ዓርብ ኅዳር 13 ቀን 2010 ዓ.ም. ኦሮሚያ በአዲስ አበባ ላይ ያላትን ጥቅም ለመወሰን የሚመለከታቸው ቋሚ ኮሚቴዎች የጠሩት ሕዝባዊ ውይይት ላይ፣ የኦሕዴድ የፓርላማ አባላትና የክልሉ መንግሥት ተወካዮች ተገኝተው ውይይቱ እንዲራዘም በሰነዘሩት ጠንካራ ተቃውሞ ምክንያት፣ ውይይቱ ተቋርጦ ለሌላ ጊዜ መሸጋገሩን መዘገባችን ይታወሳል።

ፓርላማው ኅዳር 14 ቀን 2010 ዓ.ም. የነበረውን መደበኛ ስብሰባ ለማካሄድ የሚያስፈልገውን ምልዓተ ጉባዔ ለጥቂት በማሟላት፣ ለዕለቱ በያዛቸው አጀንዳዎች ላይ ተወያይቶ ውሳኔ ማሳለፉን መዘገባችን አይዘነጋም። የፓርላማው ምልዓተ ጉባዔ ከአጠቃላይ 547 አባላቱ መካከል 275 እና ከዚህ በላይ ሲገኙ መሆኑን ሕገ መንግሥቱ የሚደነግግ ሲሆን፣ በተጠቀሰው ዕለት የነበረው መደበኛ ስብሰባ ከመበተን የተረፈውም ከአጠቃላይ አባላቱ 275 አባላት ብቻ ተገኝተው ነበር። በዕለቱ ከቀረቡት አጀንዳዎች መካከል የክልሎችን ሥልጣን እንደሚጋፋ ስምምነት የተደረሰበት የከተማ ፕላን ረቂቅ አዋጅ አንዱ ነበር። በሌላ በኩል ኢሕገ መንግሥታዊ ነው የሚል ክርክር የቀረበበትን የደን ልማት ጥበቃና አጠቃቀም ረቂቅ አዋጅን ፓርላማው በኅዳር 26 ቀን ስብሰባው በ13 ድምፀ ተአቅቦ ማፅደቁን መዘገባችን ይታወሳል።

ኢሕአዴግ በሚመራበት ዴሞክራሲያዊ ማዕከላዊነት መርህ መሠረት ከፓርቲው የበላይ አካል የተሰጡ ውሳኔዎችን መቃወም፣ ለፓርላማ አባላት እንደ ዲስፕሊን ጥሰት ይቆጠርባቸዋል፡፡ በመሆኑም በረቂቅ አዋጁ ላይ የተቃውሞ ክርክር ያቀረቡ አባላትና ሌሎችም የተቃውሞ ድምፅ ከመስጠት ይልቅ ድምፅ ተአቅቦ ማድረግን መርጠዋል፡፡ አንድ ረቂቅ አዋጅ በ13 የኢሕአዴግ አባላት ድምፅ ተአቅቦ ሲፀድቅም የመጀመርያው ሊሆን እንደሚችል ቅርበት ያላቸው ባለሙያዎች ይናገራሉ፡፡

Source    –  Ethiopian Reporter